Site icon ETHIO12.COM

“በቡጢ መታኝ ስወድቅ ደፈረኝ” የ80 ዓመት አዛውንት

አሁን አሁን እየተሰማ ያለው ዜና የወደፊቱን ጉዳይ ጥያቄ ውስጥ የሚከት እየሆነ ነው። በላይ በላይ እየተከታተሉ የሚወጡት መረጃዎች ግብረ መልሳቸው የወደፊቱን ጉዳይ ጥያቄ ውስጥ መክተት ብቻ ሳይሆን ወደ ድምዳሜምም እየወሰዱት ነው። አብሮ መኖር የማይቻልበት የቂምና የጸብ ሃውልት በየቀኑ እየተገነባ ነው። ይህ በአንድ ወገን ሳይሆን በሁሉም ወገን ነው። በግልጽ ቋንቋ “መሸዋወድ” ካልሆነ ይህንን ሁሉም በልቡ ያውቀዋል። ይረዳዋል። እንደውም ወስኖ ቁጭ ብሏል። ለዚህ ነው ” ብንለያይ ይሻላል” የሚሉ ድምጾች እየተሰሙ ያሉት።

” … በሶስተኛ ቀን የባለቤቴን አስከሬን ላነሳ ተፈቅዶልኝ ስሄድ ጉንዳን ወሮት …. እያለቀሱ ” ይህ ተሰምቷል። የተናገሩት ሚስት ናቸው። በሰላም በተቀመጡበት በቤታቸው ሙሉ ቤተስባቸውን ተነጠቀው ብቻቸውን የቀሩት አዛውንት ” እንዴት ልሁነው? ” እያሉ ሃዘን እየናጣቸውና ቁጭት እንደ ረመጥ አንጀታቸውን እየላጠው የሆኑትን ሲናገሩ ስምተናል። አይተናቸዋል። በየሰፈሩ አስከሬን ተቀብሯል። መኖሪያ ቤት ውስጥ ቀብር ተፈጽሟል። የጅምላ ጭፍጨፋ ተፈጽሟል። በጋሸና አስከሬን በድብረብርሃን ልብስ ተጠቅልሎ በየሜዳው ቤተስብ እያነባ አይተናል። ይህን ሁሉ ያደረገው በስም የሚታወቅ ወራሪ ሃይል ነው። እንዲህ ያለው ተግባር የትም ስፍራ፣ በማንኛወም የህብረተሰብ ክፍል ላይ ሊሆን የማይገባ ሃፍረት ነው። አሳፍሪ ብቻ ሳይሆን አውሬነት ነው።

በሸዋ ሮቢት ተደፍረው ራሳቸውን ያጠፉ እናት ዜና ለሰሚው ሃሞት የመጋት ያህል ሆኗል። ይህ ተግባር የትም ቦታ፣ በማንም ላይ ቢፈጸም ህሊና ላላቸውና “ሰው ነን” ለሚሉ ሁሉ ያማል። እኚህ እናት የየትኛውም ብሄር አባል ቢሆኑ እንደ እናት እንዲህ ላለው ክብረ ነክ እርኩስ ተግባር አይመጥኑም። በፍጹም።

የአር ቲ ዘጋቢ በደብረ ብርሃን ሆስፒታል በመገኘት የትህነግ ወራሪ ሃይል ታጣቂዎችን የአስገድዶ መድፈርና ሌሎች ዘግናኝ የሰብኣዊ መብት ጥሰቶችን መፈፀማቸውን ለዓለም ዘግባለች። ሌሎች ሚዲያዎች በሩ ተከፍቶ ኑና እውነቱን ዘግቡ ሲባሉ ” ካፈርኩ አይመስልሰኝ” ሲሉ የአርቲ ዘጋቢ በደብረብርሃን ኮምፕሬንሲቭ ሆስፒታል ተገኝታ ያቀረበችው ዘገባ ከሃዘንም በላይ የሚፈጥረው ስሜት በቃል ሊገለጽ አይችልም። ሜዲካል ዳይሬክተር ዳግም ሺመላሽ ለዘጋቢዋ እንደተናገሩት የአስገድዶ መድፈር ወንጀል ሰለባ የሆኑ 25 ሴቶችን ሆስፒታሉ ተቀብሎ ሕክምና ሰጥቷል።

ከእነዚህ ሴቶች መካከል አስሩ አሁንም ህክምና እየተከታተሉ መሆናቸውንና ከእነዚህ ውስጥም የ80 ዓመት አዛውንት ሴት እንደሚገኙ አመልክተዋል። ይህን ጊዜ ዘገባው የናዳ ያህል ለልቡና ውርጂብኝ ሆነ። ዘጋቢዋ አቅፋ ስማቸው ሪፖርቷን ስታቀርብ አይኗ ላይ የሚነበበው ሃዘን እንዴት አድራጊ ወገኖች ላይ ቅንታጥ ያህል ሊፈጠር አልቻለም? ምን አይነት የጥላቻ ስብከት? ምን ያህል አጥንት የዘለቀ የክፋትና የጭካኔ ትምሀርት ይሆን የ80 ዓመት እድሜ ባለጸጋ ላይ ዘሎ ጉብ የሚያስብል? ምን የሚሉት የአብዮታዊ ዴሞክራሲ ኪኒን ይሆን እንዲህ ልቡናና ህሊናን የሰለበው? ይህን ትውልድስ እንዴት ወደፊት ማረቅ ይቻላል?

የ80 ዓመት አዛውንቷ ለጋዜጠኛዋ የሕወሓት ታጣቂዎች እንዴት ወደቤታቸው መጥተው እንደደፈሯቸው ያስረዳል።‹‹ምሽት አራት ሰዓት ላይ መጥተው በራፌን አንኳኩ፤ የቤቴን በራፍ እንድከፍት ጠየቀኝ፤ ስከፍት በቡጢ አለኝ፤ ወደኩኝ፤ ደፈረኝ፤ መሳሪያ የያዘ አዲስ ሰው ነው፤ ምን እንደፈፀመብኝ በፍጹም አልረሳም›› አዛውንቷ የሆነውን ተናገሩ። ቀደም ሲል ለመቀረጽ ፈቃደኛ ሆነው ቃላቸውን ሲሰጡ ለጊዜው ከመደንገጥ ውጭ ምንም አማራጭ ባይኖርም፣ ይህን እንደ ኩራትና ጀግንነት ለሚያወድሱ ግን የዘላለም የሰውነት መገለቻቸውን በሙሉ በእርግማን ከመሰናበት ውጭ ሌላ አማራጭ የሚኖረው ” ሰው” ስለመኖሩ ያጠራጥራል።

ሌሎችም በየተራ እንዴት እንደተድፈሩ አስረድተዋል። ለጤና ችግር የተጋለጡበትን መንገድ አመልክተዋል። ይህ ከሆነው በአንድ የሳር ዘለላ እንደተፈናተቀ ውሃ ያህል ነው። ዘጋቢዋ አንድ ሙሉ በሙሉ የወደመ ሰፈር ውስጥ ገብታ ፍራሹ ላይ እየተራመደች ውድመቱን ከገለጸች በሁዋላ፣ ባዶ መስኮት ጋር ተጠግታ ” አውልቀው ወስደውታል” ስትል ተናግራለች። ዘገባው ገና የሚጀምር በመሆኑ ብዙ መስማታችን አይቀርም። በአማርኛ ሰምተናል።በንግሊዝኛ ይቀጥላል።


Exit mobile version