Site icon ETHIO12.COM

ከ32 ቢሊየን ብር በላይ ሀሰተኛ ግብይት መፈጸሙ ተገለጸ

ህገ-ወጥ ድርጅቶች ሲጠቀሙባቸው ከነበሩ የካሽ ሬጂስተር ማሽኖች ከ32 ቢሊየን ብር በላይ ሀሰተኛ ግብይት መፈፀሙን የገቢዎች ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡

ሚኒስቴሩ ሰሞኑን 63 ህገ-ወጥ ድርጅቶች እና ለህገ-ወጥ ዓላማ ሲውሉ የነበሩ 20 የሽያጭ መመዘገቢያ መሳሪያዎች መያዙን ይፋ ማድረጉ ይታወሳል፡፡

በሽያጭ መመዝገቢያ ማሽኖች 32 ቢሊየን 527 ሚሊየን 510 ሺሕ 503 ብር ከ5 ሳንቲም ዋጋ ያላቸው ሀሰተኛ ደረሰኞች ወይም ሀሰተኛ ግብይቶች እንደተሳራባቸው በማሽኖቹ ላይ በተደረገው ምርመራ ማረጋገጥ ተችሏል፡፡

በተያያዘ ደረሰኝ የማይቆርጡ ድርጅቶች ላይ በተደረገ ክትትል 199 ሰዎች በህግ ቁጥጥር ስር ውለው ተጠያቂ እንዲሆኑ መደረጉን ከሚኒስቴሩ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

በታክስ አስተዳደር አዋጅ 983/2008 አንቀፅ 108 ድንጋጌ መሠረት 8 ሚሊየን 150 ሺሕ ብር አስተዳደራዊ ቅጣት እንዲጣልባቸውም ተወስኗል፡፡

ኅብረተሰቡ ሀሰተኛ ደረሰኝ የሚያሰራጩና በግብይት ወቅት አጠራጣሪ ሁኔታ ሲያጋጥመው በአቅራቢያው ወደ ሚገኝ የታክስ ማዕከልና የፀጥታ አካላት በማሳወቅ ትብብር እንዲያደርግም ሚኒስቴሩ ጥሪ አቅርቧል፡፡ (ዋልታ)

Exit mobile version