Site icon ETHIO12.COM

በነጭ ፕሮፓጋንዳ የሚፈርስ ሀገር የለም! የገባንበት ጦርነት የህልውና ጦርነት ነው!

ኢትዮጵያ የማዳን ጥሪን ተከትሎ እየተመመ ያለው የህዝብ እንቅስቃሴ ኢትዮጵያ በቁርጥ ቀን ልጆቿ ተጋድሎ የጥፋት ኃይሎችን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለመቅበር ያላትን ዝግጁነትና ተግባር የሚያመለክት ነው፡፡ በቅርቡ በፌደራልና የክልል መንግስት አስፈፃሚዎች የግንኙነት መድረክ ለመላው ኢትዮጵያውን ለቀረበው ጥሪ መላው ህዝባችን በተለይም ወጣቱ የህብረተሰብ ክፍል ያሳየው ምላሽና ተነሳሽነት በእጅጉ የሚደነቅ ነው፡፡

ከሁሉም የኢትዮጵያ ክፍሎች ኢትዮጵያውያን ተቆጥተው በሁሉም አቅጣጫ በተደራጀ አግባብ ወደ ጦር ግንባር እየተመሙ ይገኛሉ፡፡ ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን በማሸነፍ ወኔ፣ ሥነ-ልቦና፣ ጀግነትና ቁጭት ግንባሩን እየተቀላቀሉ ይገኛሉ፡፡ የበረሃ አንበሶቹ የአፋር ልዩ ኃይልና አይበገሬዎቹ የአፋር ወጣቶች ወደ ክልላቸው ለመስፋፋት ያሰፈሰፈውን ኃይል ከጀግናው መከላከያ ሰራዊት ጋር ህብር ፈጥረው ጠላትን አይቀጡ ቅጣት በመቅጣት ሽንፈት እንዲከናነቡ በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡ በጠላት ቁጥጥር ስር ባሉ አካባቢዎች ጉዳይ አስፈፃሚ አድርጎ ያስቀመጣቸው አመራሮች ላይ ህዝቡ እርምጃ በመውሰድ ላይ ይገኛል፡፡ በሁሉም ግንባሮች ጠላትን ለመቅበር ህዝቡና የወገን ጦር አንድነቱን አጠናክሮ ቀጥሏል፡፡

የአሸባሪው ቡድን ትሕነግና ፍልፍሎቹ አለን የሚሉትን ኃይል በማሰባሰብ በወገን ጥምር ጦር ከበባ ውስጥ እየገቡ ናቸው፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተከትሎና በወገን ኃይል ከፍተኛ ንቃትና መነሳሳት ተፈጥሯል፡፡ አይጥ ከጉድጓዷ እየራቀች በሄደች ቁጥር መሞቻዋ ነው እንደሚባለው የጠላት ግብዓተ መሬት ተቃርቧል፡፡

የጥፋት ኃይሉ የዓለም አቀፉን ማህበረሰብ ለማሳሳት የዘር ማጥፋት በትግራይ ህዝብ ላይ ተፈፅሟል፣ የትግራይን ህዝብ ለማንበርከክ ረሀብ እንደ ጦር መሳሪያ ተጠቀሟል፣ አስገድዶ መድፈርን የትግራይን ህዝብ ለመቅጫነት የኢትዮጵያ መንግስት ተጠቅሟል ወዘተ እያለ ሲጠቀምባቸው የነበሩ አሰልቺ ስብከቶቹ በዓለም አቀፍ ገለልተኛ ተቋም በተደረገው የእውነት ማፈላለግ ስራ እነዚህ ጉዳዮች በኢትዮጵያ መንግስት እንዳልተፈፀሙ ተረጋግጧል፡፡

በቁጣ የተነሳሳው የህዝብ ማዕበል ያስበረገገው የሽብር ቡድኑ ማሽኖችና በሽርክና የሚሰሩ ሚዲያዎች የመጨረሻ ያሉትን የሽብር ወሬ በማሰራጨት ተጠምደዋል፡፡ ቁልፍ ኢላማቸው አድርገው የወሰዱት ደግሞ በአመራሩ፣ በህዝቡና በወገን ጦር መካከል ጥርጣሬ እንዲፈጠር፣ ፍርሃት እንዲነግስ የማሸበር ስራ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ግጭት እንዲባባስ አበክረው የሚሰሩ እንደ ፌስቡክ አይነት የማህበራዊ ሚዲያዎች የጠቅላይ ሚኒስትራችንን መዕልክቶች ከገፁ በመሰረዝ አጋርነቱን አሳይቷል፡፡

እንደ ሮይተርስ ያሉት ደግሞ በጠላት ያልተያዙ አካባቢዎችን እንደተያዙ በማስመሰል የተሳሳተ መረጃ እየዘገቡ ይገኛሉ፡፡ በተለያየ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ውስጥ ያሉ ተላላኪዎቻቸው የፀጥታ ችግር እንዳለ በማስመሰል የግል ትምህርት ቤቶች እንዲዘጉ የማግባባት ስራ እየሰሩ ይገኛሉ፡፡ በህዝቡና በወገኑ ጦር ውስጥ ጥርጣሪዎችን ለመፍጠር የመንግስት ባለስልጣናት ቪዛ እየጠየቁ ነው በሚል የውሸት ፕሮፓጋንዳ እየነዙ ነው፡፡ ከዲፕሎማሲ መርህ ውጪ የአንዳንድ ሃገር ኤምባሲዎች አዲስ አበባ እንደ ተከበበች በማስመሰልና ያሰቡት ውጥን እንዲሳካ በኤምባሲያቸው የሚሰሩ ዜጎቻቸው ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ እያሳሰቡ ይገኛሉ፡፡

መንግስት በእንዲህ አይነት መንገድ ሀገርን ለማፍረስ የተጠመዱ ወገኖች ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ እያሳሰበ በሀገር ጉዳይ ቀልድ የለምና ከድርጊቱ ባልተቆጠቡት ላይ የማያዳግም ርምጃ እንደሚወስድ ያስጠነቅቃል፡፡ መላው ህዝባችን ኢትዮጵያን የማዳን የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ የምንገኝ መሆኑን ተገንዝቦ የጀመረውን ሀገር የማዳን ንቅናቄ አጠናክሮ እንዲቀጥል፣ ዋስትናችን ህልውናችንን በአንድነት ማረጋገጥ መሆኑን በመረዳት በአፍራሽ ኃይሎችና ግብር አበሮቻቸው በኩል የሚነዙ የውሸትና መርዛማ ወሬዎቻቸው የሚመጡበት መንገድ በመዝጋት በአንድነት የመነሳቱን እንቅስቃሴ አጠናክሮ መቀጠል አለበት፡፡

የኢትዮጵያውያንና የወዳጅ ሀገር ሚዲያዎች ለህብረተሰባችን ትክክለኛውን መረጃ በወቅትና በተገቢው ጊዜ እንድታቀርቡ መንግስት ይጠይቃል፡፡ በጊዜያዊ ድሎች መወራጨት የጀመሩትን የጥፋት ኃይሎች የማይናወጥ ዘላለማዊ ድሎችን በማስመዝገብ ወርቃማ ታሪክ መፃፍ ያለብን አሁን ነውና ሁላችንም በአንድነት እንቁም፡፡ ከውስጥም ሆነ ከውጭ ከታሪካዊ ጠላቶቻችን የታቀደልንና የተደገሰለንን ድግስ በጋራ በጣምራ ክንዳችን እንወጣዋለን፡፡ እኛ ኢትዮጵያውያን ለሉአላዊነታችን፣ ለአንድነታችን እና ለማንነታችን ሞት ክብራችን ነው! ከመሥዋዕትነት ውጪ ኢትዮጵያዊነት የለም!!

ኢትዮጵያ ታሸንፋለች
የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት

_ አካባቢህን ጠብቅ
_ ወደ ግንባር ዝመት
_ መከላከያን ደግፍ


Exit mobile version