ዓለም ባንክና የዓለም ዓቀፉ የገንዘብ ተቋም ኢትዮጵያ የጠቀችውን ብድር ለመፍቀድ ያቀረቡት ዋና ቅድመ ሁኔታ የብርን የመግዛት አቅም ዝቅ ማድረግ ወይም በነጮቹ አፍ ዲቫሉዌት ማድረግ እንደነበር ሲጂቲኤን የተሰኘው የቻይና ሚዲያ በአዲስ አበባ ሪፖርተሩ አማካይነት አስታውቋል። ዛሬ ላይ የብር የመግዛት አቅምን ዝቅ ማድረግ ይጠቅማል? ለሚለው ባለሙያዎችም አስተያየት እየሰጡ ነው።
በቀረበው ጥያቄው መንግስት ባለመስማማቱ በአዲስ አበባ ከሁለት ሳምንት በፊት ሲካሄድ የነበረው ውይይት ቀጣይ ክፍል በአሜሪካ እንደሚካሂድ በወቅቱ በተሰራጨው ዘገባው ተመልክቶ ነበር። የሲጂቲኤን ዘገባ እንዳለው ኢትዮጵያ የጀመረቻቸው ታላላቅ ፕሮጀክቶች እየተገባደዱ በመሆናቸው በቀጣዩ ዓመት ኢኮኖሚው እንደሚረጋጋ ምልክቶች መኖራቸውንም አመልክቷል። ኢትዮጵያ ለአይ ኤም ኤፍ ያቀርበችው የብድር ጥያቄ 3.5 ቢሊዮን ዶላር እንደሆነም ገልጿል።
አይ ኤም ኤፍ ውይይቱን አድንቆ፣ ኢትዮጵያ የጀመረችውን አዲስ የኢኮኖሚ ሪፎርም ለማገዝ ተስፋ ሰጪ ውይይት መካሄዱን፣ ውይይቱም በተቆረጠለት ቀን ቀጥሎ እንደሚካሂሄድ ጠቅሶ በድረገጹ ካሰፈረው አሳብ ውጪ ስለምንዛሬ መቀነስም ይሁን ሌሎች ዝርዝር ጉዳዮች የሰጠው መረጃም ሆነ ፍንጭ የለም።
በቀጠሮው መሰረት በገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ የተመራው ልዑካን ቡድን ከዓለም ባንክ እና ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት ከፍተኛ ሃላፊዎች ጋር ውይይት ውይይት መጀመራቸውን የመንግስትና ሌሎች ዓለም ዓቀፍ ሚዲያዎች ድርጅቱን ጠቅሰው አስታወቀዋል።
ልዑኩ ከገንዘብ ሚኒስትሩ አሕመድ ሽዴ በተጨማሪ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ማሞ ምህረቱን፣ የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) እና ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ሃላፊዎችን እንዳካተተ የመንግስት መገናኛዎች ገልጸዋል።
የልዑካን ቡድኑ ከዓለም ዓቀፉ የገንዘብ ድርጅት ማኔጂንግ ዳይሬክተር ክርስታሊና ጂኦርጄቫ፣ ከዓለም ባንክ ምክትል ፕሬዚዳንትና የምስራቅ እና የደቡባዊ አፍሪካ ሃላፊ ቪክቶሪያ ክዋክዋ፣ ከዓለም ባንክ ምክትል ፕሬዚዳንትና የአይዳ ሃላፊ አኪህኮ ኒሺዮ እና ከሌሎች የዓለም ባንክ እና የዓለም አቀፉ ገንዘብ ድርጅት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ጋር መምከሩን ያመለከቱት የመንግስት መገናኛዎች ስለ ስብሰባው ውጤት እስካሁን ያሉት የለም። ባንኩም የሰጠው መረጃ አልተሰማም።
በምክክሩ ከተነሱ ጉዳዮች መካከል ስለኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሁኔታና የወደፊት ተስፋ፣ የተረጋጋ ሀገራዊ ጥቅል ኢኮኖሚ ለማምጣት እየተሰራ ስላለው የኢኮኖሚ ሪፎርም፣ ኢኮኖሚያዊ እድገትና የስራ ዕድል ፈጠራ፣ ምርታማነትን ማሳደግ እና የግሉ ክፍለ ኢኮኖሚን ለማሳለጥ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች ይገኙበታል፡፡
ተቋማቱ ኢትዮጵያ እየወሰደቻቸው ያሉትን ወሳኝ እርምጃዎች ኢኮኖሚውን ለማረጋጋት እና የዋጋ ንረትን ለመቅረፍ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎችን እንዲሁም በኢትዮጵያ እየተካሄደ ያለውን ሁለተኛ ምዕራፍ ሀገር አቀፍ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ፕሮግራምን በቀና መልኩ ማየታቸው ተሰምቷል።
በተጨማሪም ዓለም ባንክ እና ዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት ኢትዮጵያ እያካሄደች ያለውን የኢኮኖሚ ማሻሻያ ፕሮግራምን በሙሉ አቅም ለመተግበር ከማስቻል አኳያ በቀጣይ መደገፍ እና አብሮ መስራት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ውይይት ማድረጋቸው ቢገለጽም፣ ኢትዮጵያ ከውይይቱ በሁዋላ የምትፈልገውን ስለማሳካቷ በይፋም ይሁን ” ምንጭ” ነገረን የሚሉ ሚዲያዎች እንደወትሮው የስብሰባውን እግር ተከትለው ይህ እስከተሳፈ ድረስ ያሉት ነገር የለም።
ከገንዘብ ተቋማቱ ጋር የመጀመሪያው ውይይት በአዲስ አበባ እየተካሄደ ባለበት ወቅት ” ብር ሊገሽብ ነው። ሃብታችሁን ንብረት ላይ አድርጉ” በሚል በማህበራዊ ሚዲያዎች ሰፊ ዘመቻና ትህነትና ሲሰጥ ቆይቶ “ኢትዮጵያን ዓለም ባንክ የ1.7 ቢሊዮን ዶላር ስምምነት አደረጉ” የሚለው ዜና መሰማቱ ምንም እንኳን ውይይቱ ባይቋጭም ቅስቀሳውን ሲያካሂዱ ለቆዩት አካላት ደስታን አልፈጠርም።
ራሳቸውን ከዓለም ዓቀፍ ሚዲያዎች ጋር ያቆራኙና የሁሉም ጉዳይ ሚስጥር አዋቂ እንደሆኑ የሚናገሩ ወገኖች ውይይቱ መክሸፉን ለመጻፍ የፈጠኑትን ያህል 1.7 ቢሊዮን ዶላር መገኘቱን ለመዘገብ ፈቃደኛ አልሆኑም።
የሁለተኛው ውይይት ፍጻሜ ውጤት በምንዛሬ ችግር ለምታቃስተው ኢትዮጵያ በጉጉት የሚጠበቅ ነው። ከኮቪድ ጀምሮ በእርስ በእርስ ግጭትና ጦርነት እንድትታመስ የተለያዩ እጆች የሚዘረጉባት ኢትዮጵያ ለማገገም የውጭ ምንዛሬ ያስፈልግታል። ውሳኔው ቀደም ሲል የገንዘብ ተቋማቱ በኢትዮጵያ ላይ ሲያደርጉ ከነበረው የፖለቲካ ጫና መላቀቃቸውንም የሚያሳይ እንደሚሆንም ይጠበቃል። ተቋምቱ በዘንድሮው ዓመት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ከ6.5 በላይ እንደሚያድግ መተንበያቸው የሚታወስ ነው።
“ኢትዮጵያ ከIMF ብድር ለማግኘት የብርን የመግዛት አቅም ለማዳከም ትስማማለች ? ሌላስ አማራጭ የለም ?” በሚል የምጣኔ ሃብቱ ባለሞያ አቶ ያሬድ ኃይለመስቀልን ሸገር አናግሯቸው ነበር።
” devaluation የሚቀር አይመስለኝም። በምን ያህል ደረጃ devalue ይደረጋል የሚለው ጥያቄ ነው እንጂ devalue ሳይደረግ IMF / World Bank ገንዘብ ይሰጣል ብዬ እንደ ራሴ አልገምትም” ሲሉ ባለሙያው አስታውቀዋል።
አማራጭ ፖሊስ በራሱ መጥፎ አልነበረም። ቅደም ተከተሉን አለማስተካከል ነው ትልቁ ስህተት። ለምሳሌ ከሌሎች መጀመር ይቻል ነበር።
liberalization ሊቀድም ይችል ነበር ከdevaluation ፤ liberalization ሲደረግ አዲስ ካፒታል ወደ ሀገር ውስጥ እንዲገባ ማድረግ ይቻላል።
በዚህ ሂደት ካፒታል / ዶላር ይገኝ ነበር። ይህ ደግሞ የዶላርም ይሁን የሌላ ውጪ አሳሳቢ አይሆንም ነበር። እዳንም መቀነስ ይቻላል። አሁን ግን እዳ ይጨምራል።
ለምሳሌ ፦ የዛሬ 7 ዓመት ለባቡር ወይም ለሌላ የተበደርነው ዶላር ቢኖር መንግሥት ይጠበቅበት የነበረው 22 ብር ቀረጥ ሰብስቦ ወደ 21 ዶላር ቀይሮ መስጠት ነበር አሁን 56 እና 57 ታክስ መሰብሰብ አለበት።
የኑሮው ውድነት ?
ካለንበት ችግር በመነሳት የብር የመግዛት አቅም እንዲዳከም ቢወሰን በዋጋ ንረት ላይ በኑሮው መወደደ ላይ የሚያደርሰው ተፅእኖ ከባድ ነው።
ብዙ ነገር imported inflation የሚባለው ነዳጅ 39 ብር ነበር አሁን ከ70 በላይ ሆኗል ፤ ማዳበሪያውም ፣ ስንዴውም ፣ መኪናውም በብዛት 21 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት እቃ ወደ ሀገር ይገባል 3 – 4 ቢሊዮን የሚገመት export ታደርጋለች ይሄ ልዩነት ላይ ያለው 17 ቢሊዮን ብር የሚመጣውን እቃ ዋጋ ሊጨምረው ይችላል። ይሄ በእያንዳንዱ ቦታ ተበታትኖ በየሰዉ ኑሮ ላይ ተፅእኖ ያደርጋል።
inflation አሁን ትንሽ ረገብ አለ ቢባልም ከፍተኛ ነው። እንደገና ከፍ ሊል ይችላል።
ካፒታል ያላቸው ሰዎች ምንም ችግር የለባቸውም። ለምሳሌ ነጋዴ እቃ ቢወደድም ቢረክስም ችግር የለበትም የገዛበት ላይ ጨምሮ ነው የሚሸጠው ምናልባት ብዙ ላይሸጥ ይችላል ያ ሊጎዳው ይችላል።
ቁርጥ ያለ ገቢ ያለው ሰው ሊጎዳ ይችላል። ለምሳሌ የዛሬ 7 ዓመት 22 ሺህ ብር ደመወዝ የሚከፈለው ሰው 1000 ዶላር አካባቢ ነው አሁን ግን 450 ነው የሚያገኘው ስለዚህ ደመወዙ 50% ቅናሽ አድርጓል። በሌላ በኩል የመኖሪያ፣ የምግብ ዋጋ ጨምሯል።
ብዙ አማራጭ ያለ አይመስለኝም ከ devalue አንጻር። ያለውን ብር መቀበል ነው። አልያም ብሩን አልፈልግም ብሎ ሌላ አማራጭ መፈለግ ነው። ወይም የሚባለውን አድርጎ የሚያስከትለውን ችግር መፍትሄ መፈለግ ነው። “