Site icon ETHIO12.COM

አብይ አሕመድና ጀነራል ሄመት “በጋራ ጥቅሞችና ፍላጎታቸውን ላይ አቋም ለመያዝ ተወያዩ

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ ከሱዳን ሉኣላዊ የሽግግር ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት ሌተናል ጄኔራል መሀመድ ሀምዳን ዳጋሎ (ሄመቲ) ጋር በሁለቱ አገሮች የጋራ ጥቅምና ፍላጎቶች ላይ መወያየታቸው ተሰማ። “ፍላጎታን ጥቅም” የተባሉ ጉዳዮች እስካሁን ይፋ አልሆኑም። የአፍሪካ ህብረት ዋና ጸሃፊም አነጋግረዋቸዋል።

በሱዳን የወታደራዊ አገዛዝ እንዲያከትም የተነሳው ሕዝባዊ ተቃውሞ እያደገና እየሰፋ በሄደበት ወቅት ለጉብኘት የመጡት የሱዳን የሽግግር መንግስት ወታደውራዊ ካውንስል ሁለተኛ ሰው፣ ከጠላይ ሚኒስትር አብይ ጋር ሲመክሩ የኢትዮጵያ ጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላና የአገር መከላከያ ሚኒስትሩን አብርሃም በላይ (ዶ/ር) መገነታቸው ተመልክቷል።

የሱዳን የዜና ኤጀንሲ ሱና እንዳለው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይና ሌተናል ጄኔራሉ በሁለቱ አገራት የሁለትዮሽ ግንኙነትና የጋራ ጥቅሞችና ፍላጎቶች ዙሪያ መወያየታቸውን አመልክቷል። ይሁን እንጂ የሱዳን መንግስት ልሳን የሆነው ሱና ዝርዝር ያስቀመጠው ነገር የለም። ባለፉት ጥቂት ሳምንታት የትህነግ ባለስልጣኖች ትግራይን ለመንግስት አስረክበው በሱዳን በኩል ወደ ሶስተኛ አገር የመውጣት አማራጭ እንዲቀርብላቸው ሃሳብ መኖሩ ከተሰማ በሁዋላ ጀነራሉ ወደ ኢትዮጵያ በድንገት መምጣታቸው ሰፊ መነጋገሪያ ሆኗል።

ኢትዮጵያና ሱዳን ከታላቁ የኢትዮጵያ ኅዳሴ ግድብና ከድንበር ጉዳይ ጋር የተያያዘ ከፍ ያለ የጋራ አጀንዳ እንዳላቸው የሚታወቅ ነው፡፡

በመከላከያ ሚኒስቴር ዋናው አዲስ ህንጻ ማምሻውን በተደረገው ውይይት የሁለቱን አገራት ወንድማማች ሕዝቦች ፍላጎት ለማሳካትና ለማላቅ ያስችላል የተባለ ወይይት መደረጉን ነው ዜናው ያብራራው። ይሁን እንጂ ” ማላቅ” ሲባል የት ድረስና ያሉት ችግሮች በተለይም ለትህነግ ሃይል ደጀን በመሆን ሱዳን እየተጫወተች ያለውን አፍራሽ ሚና በምን መልኩ ለታቆም እንደምትችል ዜናው ፍንጭ አልሰጠም።

“አዲስ አበባን በመጎብኘቴና የዚህችን ውብ አገር መሪዎች በወንድማማችነት መንፈስ በማግኘቴ ደስተኛ ነኝ። ይህም የሁለቱን አገራት ግንኙነት ጥልቀትና ጥንካሬ ያረጋግጣል” ማለታቸው አመጣጣቸው በቅድመ ውይይት በርካታ ጉዳዮች የተጠናቀቁበት መሆኑንን እንደሚያሳይ ዜናውን የምተከታተሉ ገልጸዋል።

ሱዳን በህዳሴ ግድብ ለግብጽ ተገዝታ ኢትዮጵያን መክዳቷ፣ ኢትዮጵያን እንዲያተራምሱ አማጺያንን በማስለጥንና በማስታተቅ የግብጽን ህልም ለማሳካት መስራቷ፣ ለትህነግ ሽፍቶች ከለላ ምስጠቷና ኢትዮጵያ ጦርነት ላይ መሆኗን አይታ ወረራ መፈጸሟ በኢትዮጵያ ህዝብና መንግስት ዘንዳ ሱዳን በከሃጂነት ተፈርጃ ቆይታለች። የኢትዮጵያ የመከላከያ ባለስልጣናትም ዝግጅታቸው ሱዳንን ጭምር ለማስተንፈስ እንደሆነ ሲናገሩ መቆየታቸው ይታወሳል።

በተመሳሳይ ዜና ጀነራሉ ከአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ሙሳ ፋኪ ማህመት ጋር ‹‹በሱዳን አስጨናቂ ሁኔታዎች ዙሪያ›› ተነጋግረዋል።የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ሙሳ ፋኪ ማህመት ከሱዳን ሉኣላዊ የሽግግር ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት ጄኔራል መሀመድ ሀምዳን ዳጋሎ (ሄመቲ) መወያየታቸውን ያስታወቁት በቲውተር ገጻቸው ነው።

ሱዳን በሉኣላዊ የሽግግር ምክር ቤቱ ሊቀ መንበር (ፕሬዝዳንት) ጄኔራል አብዱልፋታህ አልቡርሃን የሚመራው ወታደራዊ ክንፍ መፈንቅለ መንግሥት በማድረግ የሲቪል አስተዳደሩን ማስወገዱን ተከትሎ አገሪቱ ወደ ቀውስ ልትገባ እንደቻለች ይታወሳል።

ለ3 ዓመት ቆይታ እንዲኖረው ታስቦ የነበረው የሽግግር መንግሥቱ ሲመሰረት የመጀመሪያውን ምዕራፍ ወታደራዊ ክንፉ በበላይነት እንዲመራና ባሳለፍነው ኅዳር 2014 ለሲቪል አስተዳደሩ ለቆ አገሪቱ ለምርጫ እንድትዘጋጅ ማድረግ የሚል ስምምነት ነበረው፡፡

ሆኖም በጄኔራል አልቡርሃን የሚመራው ወታደራዊ ክንፉ ሥልጣን በማስረከቢያው ዋዜማ መፈንቅለ መንግሥት በመፈፀም አገሪቱን ወደ አለመረጋጋት፤ ሕዝቡንም ወደ ከፍተኛ ተቃውሞ አስገብቶት ይገኛል፡፡ በዚህም ሱዳናዊያን የወታደሩን ድርጊት በመቃወም ዛሬም በአደባባይ የሲቪል አስተዳደር ምስረታን እየጠየቁ ይገኛሉ፡፡

Exit mobile version