Site icon ETHIO12.COM

“እርዳታ የጫኑ አውሮፕላኖች መቐለ እንዳያርፉ ተለከለ”

በትናንትናው ዕለት የእርዳታ አውሮፕላኖች ከመቀሌ ሳያርፉ የተመለሱት በአየር ጥቃቱ ሳቢያ ሳይሆን በስፍራው በሚገኙ የበረራ ተቆጣጣሪዎች ፈቃድ በመከልከላቸው መሆኑን የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት አስታወቀ፡፡

የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ጉዳዩን አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ ፣ ትናንት የኢፌዴሪ አየር ሃይል በመቀሌ የአሸባሪው ህወሃት ቡድን የወታደራዊ ማሰልጠኛና ማዘዣ ማእከል የሆነውና የቀድሞ የመከላከያ ሰራዊት ማሰልጠኛ የነበረውን ቦታ በአየር መደብደቡን አስታውሷል፡፡

በዚሁ ዕለት ከኢትዮጵያ ፌደራል መንግስት በኩል ፈቃድ የተሰጣቸው ሁለት የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የእርዳታ አውሮፕላኖች መቀሌ እንዲያርፉ በስፍራው ካሉ የበረራ ተቆጣጣሪዎች ፍቃድ በመከልከላቸው ወደ አዲስ አበባ መመለሳቸውንም ጠቁሟል፡፡

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ቃል አቀባይ ስቴፈን ዱጃሪክ ፣ አውሮፕላኖቹ ከፌዴራል መንግስት ፈቃድ የተሰጣቸው እንደሆኑና ወደ አዲስ አበባ የተመለሱት በኤርፖርቱ የበረራ ተቆጣጣሪዎች ፍቃድ በመከልከላቸው ብቻ መሆኑንም አሳውቀዋል ነው ያለው መግለጫው፡፡

ይሁን እነጂ እውነታው ይህ ሆኖ ሳለ አንዳንድ የውጭ መገናኛ ብዙሃን የእርዳታ አውሮፕላኖቹ የተመለሱት በየአየር ጥቃቱ ሳቢያ እንደሆነ በማስመሰል የተሳሳተ ዘገባ ማሰራጨታቸውን ጠቅሷል፡፡

የአየር ጥቃቶቹ በከፍተኛ ጥንቃቄ የተወሰዱና የሽብር ቡድኑ ለእኩይ አላማ የሚጠቀምባቸውን የመገናኛና የወታደራዊ ማሰልጠኛዎችን ብቻ ኢላማ ያደረጉ መሆናቸው ተመላክቷል፡፡

የሽብር ቡድኑ ይህንን መሰል የተሳሳቱ መረጃዎችን በማውጣት ህብረተሰቡን በሃሰተኛ ምስሎች ለማወናበድ የሚወስዳቸውን እርምጃዎች ተገንዝቦ ጥንቃቄን መውሰድ እንዳለበትም ድርጅቱ ጥሪ አቅርቧል ሲል ፋና ዘግቧል።

በሌላ በኩል ከኢትዮጵያ መንግሥት ፈቃድ ተሰጥቷቸው ወደ ትግራይ ክልል ዋና ከተማ የበረሩት አውሮፕላኖች በመቐለ አውሮፕላን ማረፊያ የበረራ መቆጣጠሪያ ማማ እንዳይርፉ እንደተነገራቸው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ቃል አቀባይ ስቴፈን ዱጃሪች ጠቅሶ ሬውተርስ አርብ ዘግቦ ነበር።

በተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ ጉዳዮች እና አስቸኳይ ዕርዳታ አስተባባሪ ማርቲን ግሪፊትዝ በበኩላቸው ባወጡት መግለጫ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የዕርዳታ አውሮፕላን ወደ መቐለ ያደረገው በረራ “በአየር ድብደባ ምክንያት” መስተጓጎሉን አመልክተዋል። አያይዘውም “የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ከአየር ድብደባዎቹ በፊት ማስጠንቀቂያ አልተሰጠውም” ብለዋል። እንደ እሳቸው አባባል መንግስት ወታደራዊ ጥቃት ከመፈጸሙ በፊት ሊያስታውቃቸው እንደሚገባ ነው። ግሪፊትዝ ለበረራ መንግስት አስፈላጊ ፈቃድ ሰጥቶት እንደነበር አምነዋል።

Exit mobile version