Site icon ETHIO12.COM

የአገር መከላከያ ሰራዊትና የአማራ ልዩ ኃይል ጋሸናን ተቆጣጠረ: ወደ ወልድያ እየገሰገሰ ነው


በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ እየተመራ በሁሉም ግንባሮች ወደ ከፍተኛ የማጥቃት እንቅስቃሴ የገባው የ”ዘመቻ ለኅብረ ብሔራዊ አንድነት” አስደናቂ ውጤቶችን እያስመዘገበ ይገኛል ሲሉ የመንግስት ኮምንኬሽን አገልግሎት ሚኒስትሩ ዶ/ር ለገሰ ቱሉ አስታውቀዋል።

በዚህም መሰረት በጋሸና ግንባር ጀግናው የሀገር መከላከያ ሰራዊት፣ የአማራ ልዩ ሀይል ሚሊሻና ፋኖ በጥምረት ባደረጉት ተጋድሎ የአርቢትን፣ የአቀትን፣ የዳቦና የጋሸና ከተሞችን ነጻ አውጥተዋል።

በዚህ ግምባር ጠላት ለበርካታ ወራት የዘረፈውን ሀብት በመጠቀም በወረራ የያዘውን አካባቢ ህዝብ በማስገደድ ያሰራውን ባለብዙ እርከን ኮንክሪት ምሽግ በተቀናጀ እቅድ፣ አመራርና ቴክኖሎጂ በመታገዝ በአነስተኛ መስዋዕትነት ምሽጉ ተሰብሯል።

በዚህ ግንባር በርካታ የነፍስ ወከፍና የቡድን ከባድ መሳሪያዎች በወገን ጦር ተማርከዋል።

ይህ ድል ለዝርፊያ የገባውን የጠላት ሀይል ወገቡን የቆረጠ ነው።

የወገን ጦር ጋሸናን መቆጣጠሩ ጠላት በላሊበላ፣ ወልዲያና ደሴ የተቆጣጠራቸውን አካባቢዎች በአጭር ጊዜ ውስጥ ለማጽዳት መንገዱን ምቹ ያደርጋል።

የወገን ጦር የጋሸናን እና አካባቢውን ከመቆጣጠር አልፎ በላሊባለ፣ ወልዲያና ወገል ጤና አቅጣጫ በአሁኑ ሰአት ወደፊት እየገሰገሰ ይገኛል።

በወረኢሉ ግንባር የጃማደጎሎ ወረኢሉ ገነቴ፣ ፊንጮፍቱ፣ አቀስታ ከተሞች በጀግኖቹ የሀገር መከላከያ ሰራዊት፣ የአማራ ልዩ ሀይ ሚሊሻና ፋኖ ጥምረት ከአሸባሪው ነጻ ወጥተዋል።

በሸዋ ግንባር የመዘዞ፣ ሞላሌ፣ ሸዋሮቢትና አካባቢው እንዲሁም ራሳና አካባቢው ጀግኖቹ የሀገር መከላከያ ሰራዊት፣ የአማራ ልዩ ሀይል ሚሊሻና ፋኖ በጥምረት ባደረጉት ተጋድሎ ከአሸባሪው ህወሓት ነጻ ወጥተዋል። ጅግኖቹ ወደፊት እየገሰገሱም ይገኛሉ።

በምስራቅ ግንባር በጀግናው የሀገር መከላከያ ሰራዊት፣ የአፋር ልዩ ሀይልና ሚሊሻ ባደረጉት ተጋድሎ ነጻ የወጡት የካሳጊታ፣ ቡርቃ ዋኢማ ጪፍቱ ድሬሩቃ፣ ጭፍራ አለሌ ሱሉላ ከተሞች ሙሉ በሙሉ ከጠላት ጸድተዋል፤ የአካባቢው አስተዳደር ወደ ቦታው ተመልሷል።

የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዶክተር ለገሰ ቱሉ በዛሬው ዕለት በሰጡት መግለጫ ፣ ጀግናው የሀገር መከላከያ ሰራዊት፣ የአማራ ልዩ ሃይል፣ ሚሊሻና ፋኖ በጥምረት ባደረጉት ተጋድሎ በጋሸና ግንባር የአርቢትን፣ የአቀትን እና የጋሻና ከተሞችን በቁጥጥር ስር አውለዋል፡፡

በዚህ ግንባርም ጠላት ለበርካታ ወራት የዘረፈውን ሃብት በመጠቀም እና የአካባቢውን ማህበረሰብ በማስገደድ የገነባው ኮንክሪት ምሽግ በተቀናጀ እቅድ የአመራር ጥበብ እና ቴክኖሎጂ በመታገዝ በአነስተኛ መስዋዕትነት መስበር ተችሏል ነው ያሉት፡፡

ከዚህ ባለፈም በዚህ ግንባር በርካታ የነፍስ ወከፍ፣ የቡድን እና ከባድ መሳሪያዎች በወገን ጦር መማረካቸውን ነው የገለጹት፡፡

ከታወጀ 3 ሳምንት ያስቆጠረው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በርካታ ውጤቶች የተገኘበት እንደሆነ የጠቅላይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት ፕሬስ ሴክሬተሪ ቢልለኔ ስዩም አስታውቀዋል።

የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት ፕሬስ ሴክሬተሪ ቢልለኔ ስዩም ለውጭ መገናኛ ብዙኃን ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።

በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በተደረጉ ፍተሻዎች ቀላል እና ከባድ የጦር መርሳሪያዎች፣ የጦር ሜዳ የመገናኛ መሳሪያዎች፣ የሀሰት መታወቂያዎች፣ ከመከላከያ እና ከፌዴራል ፖሊስ የተዘረፉ መለያ ልብሶች፣ ፌክ ፓስፖርቶች፣ ፎርጅድ የውጭ ሀገርና የኢትዮጵያ ገንዘቦች የተያዘ ሲሆን የአስቸኳይ ግዜ አዋጁም ውጤታማነት የተረጋገጠበት ነው ብለዋል።

በህግ ማስከበር እርምጃው የትግራይ ወጣቶች በአሸባሪው ህወሓት ቡድን ለጦርነት እየተማገዱ መሆኑን የጠቆሙት ፕሬስ ሰክሬተሪዋ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥና የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ወደ ጦር ግንባር ካቀኑ ሳምንት እንደሆናቸው ገልፀዋል።

የትግራይ ወጣቶች በሰላማዊ መንገድ እጅ እንዲሰጡ በጠቅላይ ሚኒስትሩ በድጋሚ ጥሪ እንደቀረበላቸውም አስታውቀዋል።

የሰብኣዊ እርዳታ አቅርቦትን በተመለከተ በአማራ ክልል በአሸባሪው ህወሓት ጦርነት በመክፈቱ ምክንያት ከ1.1 ሚሊዮን በላይ ዜጎች መፈናቀላቸውን ገልጸዋል።

በጦርነቱ ምክንያት በአማራ ክልል ከ5 ሚሊዮን በላይ ዜጎች መጎዳታቸውን፤ በአፋር ክልል ደግሞ ከ260 ሺህ በላይ ዜጎች ላይ በጦርነቱ ምክንያት ጉዳት የደረሰባቸው ሲሆን ከ100 ሺህ በላይ ዜጎች ደግሞ መፈናቀላቸውን ተናግረዋል።

ጉዳት በደረሰባቸው አካባቢዎች ተጎጂዎች ለመድረስ እንዲያስችልም የፌዴራል መንግስትና የክልል መንግስታት አጋር አካላት፤ በጥምረት፣ የአደጋ ስጋትና ስራ አመራር ኮሚሽን ጋር በተቀናጀ መልኩ የሰብኣዊ እርዳታ አቅርቦት ላይ እየሰራ መሆኑንም አብራርተዋል።

እስካሁን ባለው ሂደት ወደ መቀሌ ሁለት በረራዎች መካሄዳቸውንና 40 ሚሊዮን ብር ደግሞ በሰብኣዊ እርዳታ ለሚንቀሳቀሱ አጋር አካላት አስተዳደራዊ ወጪ እንዲሆን መፈቀዱንም አብራርተዋል።

333 ሰብኣዊ እርዳታ የጫኑ ተሽካርካሪዎች ወደ መቀሌ መጎዋዛቸውንም አንስተዋል።

160 እርዳታ የጫኑ ተሽከርካሪዎች 9 ሺህ 600 ሜትሪክ ቶን ምግብና ምግብ ነክ ያልሆኑ እርዳታዎች ጭነው ወደ መቀሌ መጫናቸውን ተናግረዋል ሲል ኤፍቢሲ ዘግቧል።

Exit mobile version