ETHIO12.COM

“ሩሲያ ዩክሬይንን ወረረች?”

እኤአ በፌብሩዋሪ 2014 በ ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ወደ ሥልጣን የመጣውንና ምርጫው “ደህንነትና ትብብር ድርጅት” (OSCE Organization for Security and Cooperation) በተሰኘው ዓለምአቀፋዊ ድርጅት የጸደቀው የዩክሬን መንግሥት በመፈንቅለ መንግሥት ተወገደ። ፕሬዚዳንቱ ቪክቶር ያኑኮቪች ሕይወታቸውን ለማዳን ከአገር ለቅቀው ወጡ።

መፈንቅለ መንግሥቱ የተቀነባበረው በተለይ በአሜሪካ ባልሥልጣናት ነው። ትውልደ ዩክሬን የሆነችውና በወቅቱ በአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የአውሮጳና ዩሬዢያ ረዳት ጸሐፊ የነበረችው ቪክቶሪያ ኑላንድ የሤራው ዋና አቀናባሪ ነበረች። አብሯት ሟቹ ሴናተር ጆን ማኬይን ሠርቷል። ፕሬዚዳንት ያኑኮቪችን ከሥልጣን ለማስወገድ ቪክቶሪያ ራሷ ከማስተባበር ባለፈ ሰላማዊ ሰልፍ የሚወጡትን ዩክሬናውያንን ከመደገፍ አልፋ ለሰልፈኞች ብስኩት ስታድል በወቅቱ ተዘግቧል። ይህንን ባደረገች ቀን ለዩክሬይን ባለሃብቶች አሜሪካ ለዚህ ፕሮጀክት አምስት ቢሊዮን ዶላር መድባለች፤ አይዟችሁ፤ የአውሮጳ ኅብረት የዩክሬይንን ወደ ኅብረቱ እንድትገባ አለመወሰኑና በጉዳዩ ላይ ለዘብተኛ አቋም በመያዙ “fuck the EU” በማለት መናገሯም በወቅቱ የተዘገበ ነበር።   

በወቅቱ በምሥጢር በተቀዳ የስልክ ንግ ግር እንደታወቀው ቪክቶሪያ ከመፈንቅለ መንግሥቱ በኋላ ስለሚመሠረተው መንግሥት እና እነማንን ማካተት እንዳለበት አስቀድሞ የተሠራ መሆኑን ስትናገር የነበረ ሲሆን ባለፉት ሁለት ዐሥርተ ዓመታት ለዚሁ ዘመቻ አምስት ቢሊዮን ዶላር ተመድቦ ሲሠራበት እንደነበር ተናግራለች። ቪክቶሪያ መፈንቅለ መንግሥቱን ስታቀነባብር በወቅቱ የአሜሪካ ምክትል ፕሬዚዳንት የነበረው ጆ ባይደን በበላይነት ፕሮጀክቱን ይመራ ነበር። የባይደን ልጅ ደግሞ ከዩክሬይን ከሚገኘው የንግድና ኢንቨስትመንት ሥራ ቀጥተኛ ተጠቃሚ ነበር።

የቪክቶሪያ ባል ሮበርት ኬገን በዋንኛነት “አዲሱ አክራሪዎች” (neocon) የሚባሉትና በየአገሩ የአገዛዝ ለውጥ “regime change” እንዲደረግ ከሚያሤሩ የአሜሪካ ዋንኛ ሰዎች መካከል በቀዳሚነት የሚጠቀስ ነው። የቀድሞውን ፕሬዚዳንት ቡሽ ወደ ኢራቅ ጦር እንዲያዘምትና የአገዛዝ ለውጥ እንዲያደርግ ሲመክርና ሲያገባባ የነበረ ሰው ነው።

የሩሲያ ወዳጅነት የነበራቸውና በዴሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጡት ያኑኮቪችን ከሥልጣን ማስወገድ የአሜሪካና የቪክቶሪያ ዋንኛ ሥራ ሆኖ ቀጥሎ መፈንቅለ መንግሥቱ እየተፋፋመ ሲመጣ ያኑኮቪች የአውሮጳ ኅብረት ዋስትና የሰጠው ዕቅድ እንዲወጣ፣ እርሳቸውም ከሥልጣናቸው ብዙውን ሊቀንሱ፣ እንዲሁም ሌላ ምርጫ በቅርብ እንዲደረግና በምርጫ ከሥልጣን ለመልቀቅ ቢስማሙም ለአሜሪካ፣ ለቪክቶሪያና ለተሰኘውና በአሜሪካ ለሚደገፈው የዩክሬይን አክራሪ ቡድን እና ለኒዮናዚ ሚሊሺያዎቹ አጥጋቢ አልሆነላቸውም። ያኑኮቪችን ካላስወገዱ በምንም እንደማይስማሙ በመናገር አማጺያኑ የመነገሥትን ሕንጻ በወረሩበት ጊዜ ፕሬዚዳንት ያኑኮቪች እና ባለሥልጣኖቻቸው ሕይወታቸውን ለማዳን አመለጡ፤ ያኑኮቪች አሁን በሩሲያ ይገኛሉ።  

ሕጋዊው ፕሬዚዳንት ያኑኮቪች በሕገወጥ መንገድ ልክ እንደ ግብጹ ሙርሲ ከሥልጣን ከተወገዱ በኋላ በመፈንቅለ መንግሥት ሥልጣን የያዘው ቡድን ከአጠቃላዩ ሕዝብ 30% የሚሆኑት ራሺያና ተናጋሪ ዩክሬናውያን ላይ መድልዖ ማድረስ ጀመረ። ራሺያኛ ቋንቋ የዩክሬይን ኦፊሺያል ቋንቋ መሆኑን አስቀረ፤ በሕዝብ መካከል መቃቃር ከማስከተል አልፎ ጠላትነትን አስፋፋ። “Crimes of the Euromaidan Nazis” በሚለው ዘጋቢ ፊል በግልጽ እንደተዘገበው ወደ ክሬሚያ ሲጓዙ የነበሩ አውቶቡሶች ጥቃት ተፈጸመባቸው። ኦዴሳ በተባለችው ከተማ የሚኖሩና የመፈንቅለ መንግሥቱ ተቃዋሚ የነበሩ 30 ሰዎች ተገደሉ።

በሁለተኛ የዓለም ጦርነት ወቅት ጀርመን የዚያን ጊዜውን ሶቪየት ኅብረት በወረረ ጊዜ በምዕራብ ዩክሬይን የሚገኙ በርካታ የናዚ ደጋፊዎች ነበሩ። እነዚሁ ወገኖች ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ተጠናክረው መጥተው ስቮቦዳ (Svoboda) ወይም ነጻነት የተሰኘ እና ሌሎች ቀኝ አክራሪ ጽንፈኛ ፓርቲዎችን መሥርተዋል። የዩክሬይን መንግሥት እነዚህን የናዚ ደጋፊዎችን ከማጀገን አልፎ የጸረ ናዚ አቋም ይዘው ሲታገሉ የነበሩ ሰዎችን ሃውልቶች የሚያስወግድ ሕግ እስከማውጣት ደርሶ ነበር። ይህንን ተግባርና የሁኔታውን መቀጠል የሚያስከትለውን ችግር አስመልክቶ ከ4 ዓመት በፊት “Neo-nazis and the far right are on the march in Ukraine” በሚል ርዕስ በወጣው መጣጥፍ ላይ የሰማው ባይኖርም አሜሪካ ይህንን ዓይነቱን ተግባር ለምንድነው የምትደግፈው ሲል ጸሃፊው ሞግቶ ነበር።

የክሬሚያ፣ የዶኔትስክና የሉሃንስክ መገንጠል የዛሬ ሰባት ዓመት እኤአ በ2014 የተካሄደው መፈንቅለ መንግሥት ውጤት ነው።  በክሬሚያ በፍጥነት በተደረገው ሕዝበ ውሳኔ 83 በመቶ ሕዝብ ወጥቶ ድምጹን የሰጠ ሲሆን 97 በመቶው ክሬሚያ ከዩክሬይን እንድትገነጠልና ከሩሲያ ጋር ዳግም እንድትዋኻድ የድጋፍ ድምጽ የሰጠ ነበር። ከ1783 ጀምሮ ክሬሚያ የሩሲያ አካል የነበረች ሲሆን በ1954 የክሬሚያ አስተዳደር በዩክሬይን ሥር እንዲሆን ሲደረግ ያኔ ሁሉም በሶቪየት ኅብረት ሥር ነበሩ። ይህ የተደረገው ግን ሕዝቡ ሳይማከር ነበር። 

ሉሃንስክና ዶኔትስክ ከሩሲያ በድንበር የሚዋሰኑ ሲሆን አብዛኛው ሕዝብ የሩሲያ ቋንቋ ተናጋሪ ነው፤ ለሩሲያም ምንም ዓይነት ጥላቻ የላቸውም። የዛሬ ሰባት ዓመት በተካሄደው መፈንቅለ መንግሥት ሥልጣን የያዘው አገዛዝ ከእነርሱ ጋር ጠላትነት ውስጥ የገባ ሲሆን እነርሱም የአገዛዙን ፖሊሲዎች አጥብቀው ይቃወሙ ነበር። ከመፈንቅሉ በኋላም በ2014 እነርሱም የሉሃንስክ ሕዝብ ሪፑብሊክ እና የዶኔትስክ ሕዝብ ሪፑብሊክ ብለው ራሳቸውን በመጥራት በኪየቭ ከሚገኘው አገዛዝ ራሳቸውን ነጻ አወጡ።

የሚንስክ ስምምነት ተብሎ በሚጠራው በ2014 እና በ2015 የዩክሬይን መንግሥት፣ የዩክሬይን አማጺዎች፣ ሩሲያና የአውሮጳ ኅብረት ስምምነት ፈርመው ነበር። የስምምነቱ ዋና ዓላማ በምስራቃዊ የዩክሬይን ግዛት በዶኔት ስክና በሉሃንስክ ደም መፋሰስ እንዲቆም ማድረግ ሲሆን የዩክሬይንን ግዛት አስጠብቆ ሁለቱ ግዛቶች በራስገዝነት እንዲተዳደሩ ነጻነት የሚሰጥ ነበር። ይህ ያልተለመደ ተግባር አልነበረም፤ በአውሮጳ 17 ተመሳሳይ ራስገዝ ዞኖች አሉ። ሆኖም አሜሪካና የዩክሬይን መንግሥት ወሳኔውን ውድቅ በማድረጋቸው ሩሲያ ባለፈው ወር (2022) ለሁለቱ ግዛቶች እንደ አገር ዕውቅና ሰጥታቸዋለች።

በዓለምአቀፍ ሕግ መሥረት መገንጠል ሕገወጥ ተግባር ነው። ሆኖም አሜሪካና ኔቶ ይህንን የመቃወም የሞራል ልዕልና የላቸውም። ምክንያቱም ዩጎዝላቪያ እንድትበታተን፣ ኮሶቮ ከሰርቢያ እንድትገነጠል፣ ደቡብ ሱዳን ከሱዳን እንዲገነጠል እንዲሁም በኢራቅና ሶሪያ የኩርድ ተገንጣዮችን በኢትዮጵያም አገራችን የትግራይ ሕዝብ ተገንጣይ ድርጅትን ሲደግፉ የኖሩ ናቸው። በመሆኑም በአሁኑ የዩክሬይን ጦርነት ቀጥተኛ ተሳታፊዎች ናቸው።

በዚህም ምክንያት፦ በሊቢያ 14,500 ሰዎች ሞተዋል። በአፍጋኒስታን 165,000 ሰዎች ሞተዋል። በሶሪያ 224,000 ሰዎች ሞተዋል። በኢራቅ 1,200,000 ሰዎች ሞተዋል። እነዚህ ሁሉ እልቂቶች ማንንም አላስደነገጡም። እነዚህን ሁሉ ጥፋት ባደረሱ አገሮች ላይ በአንዳቸውም ማዕቀብ አልተጣለባቸውም።

በመሆኑም ሩሲያን ለማንበርከክ በአሁኑ ጊዜ ምዕራባውያን በዚህ መልኩ ነው የተረባረቡበት ያሉት። 

1. የአውሮፓ ህብረት የዩሮ የባንክ ኖቶች ወደ ሩሲያ እንዳይተላለፉ ማገዱን አስታወቀ።

2. Sputnik: አፕል በሩሲያ ውስጥ ባለው ኦፊሴላዊ ገፁ ላይ ሁሉንም ምርቶች ሽያጭ አቁሟል።

3. ዓለም አቀፉ የራግቢ ፌዴሬሽን … ሩሲያ እና ቤላሩስ ከአባልነት በፌዴሬሽኑ ውስጥ እንዲታገዱ ወሰነ ።

4. ካናዳ ድፍድፍ ነዳጅ ከሩሲያ እንዳይመጣ እንከለክላለን አለች።

5. የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ከሩሲያው “ጋዝፕሮም” ጋር የነበረውን የ40 ሚሊየን ዩሮ የስፖንሰር ሺፕ ስምምነትን ሰረዘ።

6. የአለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ስራ አስፈፃሚ ቦርድ የሩሲያ እና የቤላሩስ አትሌቶች በአለም አቀፍ ውድድሮች ላይ እንዳይሳተፉ ለማገድ እየመከሩ ነው።

7. ስዊዘርላንድ በሩሲያ ላይ የገንዘብ ማዕቀብ መጣል እና ጉምቱ ግለሰቦች ኩባንያዎቻቸው ንብረት አገደች።

8. ጉግል፡ የ”ጉግል ካርታ” አገልግሎት በዩክሬን በማገድ ራሺያ እንዳትጠቀም አደረገች።

9. ብሪታንያ የሩሲያ መርከቦችን በብሪቲሽ ወደቦች እንዳይቆሙ አገደች።

10. FIFA የሩሲያ ቡድኖች በሚጫወቱበት በማንኛውም ጨዋታ ላይ የሩሲያ ባንዲራ እና የሩሲያ ብሔራዊ መዝሙር መጠቀምን ከለከለ።

11. FIFA: የፊፋ [ዓለም አቀፍ የእግር ኳስ ማህበር] ጽሕፈት ቤት በሩሲያ ምንም ዓይነት ዓለም አቀፍ ውድድር እንዳይካሄድ በሙሉ ድምፅ ወስኗል።

12. The Wall Street Journal: FedEx እና UPS በዩክሬን ጦርነት ምክንያት ወደ ሩሲያ የሚላኩ ምርቶችን አቆሙ።

13. AFP: የዓለም ባንክ በሩሲያ እና በቤላሩስ የሚያደርጋቸውን ፕሮጀክቶች በሙሉ አገደ።

14. የሩሲያ ድመቶች በዓለም አቀፍ ትርዒቶች እንዳይቀርቡ ታገዱ ። ክልከላው በሩሲያ የተዳቀሉ የድመት ዝርያዎችን ጭምር ያካትታል ተብሏል። ሩሲያ ዩክሬንን “ወራለች” በሚል ነው በትርዒቶቹ ድመቶቹ እንዳይሳተፉ ያገደው።

እነዚህ በጣም ጥቂቶቹ ናቸው፤ በግለሰብ ደረጃ ሩሲያውያን ከዓለም አገራት መድልዖና መገለል እየደረሰባቸው ነው። ለምሳሌ ያህል በርሊንን የሙኒክ ሲምፎኒክ ኦርኬስትራ ሥመጥሩውን መሪ (ኮንዳክተር) ሩሲያዊዩን ቫለሪ ገርጊዬቭን የፑቲን ወዳጅ ነህ ብሎ አባርሮታል።

አሁን የምዕራቡ ዓለም አለንልሽ የሚላት ዩክሬይን ውስጥ ምን ይካሄድ እንደነበር ከጦርነቱ በፊት ቢቢሲ የዘገበው መረጃ ይህንን ይመስል ነበር።https://www.goolgule.com/wp-content/uploads/2022/03/Ukraine-by-BBC.mp4

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ

Exit mobile version