ETHIO12.COM

ለሶስት ዓመታት አትላስ ሆቴል የመሸገ ተጠርጣሪ ተያዘ፣ በትህነግ ደጋፊ ቤት በጥቆማ የጦር መሳሪያ ተገኘ

May be an image of 1 person

በአትላስ ሆቴል ለሶስት ዓመታት አልጋ ተከራይቶ የሽብር ድርጊት ሲፈጽም የነበረ ተጠርጣሪ በቁጥጥር ስር ዋለ።በአዲስ አበባ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 02 በሚገኘው አትላስ ሆቴል ውስጥ ለሶስት ዓመታት አልጋ ተከራይቶ የሽብር ድርጊት ሲፈጽም የነበረ ተጠርጣሪ በቁጥጥር ስር መዋሉን የኢዜአ ምንጮች ጠቅሶ ነው ያስታወቀው። ተጠርጣሪው ከሽብርተኛው ሸኔ ጋር በህቡዕ በመገናኘት ተልዕኮዎችን ሲያስተባብር እንደነበር የሚያሳይና የሃሰት መረጃ የሚያሰራጭበት ማስረጃ ተይዞበታል።

ተጠርጣሪው ባረፈበት ሆቴል ውስጥ በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻ አደንዛዥ ዕፅ፣ ሶስት ኮምፒዩተሮች፣ ሁለት ፕሪንተሮች፣ ሰባት የተለያዩ ማህተሞች፣ አንድ ላፕቶፕና አንድ ትልቅ ማይክ ተገኝቷል። እንዲሁም በማህበራዊ ሚዲያዎች ለመልቀቅ ያዘጋጀቸው የሃሰት ፕሮፓጋንዳ ሰነዶች ከሁለት ግብረአበሮቹ ጋር በቁጥጥር ስር መዋሉን ለመረጃው ቅርበት ያላቸው ምንጮቻችን አመልክተዋል።

በሌላ ተመሳሳይ የፖሊስ ዜና “ከአሸባሪው ህወሃት ጋር ትስስር እንዳላት የተጠረጠረች”ግለሰብ ቤት የጦር መሳሪያዎች ተገኝተዋል። ፖሊስን ጠቅሶ ኢዜአ እንዳለው ከአሸባሪው ህወሃት ጋር ትስስር እንዳላት በተጠረጠረች ግለሰብ ቤት የጦር መሳሪያ የተገኘው በፍተሻ ነው።

የኢዜአ ምንጮች እንዳመለከቱት የአካባቢው ህብረተሰብ ግለሰቧ ከአሸባሪው ህወሃት ጋር ትስስር እንዳላት ለፖሊስ ባደረሱት ጥቆማ መሰረት በግለሰቧ መኖሪያ ቤት ውስጥ በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻ ሁለት ክላሽንኮቭ ጠመንጃዎች ከ60 መሰል ጥይቶች ጋር እንዲሁም ሁለት ሽጉጦች ከ20 መሰል ጥይቶች ጋር በፀጥታ አካላት በቁጥጥር ስር ውሏል።

ከሽብርተኞቹ ህወሃትና ሸኔ ጋር የህቡዕ ትስስር በመፈፀም ሀገር በማተራመስና በማፍረስ ሴራው ውስጥ ለመሳተፍ ዝግጅት እያደረጉ ያሉ ተጠርጣሪዎችን በህግ ቁጥጥር ስር የማዋሉ እንቅስቃሴ ተጠናክሮ መቀጠሉንም ዜናው ጨምረው ገልጿል።

የመከላከያ ሠራዊት እና የፖሊስ የደንብ ልብሶችን ለጥፋት ቡድኖች ሊያስተላልፉ የነበሩ ተጠርጣሪዎች ቁጥጥር ስር ዋሉ

በተመሳሳይ የሽብር ዜና በቡራዩ ከተማ የመከላከያ ሠራዊት እና የፖሊስ የደንብ ልብሶችን ለጥፋት ቡድኖች ለማስተላለፍ ሲዘጋጁ የነበሩ ተጠርጣሪዎች ቁጥጥር ስር መዋላቸው ታውቋል። በቁጥጥር ስር የዋሉት ተጠርጣሪዎቹ በፈጠሩት ህቡዕ ህዋስ በኩል ከአዲስ አበባ ወደ ምዕራቡ የሀገሪቱ ክፍል ለማስተላለፍ እና ለአሸባሪው ሸኔ ለመስጠት ሲዘጋጁ እንደነበር የወረዳ 3 ፖሊስ ጣቢያ አዛዥ ኢንስፔክተር ኦላና ብርሃኑ ሞሲሳ ገልጸዋል። ኅብረተሰቡ አሁንም በያለበት አካባቢውን በንቃት እንዲጠብቅ እና አጠራጣሪ እንቅስቃሴዎችን ሲመለከት ለፀጥታ ኃይሎች በፍጥነት እንዲያሳውቅ ኢንስፔክተር ኦላና ብርሃኑ ማሳሰባቸውን ኦቢኤንን ጠቅሶ ኢብኮ ዘግቧል።

ሌላው የሽብር ዜና – የአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ፖሊስ ከህብረተሰቡ በደረሰው ጥቆማ ለሽብር ተግባር ሊውሉ የነበሩ ቁሳቁሱች መያዙን አስታውቋል፡፡

የክፍለ ከተማው ፖሊስ ከሌሎች የፀጥታ ሀይሎች ጋር ባደረገው የተቀናጀ ፍተሻ የነፍስ ወከፍ መሳሪያዎች፣ የብሬል ጥይቶች፣ የአጭር ርቀት መገናኛ ሬድዮኖች እንዲሁም የጦር ሜዳ መነፅርና ተጥለው የተገኙ ቦምቦች ጨምሮ በግለሰብ እጅ መገኘት የሌለባቸው መሳሪያዎችን በቁጥጥር ስር ማዋሉን አስታውቋል፡፡በተጨማሪም የሽብር አባላት መመልመያ እና ማሰልጠኛ ሰነዶች የተገኙ ሲሆን በተለይም የአሸባሪው ህወሃት ጁንታ መታወቂያና በሽብር ቡድኑ መሪ የተፈረመ የምስክር ወረቀቶች መገኘት መቻላቸውን ታውቋል። ክፍለ ከተማው የኦሮሚያ አዋሳኝና ማስፋፊያ ክፍለ ከተማ እንደመሆኑ በርካታ ፀጉረ ልውጦችን እና ሰርጎ ገቦችን ለመለየት እንዲሁም እነሱ ለእኩይ ሴራቸዉ ልጠቀሙባዉ ያሰቡትን መሣሪያዎች የህብረተሰቡ ጥቆማ አስፈላጊ በመሆኑ የተለመደ ትብብሩን አጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ መገለጹን የአቃቂ ቃሊቲ ኮሚኒኬሽን ያወጣው መረጃ ያመክታል፡፡ህዳር 16 ቀን 2014 ዓ.ም

Exit mobile version