ETHIO12.COM

ኦፌኮ -ከአማራ ክልል የተነሱ ታጣቂዎች በኦሮሚያ የመሬት ወረራ ፈጽመዋል- “ውሃ ሲወስድ እያሳሳቀ ነው”

“ከአማራ ክልላዊ መንግስት በመነሳት የጦር መሳሪያ የታጠቁ ኃይሎች በኃይል በመጣስ ጦርነት አውጀው የመሬት ወረራና የግዛት ማስፋፋት ተግባር ላይ ተሰማርተው ይገኛሉ”፦ ኦፌኮ

የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ ምክትል ሊቀ መንበር አቶ መልካሙ ሹምዬ የኦፌኮ መግለጫ ኦነግ ሸኔ ያሉት አካል በኦሮሚያና በሌሎች የሀገሪቱ ክልሎች ለሚፈፅመው ጥቃት አማራን ተጠያቂ የሚያደርግ እና በአማራ እና በኦረሮሞ ህዝብ መካከል ግጭት የሚፈጥር ነው ሲሉ ተችተዋል፡፡ VOA

ከአማራ ክልላዊ መንግስት በመነሳት የጦር መሳሪያ የታጠቁ ኃይሎች በኃይል በመጣስ ጦርነት አውጀው የመሬት ወረራና የግዛት ማስፋፋት ተግባር ላይ ተሰማርተው ይገኛሉ ሲል የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ (ኦፌኮ) ገለፀ።

ኦፌኮ መንግስት ሰሞኑን በአዲስ መልኩ ያወጀው ዘመቻ በጥቂቱ ፈንጥቆ የነበረውን የሰላም ጭላንጭል መልሶ የሚያደበዝዝ፤ ኦሮሚያና አገሪቱን ለተጨማሪ አደጋ የሚያጋልጥ እንጂ ዘላቂ መፍትሄ የማይሰጥ ነው ብሏል

በኹለቱ አካላት መካከል ያለው ግጭት ፖለቲካዊ መንስዔ ያለው ሲሆን መፍትሄውም ፖለቲካዊ መሆን አለበት ብሎ እንደሚያምንም አስታውቋል፡፡

በአጎራባች የኦሮሚያና የአማራ ክልሎች መካከል የሰላምና ፀጥታ ችግር እየተባባሰ ነው ያለው መግለጫው፣ ከሰሞኑ ይፋ እየተደረጉ ካሉ ዘገባዎች መረዳት እንደሚቻለው ከአማራ ክልላዊ መንግስት በመነሳት የጦር መሳሪያ የታጠቁ ኃይሎች በተለያዩ ሥፍራዎች በኩል የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስትን የታወቀ ወሰን በኃይል በመጣስ ጦርነት አውጀው የመሬት ወረራና የግዛት ማስፋፋት ተግባር ላይ ተሰማርተው ይገኛሉ ሲል በመግለጫው አስታውቋል፡፡

እነዚህ ኃይሎች ሰላማዊ ሰዎችን በመግደል፤ አርሷደሮችን ከመሬታቸው በማፈናቀል ክልሉን ወደማያባራ የግጭት ቀጠና እየለወጡት እንደሚገኙ፣ በተለይም ይህ የጦር ዘመቻና የመሬት ወረራ በምስራቅ ወለጋ፣ ሆሮ ጉድሩ ወለጋ፣ ሰሜን ሸዋ፣ ምዕራብ ሸዋና በምስራቅ ሸዋ ዞኖች፣ በተቀናጀ አኳኋን እየተካሔደ እንደሚገኝ ከአባሎቻችን እና ከአካባቢው ማህበረሰብ ለመረዳት ችለናል ብሏል፡፡

ታጥቀው ወረራ እያካሔዱ ባሉ የአማራ ክልል ኃይሎች በሚዲያ የሚሰጡት መግለጫም ይህንኑ ያረጋግጣል ሲልም ገልጿል፡፡

ይህን ወረራ የሚያካሂዱት ከክልሉ መንግስት እውቅና ውጪ ታጥቀው የሚንቀሳቀሱ “ጽንፈኛ” ኃይሎች ናቸው ቢባልም ይህ እውነት እንዳልሆነ የሚያመላክቱ ማስረጃዎች አሉ ያለው ኦፌኮ፣ እንዲህ ያለው አሰራር ህገመንግስቱን ከመፃረር አልፎ የሁለቱ ክልሎች ወንድማማች ህዝቦች ወደለየለት ጦርነት እንዲገቡ በር የሚከፍት መሆኑን አበክሮ አስጠንቅቋል፡፡

ይህ በጥላቻ ፕሮፓጋንዳ እየታገዘ የሚካሔደው የመሬት ወረራና የግዛት ማስፋፋት ዘመቻ ቀድሞውንም ባልሻረ ቁስል ላይ ጨው በመነስነስ የኹለቱን ህዝቦች ግንኙነት ወደከፋ የመጠፋፋት ጦርነት ሊገፋ እንደሚችል ኹለቱም ወገኖች ሊገነዘቡ ይገባል ሲልም ገልጿል፡፡

በኹለቱ ክልሎችና እነዚህ ትልልቅ ህዝቦች መካከል የሚደረገው ጦርነት አገሪቱንም ለብተና፤ የአፍሪካን ቀንድ ደግሞ ለከፋ አለመረጋጋት የሚያጋልጥ መሆኑ ታውቆ ይህ ድርጊት በአስቸኳይ እንዲቆም ኦፌኮ ባወጣው መግለጫ አሳስቧል፡፡(አዲስ ማለዳ)

Exit mobile version