Site icon ETHIO12.COM

ኦኦ! አምላክ ሆይ! ስንት ነገር በስምህ ተነገደ?

ምን አለ መሰላችሁ? እንደሌላው ጊዜ ምንም የለም አልልም። በዚህች ፍትሃዊ ባልሆነች እና በተሰበረች ግን ደግሞ ለመኖር በምታጓጓ ዓለም ውስጥ ብዙ ነገር አለ።ለዚህም መሰለኝ አንድ በእድሜ ጠና ያለው “ሰባኪ” ወዳጄ አንዳንዴ በመሃል ኑሮ ሾጥ እያደረገው መሆኑ ትዝ ሲለው መሰለኝ ከፍ ባለ ድምፅ “እንኑርበታ! እኛም መኖር እንፈልጋለን እኮ!” ይላል።

በፊት በፊት ነገርን ንቀህ እና ቀለል አድርገህ እየተውክ ካልሆነ በስተቀረ ብዙ የምትተወው ሰው ይበዛል! ይባል ነበር – ያኔ ድሮአሁን አሁን ግን ንቄ ልለፈው የምትለው ነገር ብዙ ዋጋ ያስከፍላል። ህዝባችንን ያማረረው የኑሮ አስጨናቂ ፈተና፣ ስርዓት-አልበኝነት፣ የለት-ተዕለት ህይወት መወሳሰብ፣ ህገ-ወጥነት፣ አጉራ ዘለልነት፣ ጋጠወጥነት፣ ሁሉን አዋቂነት ወዘተ… ነገሮች ተዳምረው ህዝቡን ከትላንት ይልቅ ዛሬን በስጋት ውስጥ እንዲኖር አስገድዶታል።

ከተስፋ ይልቅ ፍርሃትን አንግሶበታል። ይህ ደግሞ ነገሮችን በጊዜ ከማስተካከል ይልቅ ንቆና በዝምታ የማለፍ ምክንያታዊ ውጤት ይመስለኛል። ችግሩ ማህበራዊ መናጋትንም አስከትሏል። “ምነው በእንቁላሉ ጊዜ … ” ያስብላል።ባሻዬ ይሄ ችግር ደግሞ መጠኑ ይለያይ እንጂ በመንፈሳዊውም ሆነ በዓለማዊውም ዓለም በተለይም በፓለቲካው፣ በማህበረ-ኢኮኖሚው፣ በሃይማኖታዊ መስክ … ብዙ የነሆለሉ የትየለሌ አብዬታዊ ዱርዬ ነጋዴዎችን ፈጥሯል መሰለህ።

በዚህ ምክንያት አየር ተይዞበታል-በህዝቡ።ታዲያ ከሚታየው ውስብስብ ሰው ሰራሽ አርተፊሻል ችግሮች አንፃር ሰውየው ከመንግስት መፍትሄ ሲያጣ “ኦ አምላክ ሆይ ስንት ነገር በስምህ ተነገደ!” ማለቱ ምን ይገርማል ታድያ? ሲያንስ ካልሆነ በስተቀር? ባሻዬ አንዳንድ ጉዳዮች እኮ ከመንግስት እጅ ያመለጡ እና ከህግ አቅም በላይ የሆኑ ይመስላሉ እኮ ጎበዝ።

ታዲያ አልተነገደም እንዴ? ተነግዷል እኮ ጃል! ችግሩ ሃይ ካልተባለ ገና እንደ ጉድ “ይነገዳላ”! ከአስር አመታት በፊት ከፍ ባለ ድምፅ”በስመ ቅዱሳን እርኩሳን!በስመ ምሁራን ሌቦች!” እያለ በአደባባይ ላይ ጮክ ብሎ “ይሳደብ” የነበረው “እብድ” ለካ ቀድሞ ታይቶት ነው ቶሎ ያበደው። ገብቶት ከሆነ ማበዱ ትክክል ነበርም ያስብላል። ስለዚህ ሁሉም ህዝብ ሳያብድ የማንም ወፈፌ ከመሬት እየተነሳ እንደፈለገኝ ልጋልብ፣ ላሳብድህ ሲለው ቁም! ስርዓት ያዝ ካላለው ማጠፍያው ይቸግራል።

መንግስት ግን ያዝ ለቀቅህን ተወት አድርግና ጭክን ብለህ ወገብህን ታጠቅና የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ለውጥ የሚያመጣ ጠንካራ አሰራርና ስርዓት ዘርግተህ ይሄንን አደጋ ከህዝቡ ላይ አስወግደህ አስገርመን እስኪ? ህዝቡም ከሚያብድ ይደነቅብህ በናትህ።እስከዚያው ድረስ ግን ህዝቡ “ኦኦ! መንግስት ሆይ! ስንት ነገር በስምህ ተነገደ?” ይልሃልና ፍጠን!

በላይ ባይሳ – ጥቅምት 7/2014 ዓ.ም

Exit mobile version