Site icon ETHIO12.COM

እየተረባረቡ ነው – ኢትዮጵያውያን ለሁሉም ነገር ዝግጁ እንሁን

• ኢትዮጵያውያን ለሁሉም ነገር ዝግጁ እንሁን!!!!!
• የምዕራባውያንን በተለይም የአሜሪካንን ያልተገባ እና አሣፋሪ ጫና ተቋቁመን መሻገራችን እሙን ነው!!!!!
• ከእባብ እንቁላል እርግብ አንጠብቅም!!!!!

ሁለት ነገሮች

አንደኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት እህል ጭነው ወደትግራይ የገቡ ተሽከርካሪዎች እየተመለሱ እንዳልሆነ ማስታወቁ ነው። ካለፈው ሀምሌ ወር አንስቶ 466 የእርዳታ እህል ወደትግራይ ይዘው ከሄዱ ከባድ የጭነት ተሽከርካሪዎች ውስጥ የተመለሱት 38 ብቻ ናቸው። የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት እንዳረጋገጡትም 93 በመቶ የሚሆኑት የእርዳታ ተሽከርካሪዎች በሄዱበት #ቀርተዋል። መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ትግራይ ገብተው የውሃ ሽታ ሆነው የሚቀሩት ተሽከርካሪዎች ለጁንታው ታጣቂዎች ማጓጓዣ እንዲሆኑ ተፈርዶባቸዋል። በተለይ አሁን ወደአማራ ክልል በወረራ በያዛቸው አከባቢዎች በሺዎች የሚቆጠሩ ታጣቂዎች እየተራገፉ ያሉት የእርዳታ እህል ጭነው ከገቡ በኋላ ህወሓት ባስቀራቸው ተሽከርካሪዎች ነው።

ብዙ ጥያቄዎች ይነሳሉ። መልስ ግን የሚኖራቸው ስለመሆኑ እርግጠኛ መሆን አይቻልም። ቁልፉ ጥያቄ ግን የተ.መ.ድ. ይህን በተመለከተ በግልጽና ጠንከር ባለ መግለጫ ህወሀትን የማያወግዘው ለምንድን ነው? ኢትዮጵያ ቢሮክራሲ አበዛች፣ በየቦታው የቁጥጥር ኬላ አስቀምጣ እንቅስቃሴውን አጓተተችብን እያሉ በየትዊተሩ እና ዓለምዓቀፍ መድረክ ላይ እርግማን የሚያዘንቡ ተቋማትና ባለስልጣናት የህወሀትን ቅጥ ያጣ ብልግና ለመናገር ምነው አፋቸው ተለጎመ??? የአሜሪካን ነገር እንኳን አንጀትና ቆሽት የሚያደብን ስለሆነ ባይነሳ ይመረጣል። የህወሀትን ሀጢያት በጽድቅ እየወሰደች ሽልማት የምትሰጥ፣ በተበዳይ ላይ ቅጣት የምትጥል፣ ለፖለቲካ ሽሪኮቿ ስትል ኢሰብዓዊነትን የምታበረታታ #ኢፍትሀዊ_ሀገር መሆኗን በሚገባ በማረጋገጧ ከእባብ እንቁላል እርግብ አንጠብቅም!!!! የኢትዮጵያ መንግስትስ አሁን ከያዘው አቋም ትንሽ መረር አድርጎ የተሽከርካሪዎቹን ቀልጠው መቅረትን ትልቅ የዲፕሎማሲ ነጥብ ማስቆጠር ለምን አልቻለም?!?

= ሁለተኛው ጉዳይ የአፈቀላጤ ጌታቸው ረዳ የሰሞኑ ንግግር ነው። ጌታቸው የግብጽ ደህንነት መስሪያ ቤት በሚዘውረውና የአልሲሲ ቡራኬ የሚሰጣቸው ሰዎች በሚጋበዙበት የቴሌቪዥን ጣቢያ ላይ ቀርቦ የህወሀትን እቅድ ይፋ አድርጓል። አዲስ ነገር አይደለም። በተግባር ላለፉት 40 ዓመታት የታየ ጉዳይ ነው። ህወሓት በኢትዮጵያ ፍርስራሽ ላይ ብቻ ህይወት ያለው ቡድን እንደሆነ ራሱም የሚደብቀው አይደለም። ኢትዮጵያን የሚፈልጓት እነሱ እስከገዟትና የትግራይ ብሄርተኝነት የበላይነትን ይዞ እስከቀጠለ ብቻ ነው። ከዚያ ውጭ የምትኖር ኢትዮጵያ ለህወሀት ፍርስርሷ መውጣት አለበት። አሁን እየተደረገ ያለው ጦርነትም ሌላ የተቀባባ ምክንያት ይሰጠዋል እንጂ ዋና ጉዳዩ ከወዲህ ያለው ነው!!!!

ጌታቸው በአልሲሲ (የግብፅ) ቲቪ ላይ ቀርቦ የተናገረውም ይህንኑ የሚያጠናክር ነው። ኢትዮጵያን የማፈራረስ ጦርነት ውስጥ መግባታቸውን፣ በውጤቱም የትግራይን መንግስት እውን እንደሚያደርጉ አፉ ሳይተሳሰር፣ ግልጽ በሆነ ቋንቋ ተናግሯል። ይህ ጦርነት የግብጽን አጀንዳ የተሸከመ ስለመሆኑ ከበቂ በላይ የሆነ ማስረጃ ነው። ማሽሞንሞን አያስፈልግም። ጌታቸው የድርጅቱን ፍኖተ ካርታ ፍንትው አድርጎ ነግሮናል። እንግዲህ ከዚህ የኢትዮጵያ ክፉ ጠላት ጋር ድርድር ይደረግ እያሉ የሚያላዝኑና ለራሳቸው “የሰላምና የእርቅ” ሻምፒዮን ክብር የሰጡ ‘ምክንያታውያን’ ግለሰቦች ከጌታቸው ረዳ ምስክርነት በኋላ አቋማቸውን ይቀይሩ ይሆን? ወይስ አሁንም ድርድር ወይም ሞት ብለው ይቀጥላሉ?!?

ኢትዮጵያዊነት በሚታለፍ ፈተና ላይ ይገኛል። ምዕራብ ዓለም በተለይም አሜሪካና የአውሮፓ ህብረት ለህወሀት የእብደት ጦርነት እውቅና ሰጥተው በተቃራኒው ሀገር ለማዳን የማይናወጥ አቋም በያዘው መንግስት ላይ ቅጣት ለመጣል እየተረባረቡ ነው። ህወሓት እያጠፋ፣ የሚቀጣው መንግስት ሆኗል። ህወሓት እየገደለ፣ የሚወነጀለው የዶ/ር አብይ አህመድ አስተዳደር ነው። ህወሓት እየዘረፈና ሀገር እያተራመሰ፣ የማዕቀብ ጋጋታው የሚጎርፈው በጠሚ/ር አብይ ላይ ሆኗል። መቼም እነአሜሪካን በኢትዮጵያ ጉዳይ ማንነታቸው እርቃኑን ለአደባባይ በቅቷል። የተጀቦኑበት ካባ ተገልጦ መለመላቸውን ለዓለም እየታዩ ነው። የፍትህ ገመድ ትቀጥን ይሆናል እንጂ አትበጠስም!!!!

የኢትዮጵያ ፍትህም ይዘገይ ይሆናል እንጂ የሚቀር አይሆንም!!!!! ኢትዮጵያ ማሸነፏ እውነት… መሻገሯም እሙን ነው!!!!!

Mesay Mekonnen

Exit mobile version