Site icon ETHIO12.COM

ጣልቃ ከገባ የኮሚሽኑ ሰብሳቢ ስራቸውን እንደሚለቁ ራሱ መንግስት አስታወቀ፤ የመንግስትን ዜና ገልብጦ ሟርት!!

በተለይም ዛሬ የምርመራ ጋዜጠናነት መፈቀዱ፣ እያንዳንዱ ተቋም፣ ሃላፊ፣ አመራር፣ ቦርድ … እንደሚበረበር በይፋ በተነገረበት፣ ሲሽሞነሞን የነበረው ዝርፊያ እየተራከሰ ባለበት በአሁኑ ወቅት ለአገር የሚጠቅም፣ ለትውልድ የሚበጅ የምርመራ ስራ ሰርቶ ታሪክ ማስቀመጥ እየተቻለ፣ በማህበራዊ ሚዲያ መንግስት ራሱ ይፋ ባደረገውና በሚያደርገው ጉዳይ ላይ ማተኮሩ እንደ ሚዲያም አያስከብርም። አቅሙ ባለበት፣ መድረኩ በተዘጋጅበት፣ መረጃው ሰፊ በሆነበት ጊዜ ታላላቅ ስራዎችን መስራት እንጂ ማህበራዊ ሚዲያ ውስጥ ዜና መልቀም ብዙም ሊበረታታ አይገባም።

የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን የስራ መጀመሪያ ትውውቅ ፕሮግራም ማካሄዱን ጠቅሶ በምክር ቤቱ የማህበራዊ ገጽ ” የአስፈፃሚው አካል ወይም የመንግሥት ጣልቃ-ገብነት እንደማይኖር እምነታቸው መሆኑን ጠቁመው በኮሚሽኑ አሰራር ውስጥ የመንግሥት ጣልቃ ገብነት የሚኖር ከሆነ ግን ኃላፊነታቸውን በፈቃዳቸው እንደሚለቁ አሳስበዋል” ሲል ዜናውን አስፍሯል።

የኮሚሽኑ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መስፍን አርኣያ ከኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ጋር ባደረጉት ቆይታ በቀሪው ዕድሜያቸው ለአገራቸው ታላቅ ስራ ለመስራት፣ አብቶች ጥንት እንዳደረጉት ሁሉ እሳቸው የሚመሩት ኮሚሽን የሚችለውን ሁሉ አድርጎ አንድ ታሪክ የማስቀመጥ ራዕይ እንዳላቸው ነው።

የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን አባል ሆነው እንዲሰሩ ኃላፊነት የሰጣቸው ሕዝቡ በመሆኑ ሙሉ ጊዜያቸውን ሰጥተው በኃላፊነት መንፈስ ለመስራት ዝግጁ መሆናቸውንና ከሚዲያውና ሌሎች አካላት ጋር በጋራ እንደሚሰሩ ፕሮፌሰሩ ቢያስታውቁም፣ ራሱ መንግስት የጻፈውና ያሰራጨው ዜና ኮሚሽኑንን ” እንደሚለቁ አሳሰቡ” በሚል ተገልብጦ ቀርቧል። ይህን ታላቅ ረዕይና ተስፋ ያነገበ ኮሚሽን ተስፋ በሚሞሉ መሪ ቃላቶች ማነቃቃትና ማስተዋወቅ ሲገባ መበተኑ እንዲቀድም የሚፈለግበት ምክንያት ምንድን ነው?

ዛሬ ትግራይ ፈርሳለች። ሕዝቡ መከራ ውስጥ ነው። እናቶች፣ አባቶች፣ ህጻናት፣ ወጣቶች በጥቅሉ በትግራይ ያሉበት ሁኔታ ያሳዝናል። ያማል። “እስከመቼ” የሚል ጥያቄ ያስነሳል። በአማራ ክልል እገር፣ ተቋማት፣ ህዝብ፣ ሃብቱ፣ ማንነቱ፣ ሞራሉ ተምቷል። ተገድሏል። በአፋር በተመሳሳይ ሃፍረት እየተፈጸመ፣ ሕዝብ እየተገደለና እየተሰቃየ ነው። በኦሮሚያ ንጹሃን ይገደላሉ፣ በማንነታቸው ይፈናቀላሉ። ይህ ሁሉ ያበቃ ዘንድ በመመኘት በመጥፎ ጉዳይ ውስጥ መልካሙን መፈለግ ሲገባ ከብረሃን ውስጥ ጥቀርሻ መርጦ መርጨት በየትኛው መስፈርት ትክክል ይሆን ይሁን? እስኪ ወደ ሁዋላ እንመለስ።

በኢትዮጵያ የነጻ ሚዲያ ታሪክ “ገለልተኛ” የሚለው እሳቤ አያግባባም። ቀደም ሲል መጠኑን በመቶኛ አስልቶ መናገር ባይቻልም፣ አንድም በተቃዋሚዎች፣ አለያም በመንግስት መደጎምና መደገፍ መረጃ መቀበል ገሃድ የወጣ እውነት ስለመሆኑ መከራከር የሚችል አካል አይኖርም። ካለም በዘመኑ ቋንቋ “ባለበት የተቸከለ” ነው። ይህ ሲባል ግን ገለልተኛ ለመሆን የሚጥሩ፣ ድጋፋቸውን ረቀቅ ባለ መልኩ የሚያደርጉና የችግር ጊዜ ካልሆነ በቀር ሚዛናዊ የሚባሉ አይጠፉም ማለት አይደለም። ይህ አይነቱ አካሄድ በውጭው ዓለምም የተለመደ ነው።

በግሌ ለ1997 ምርጫ መኮላሸትና በዜሮ መባዛት በወቅቱ የተፈለፈሉ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች አፍ ብቻ የሆኑ፣ አንዳንዴም አቅጣጫና መመሪያ ለመስጠት የሚቃጣቸውና “ዋ” እያሉ ሲያስፈራሩ የነበሩ ሚዲያዎችና ባለቤቶቻቸው ቅድሚያ ረድፍ ይይዛሉ። በውቅቱ ትህነግ የሚመራው መንግስት የሕዝብን ድምጽ ሰርቆ፣ የተሰረቀ ሕዝብ ድምጽ ሲያሰማ ጠብ መንጃ መርጦ ነጹሃንን መግደሉ የዘመኑ ጥቁር ታሪክ ቢሆንም፣ ፖለቲካውን ከማርጋትና የረጋ አሳብ ከማካፍለ አንጻር የሚዲያዎች ተሳትፎ ቢሰላ ምንም ነው ለማለት የሚያስችል ነበር። የመንግስት ሚዲያዎችም በዚያኛው ወገን እንደዛው።

ከሁለት አስርት ዓመታት በሁዋላ የተፈጠረውን የለውጥ ቱርፋት ተንተርሶ በብዛት የፈላውና የራሱ ፍላጎት ያለው የሚዲያ ጋጋታ በአብዛኛው የለውጡን ዕድል እየበላው ነው። ከመልካም አሳብ ውስጥ መጥፎን በመንቀስና ከጉዳዩ አውድ ጋር በማይገናኝ መልኩ ለክፉ አካሄድ መጠቀም፣ ይህንኑ ክፉ አካሄድ በማሰራጨትና በማራባት መሸጥና ሕዝብ ግራ እንዲጋባ ማድረግ በአብዛኛው የሚዲያዎቹ ስራና ዓላማ ነው።

በተቃራኒው ዕድሉን በተስፋ በማጀብ መጪውን ጊዜ የተሻለ ለማድረግ በማሰብ ለትውልድ የሚሰሩ፣ በያሉበት የአገራቸው አምባሳደር የሆኑ፣ በሁሉም አቅጣጫ የአገርና የፓርቲን ፍላጎት ለይተው ለመስራት የሚታትሩ ” መልከ ግቡ” ሚዲያዎች መኖራቸው ጥርጥር የለውም። መንግስትን በወጉ እስኪያስነጥሰው ድረስ የሚቀጠቅጡ ሚዲያዎች አስፈላጊ ከመሆናቸው አንጻር በዚህ በበጎ ጅማሬ የተነሱትን ማገዝና ማበረታት አስፈላጊ ቢሆንም፣ ዛሬ ላይ እንደሚታየው ምናምንቴና ቅራቅንቦ የሞት፣ የመለያየት፣ የጥፋት ስብከት ለሚያሰሙት ሚዲያዎች አሸርጋጁና እርጥባን ሰጪው አይሎ መታየቱ ያስገርማል። ያሳዝናል። ያበሳጫልም።

ይህን ካልኩ ወደ ዋናው ጉዳዬ ልግባ። የብሔራዊ ምክክር ኮሚሽን ከተመሰረት ገና በሁለተኛው ቀኑ ሰብሳቢውን ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያን በመጥቀስ በግንባር ዜናነት የ”መበተኑ” ዜና ወይም ” እንለቃለን አሉ” የሚል ዜና ተሰምቷል። ይህ ከብረሃን ውስጥ ጨለማን የመመኘት ዝንባሌን የሚያመላክት ሟርት ነው። መቋቋሙ በውል ያልተሰማውን ተቋም፣ “እንለቃለን አሉ” የሚል ስም ማጎናጸፍ ሟርት ብቻ ሳይሆን ሃላፊውን መጫንም ነው።

ቀን በቀን በመሳደብ፣ የሁሉም ነገር አዋቂ በመሆን ሲተፉ የሚውሉና የሚያመሹ፣ ዕርግማንና ሟርት ስራቸውና ቀለባቸው የሆኑትን ለተከታዮቻቸው በመተው፣ ሌሎች ግን ይህን ኮሚሽን በማገዝ አገሪቱ ከገባችበት ቅርቃር እንድትወጣ የበኩላቸውን ማድረግ ይገባቸዋል።

በተከማቸው ቁስል ላይ ህክምና በማካሄድ፣ የኢትዮጵያን ነገ ለመስራት አስፈላጊውን ሁሉ ለማድረግ ወደ ሁዋላ እንደማይል ያስታወቀውን መንግስት አንገቱን አንቆ ቃሉን እንዲጠብቅ ማሳሳሰብ፣ ማስጠንቀቅና ይህ ዓይነቱ አግባብ ይበልጥ መቀራረብ እንዲፈጥር፣ የመንግስት ሃይሎች ተራ የቀበሌ ነዋሪ ሆነው መኖር እንደሚችሉ በማሳየት መስራት ከሚዲያው ይጠበቃል።

በተለይም ዛሬ የምርመራ ጋዜጠናነት መፈቀዱ፣ እያንዳንዱ ተቋም፣ ሃላፊ፣ አመራር፣ ቦርድ … እንደሚበረበር በይፋ በተነገረበት፣ ሲሽሞነሞን የነበረው ዝርፊያ እየተራከሰ ባለበት በአሁኑ ወቅት ለአገር የሚጠቅም፣ ለትውልድ የሚበጅ የምርመራ ስራ ሰርቶ ታሪክ ማስቀመጥ እየተቻለ፣ በማህበራዊ ሚዲያ መንግስት ራሱ ይፋ ባደረገውና በሚያደርገው ጉዳይ ላይ ማተኮሩ እንደ ሚዲያም አያስከብርም። አቅሙ ባለበት፣ መድረኩ በተዘጋጅበት፣ መረጃው ሰፊ በሆነበት ጊዜ ታላላቅ ስራዎችን መስራት እንጂ ማህበራዊ ሚዲያ ውስጥ ዜና መልቀም ብዙም ሊበረታታ አይገባም።

የኮሚሽኑ ሰብሳቢ የአእምሮ የተዋጣላቸው ሃኪም ናቸው። አብዛኛው የአገሪቱ ችግር ከአስተሳሰብ ሕመም የመነጨ ነው ተብሎ ስለሚያሰብ፣ ምርጫውን አለማድነቅ በራሱ መበደል ነው። እንደ እውነቱ ቢሆን ኖሮ እሳቸው ለምን አስፈለጉ? የሚለውና ራሳቸው ከሙያቸው አንጻር ኮሚሽኑንን እንዴት እንደሚያስኬዱት፣ ምን አጠቃላይ እይታ እንዳላቸው ለማወቅ መጓጓት በቀደመ ነበር።

ፎቶ – ሱዳን የተሰደዱ ወገኖች

Exit mobile version