Site icon ETHIO12.COM

 “ምዕራባዊያን ብቻችንን አጋፍጠውናል”ዩክሬን – ከሩሲያ ጋር ለመደራደር ዝግጁ ናቸው – ሩሲያም ፈቃዷን ዘግይታ አሳይታለች

“እንደሚደግፉን ነበር ቃል ሲገቡልን የነበሩት፤ ሆኖም ሞትን እንድንጋፈጥ ብቻችንን ትተውናል

ብቻችንን አጋፍጠውናል። አገራችንን ለመጠበቅ በብቸኝነት እየተዋጋን ያለነውም እኛው ብቻ ነን”

ፕሬዝዳንቱ የሩሲያ ኮማንዶዎች ሊይዟቸው እንደሚችሉ ሲጠቁሙም ሞስኮ ቁጥር አንድ ዒላማ አድርጋኛለች

የዩክሬን ፕሬዝዳንት ቮሎድሚር ዘለንስኪ ስለ አሜሪካ መሩ የምዕራባዊያን ጎራ ሲናገሩ “ብቻችንን አጋፍጠውናል። አገራችንን ለመጠበቅ በብቸኝነት እየተዋጋን ያለነውም እኛው ብቻ ነን” ሲሉ ወቅሰዋል፡፡

የዩክሬኑ ፕሬዝዳንት ዛሬ ለ27 የአውሮፓ አገራት መሪዎች አገራቸው በሰሜን አትላንቲክ ጦር ቃል ኪዳን ድርጅት (ኔቶ) ስር እንድትታቀፍ ጥያቄ ቢያቀርቡም ማንም ምላሽ እንዳልሰጣቸው አሳውቀዋል። “ሁሉም ፈርቷል” ሲሉም አሜሪካን ጨምሮ ከዚህ ቀደም አይዟችሁ በማለት ዩክሬን ከሩሲያ ጋር ውጥረትና ጦርነት ውስጥ እንድትገባ ሲገፋፉ የነበሩ ሁሉ ፊታቸውን ማዞራቸውን በምሬት ስለመግለፃቸው ሲጂቲኤን ዘግቧል።

ዓለም ዐቀፉ ማኅበረሰብ የሚባለው አካል ዩክሬንን እንደተዋት የገለጹት ፕሬዝዳንቱ “እንደሚደግፉን ነበር ቃል ሲገቡልን የነበሩት፤ ሆኖም ሞትን እንድንጋፈጥ ብቻችንን ትተውናል” ሲሉ ተደምጠዋል።

የሩሲያን ጦር ኃያልነት የተረዱት ፕሬዝዳንት ዘለንስኪ ዩክሬን ከሩሲያ ጋር ለመደራደር ዝግጁ መሆኗን ገልፀው መነሻቸው ግን ፍርሃት አለመሆኑን ደግሞ አክለዋል። እኛ አንፈራም ሲሉም አክለዋል።

ፕሬዝዳንቱ የሩሲያ ኮማንዶዎች ሊይዟቸው እንደሚችሉ ሲጠቁሙም ሞስኮ ቁጥር አንድ ዒላማ አድርጋኛለች ሲሉ መግለፃቸውን አልጀዚራ ጽፏል።

የሩሲያ ጦር ትናንት ብቻ የተለያዩ 74 የዩክሬን ጦር ወታደራዊ ስፍራዎች ማውደሙን ሲገልፅ ዛሬ ዋና ከተማዋን ኬይቭ እንደተቆጣጠረ መርጃዎች እየወጡ ይገኛሉ።

ይህንንም ተከትሎ የዩክሬን መከላከያ ኃይል ማንኛውም ዜጋ እንዲዋጋ በትዊተር ገጹ ጥሪ አቅርቧል ሲል ቢቢሲ ዘግቧል።

የወታደሮቹ አዛዥ መግለጫ በዚህ ውጊያ “የእድሜ ገደቦች የሉም” ብሏል- ይህም ለአካለ መጠን ያልደረሱ ልጆችም ትግሉን እንዲቀላቀሉ ሊፈቀድ እንደሚችል ያሳያል ተብሏል።

የዩክሬን ጦር የሩሲያን ጉዞ ለመግታት በሚል ድልድዮችን ጨምሮ ግዙፍ የመሰረተ ልማት አውታሮችን ሲያፈርስ የነበረ ቢሆንም መግታት አልቻለም፡፡

በመጨረሻ የወጡ መረጃዎች እንደሚያሳዩት ሩሲያ ለመደራደር ፈቃደኛ መሆኗን አሳይታለች። ተደራዳሪ ቡድንም ወደ ቤላሩስ እንደምትልክ አስታውቃለች። ድርድሩ ቀላል እንዲሆን ወታደሩ የመንግስትን ስልጣን እንዲተካ ፑቲን መክረዋል። ፑቲን አገራቸው ለመደራደር ዝግጁ መሆኗን ያስታወቁት የዩክሬን አቻቸው የመነጋገውር ፍላጎት እንዳላቸው በአደባባይ መግለጻቸውን ተከትሎ ነው። ሁለቱም ወገኖች የመደራደር ፍላጎት ቢያሳዩም የሩሲያ ሰራዊት ወደፊት መግፋቱን አልገታም።

Exit mobile version