Site icon ETHIO12.COM

“ቆንጆዎቹ “ራሳቸውን ይፋ አድርገዋል!

ጸሃፊው ጌታቸው ሽፈራው “አጭበርባሪዎቹ ራሳቸውን ይፋ አድርገዋል!” በሚል ቢሰየመውም ከአናቱ ለማለዘብ “ቆንጆዎቹ” በሚል የቀድሞ የትህነግ አባላትና ምልምሎች ስም ተክተነዋል። ጽሁፉ ሙሉ በሙሉ የጸሃፊው ሃሳብ ብቻ ነው።

Ethiopia : ከሶስት ወር በፊት የኢትዮጵያ ተቆርቋሪዎች ነን የሚሉ አጭበርባሪዎች ራሳቸውን ግልፅ ሳያደርጉ መግለጫ ሰጥተው ነበር። በጊዜው ስማቸውን ያልጠቀሱበትን ምክንያት ሲያስቀምጡ “ሰው ሀሳባችን በደንብ ሳይሰማ ይፈርጀናል” የሚል ውሽልሽል ምክንያት ነበር። ይሁንና እነማን እንደሆኑ ይታወቁ ነበር። ያሰባሰባቸው ስዬ አብርሃ ነው። ልደቱ አያሌው፣ ታምራት ላይኔና ያሬድ ጥበቡ አሉበት። ከሚዲያ የርዕዮቱ ቴዎድሮስ አለ። እነ ኤርሚያስ ለገሰም ያግዛሉ። ይህ ቡድን በወቅቱ የትግሬ ወራሪ ኃይል ወልቃይት ጠገዴ በኩል ኮሪደር ይሰጠው ብሎ ቅድመ ሁኔታ ባለው ዝባዝንኬ አስቀምጧል።

የትግሬ ወራሪ ኃይልን ደፍሮ አይተቸውም። “አዲሱ ኢህዴን” በሚል የፃፍኩት በየዩቱዩቡ አለ። እነ ያሬድ አይደለንም ብለው መጥተው ነበር። ቴዎድሮስ ፀጋዬም ክዶ ነበር። ተጨባጭ መረጃ ይዤ “እነሱ ናቸው” ብዬ ለፃፍኩት ፅሁፍ ኢትዮ 360 በፕሮግራሙ መሃል እኔን ተሳድቦ አልፎታል። ታምራትና ያሬድ አንድ ሙሉ ፕሮግራም ላይ ቀርበው ክደዋል። ቴዎድሮስ ሌላ አንድ የስድብ ፕሮግራም አዘጋጅቶበታል። ያሬድ ሌሎች ፕሮግራሞች ላይ ቀርቦ ክዷል። እኔ በተጨባጭ መረጃ ነበር የፃፍኩት። የካዱት ዛሬ ብቅ ብለዋል።ዛሬ እነዛ አጭበርባሪዎች በይፋ መጥተዋል። ያኔ የኢዮጵያ ተቆርቋሪዎች ነበር። ዛሬ መሃሉ ላይ ሕልውና የሚል ሰንቅሮ “የኢትዮጵያ ሕልውና ተቆርቋሪዎች” ብሎ መጥቷል። ከመግለጫው ላይ የታምራት፣ የልደቱና የያሬድ ፎቶ ተለጥፏል። ያኔ ሌላ ሰው ነበር ያነበበው ዛሬ ያሬድ አንብቦታል። ለምንኛውም ጉዳዮች እንዴት ወደዚህ አመሩ? የሚለውን እንመልከት።

1) ርዕዮት ሚዲያና ኢትዮ 360 አንድ ላይ ሆነው በሕዝባችን ላይ ሲዘምቱ፣ በግልፅ ሕዝባችን ላይ የሚዘምተው ቴዎድሮው የ360 ሰዎችን ሲጋብዝ “እረፉ” ብለን አጋለጥን። ለጊዜው በይፋ በጋራ መስራታቸውን አቆሙ። ርዕዮት በግልፅ የትግሬ ወራሪ ኃይልን አላማ ሲያራምድ እነ ኤርሚያስ ሰበብ ፈልገው የትህነግን አላማ ማስተጋባት ቀጠሉበት። እየተገባበዙ ፕሮግራም መስራታቸውን ግን አቆሙ።
2) ልደቱ አያሌው ተደብቆ ከርሞ ነበር። አንድ ፅሁፉ በኢትዮ 360 አስነብቦ ወደ መድረኩ መመለሱን አሳወቀ። ወዲያውኑ ቃለ መጠይቅ አደረጉለት። በኢትዮ 360 ቃለ መጠይቅ ከተደረገለት ጥቂት ቀናት በኋላ፣ በጓድነታቸው መሰረት ርዕዮት ሚዲያ ቃለ መጠይቅ አደረገለት። በቀጥታ ርዕዮት ሚዲያ ላይ ያልወጣው፣ በርዕዮትም ያልተዋወቀው ወያኔን እየደገፈ ነው እንዳይባል አስቦ ነው።
3) ይህ ቡድን በትንሹ 3 ሚዲያ አለው። ኢትዮ 360 ውስጥ ያለው አባላቸው ስልታዊ በሆነ መንገድ ያግዛል። ርዕዮት በደንብ ይሄድበታል። በጣም የደፈረ ደግሞ TMH ድረስ ይሄዳል። ያሬድ ጥበቡ TMH ድረስ ሄዶ ቃለ መጠይቅ አድርጓል። ሰሞኑን አበበ ተክለሀይማኖት ጋር ሆኖ ለአለቆቹ ታማኝነቱን አሳይቷል። የሕዝብን ሙቀትም መለኪያ ነው። የትግሬ ወራሪ ኃይልን ሰበር ዜና ሲያጋራ ይውላል። ገፁ ገብታችሁ ማየት ትችላላችሁ።
4) በተለያዩ መድረኮች፣ በማሕበራዊ ሚዲያ፣ በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ድርድር ወዘተ የሚለውን ሊያስለምዱን ይጥራሉ። አሁን በይፋ መጥተውበታል።
5) ነገሮች ቀርበዋል ብለው ሲያስቡ ደግሞ በግልፅ መጥተዋል። ዛሬ ደብረፅዮን መቀሌ ላይ ስለ ሽግግር መግለጫ ሰጠ። ከደብረፅዮን መግለጫ ሁለት ሰዓት ብቻ ዘግይቶ የእነ ልደቱ (አሰባሳቢው ስዬ አብርሃ ነው) መግለጫ ወጣ። በደንብ ተናብበው ነው። የግድ የአለቆቻቸው መግለጫ ከመቀሌ መቅደም ነበረበት። ኢትዮ 360 ከደብረፅዮን መግለጫ አራት ሰዓት፣ ከእነ ልደቱ ሁለት ሰዓት ዘግይቶ የእነ ደብረፅዮን መግለጫን ሰበብ አድርጎ ወጣ ገባ እያለ የምናውቀውን ስራውን ቀጥሏል።
6) ደብረፅዮን በመግለጫው አማራ ክልልን የማይወክሉ አማራ ኢሊቶች አብረውን ይሰራሉ ብሏል። የትግራይን ጀኖሳይድ እውቅና የሚሰጥ አብሮን ይሰራል ብሏል። ታምራትም፣ ልደቱም፣ ያሬድም ለትግሬ ወራሪ ሲያደገድጉ ነው የከረሙት። ኢሳያስን ሲረግሙ፣ የሀሰት ሰብአዊ መብት ሪፖርትን ሲያመነዥኩ ነው የከረሙት።

አሁን ግልፅ ሆኗል። ከሶስት ወር በፊት ጠርጥር አዲሱ ኢህዴን መጣልህ ስል ብዙ ሰው ውሸት መስሎት ነበር። እንሆ ራሳቸው አምነዋል።

ለተያያዘው መረጃ ግንዛቤ:-

በጌታቸው ሽፈራው


Exit mobile version