ETHIO12.COM

የአቅመ ደካሞችን ጣሪያ መድፈንም ያስወግዛል?

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የአዲስ አበባ ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ተገኝተው ሪፖርት ካደመጡ በሁዋላ በሰጡት የስራ መመሪያ አገልጋይነት እጅግ ውድና መሰረታዊ መርህ ሊሆን እንደሚገባ ጠንካራ ቃላቶች በመጠቀም ተናግረው ነበር። መናገር ብቻ ሳይሆን ህሊናን በሚነካ መልኩ ሌብነትንና ዘረኝነትን ኮንነዋል። በዛው መጠን ስለ ደካሞች ምርቃትም አንስተዋል።

የአቅመ ደካሞችን ቤት የማደስ ዓመታዊ መርሃ ግብር ዛሬ ያስጀመሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ” አፈር ሳታቦካ ለውጥ የለም፣ ኮብራ መንዳት ዋጋ የለውም” ሲሉ በዘንድሮው የአቅመ ደካሞችን ቤት ማደስ ላይ ትኩረት እንዲሰጥ አሳስበው ነበር። የሚያማርሩ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች የመኖራቸውን ያህል የሚያፈስ ቆርቆሮ ሲቀየርላቸውና ጎርፉ ሲቆምላቸው ለሊቱን ሙሉ የሚመርቁ እናቶች እንዳሉ ለካቢኔ አባላቱ ነግረዋቸው ነበር።

“የአቅመ ደካሞችን ቤት አድሱና ተመረቁ” ያሉት አብይ አህመድ ወደ ስልጣን ከመጡ በሁዋላ በኢትዮጵያ መሪዎች ዘንዳ ብዙም ያልተለመደውን የድሆች ቤት ማደስ፣ አቅመ ደካሞችን ማዕድ ማቋደስ፣ ቤተመንግስት ከፍቶ ህዝብን ማግኘት፣ ተማሪዎች በትምህርት ቤት ምግብ እንዲያገኙ ማድረግ፣ የትምህርት መሳሪያና መለያ ልብስ በነጻ ማደል የመሳሰሉት፣ እንዲሁም አረንጓዴ አሻራና አሁን ላይ አስገራሚ ዜና የሆነው የስንዴ አብዮት ከሚጠቀሱላቸው ደግ ተግባሮቻቸው መካከል ይጠቀሳሉ። “አባይን ግድብን ሸጡ” የተባሉት አብይ አህመድ “አባይ ሲናገር ስድቡ ቆመ” እንዳሉት የስንዴ አብዮት መናገር ሲጀምር ስድቡ እንደሚቆም ያስታወሱት ኢትዮጵያ በነቀፌታና በጥላቻ ጀልባ መሳፈሯን ለማሳየት ነበር።

ጥቂት “ተቺዎች” ነን የሚሉ ዕለት ዕለት ስራዬ ብለው እርግማን ሲያወሩባቸው ቢውሉም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሲነጋ አዲስ ከተገነባው የኢትዮጵያ መከላክያ ጋር፣ ሲመሽ ጎመን እርሻ፣ ዳግም ሲነጋ የድሃ ቤት ማፈርስ ላይ፣ ከዛም ሲልቅ በሴራ የተበላሸውን የዲፕሎማሲ አካሄድ እያቃኑ መታየታቸውን በበጎ ሲያነሱ አለመታየታቸውን በርካቶች እየተቹ ነው።

መልካሙን አድንቆ፣ የጎደለውን መተቸት ለምን ነውር እንደሚሆን እንደማይገባቸው የሚናገሩ ” ትችት ሚዛን የሚኖረው በጎውን በጎ ሲል ብቻ ነው። አለያ ግን ተራ ጥላቻና ሌላ ዓላማ የማራመድ ጉዳይ ነው” ሲሉ የጥላቻው ጽንፍ በጎ ተግባራትን ማየት እንዳይቻል ማድረጉን ይናገራሉ።

” ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዳሉት አባይን ሸጡ ያሉ፣ አባይ ውሃ ይዞ ኤሌክትሪክ ማምረት ሲጀምር ይቅርታ አልጠየቁም። ማስተባበያ አልሰጡም። ይህ የሚያሳየው የሚዛንን መሳት ነው” የሚሉት አስተያየት ሰጪዎች በኢትዮጵያ አሁን የተጀመረው የስንዴ አብዮት ቀና ልብ ላላቸው ሁሉ ታላቅ አጀንዳ ሆኖ አርሶ አደሩን በማበረታታት ተረጂነትን ትውልዱ እንዲጠየፍ ድጋፍ ማድረግ በተግባቸው ነበር” ሲሉ ቅሬታቸውን ያኖራሉ።

አንድ መሪ ምንም ጥፋት ቢኖርበት የድሆች ሰፈር ገብቶ አዋራ እየቃመ ቤት ሲጠግንና አርዓያ ሆኖ ሲያስተባብር ማድነቅና ሌሎች ይህን ዓላማ እንዲከተሉ ማበረታታት ሲገባ ለስድብ ጣትን ምላስን ማሾል የጤና እንዳልሆን አምርረው የሚናገሩም ነቃፊዎቹ ጥቂት መሆናቻውን ” የፌስ ቡኳ ኢትዮጵያና መሬት ላይ ያለችው ኢትዮጵያ አንድ አይደሉም” ሲሉ የአብይ አህመድን ምሳሌ ያጠነክራሉ።

ማታ ማታ የሶስት እንቁራሪት ድምጽ ሲሰማ ብዙ መስለውት ከተማ ሄዶ በቀን 500 እንቁራሪት ለማቅረብ ከአንድ ሬስቶራንት ጋር ተስማምቶ በበነጋው እንቁራሪቶቹን ለመያዝ ወደ ውሃው ሲሄድ ሶስት ሆነው እንዳገኛቸው፣ ከዛም የተስማማበት ሬስቶራንት ሶስቱን ይዞ በመሄድ በገባው ውል መሰረት 500 ማቅረብ እንደማይችል፣ ባለ ሬስቶራንቱም “ለምን የማትችለውን ተናገርክ ሲለው” ሰውየው ” ጌታዬ ይቅርታ ማታ ማታ ሲጮሁ ብዙ መስለውኝ ነው” ብሎ እንደመለሰ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ከካቢኔዎቻቸው ጋር ሲመክሩ መናገራቸውን የሚያስታውሱ፣ ” አብይ አሕመድ ስራ ላይ ናቸው” ሲሉ ያደንቋቸዋል።

ሰሞኑንን የሚወራ ሲጠፋ ” የአብይ አሕመድ ባለቤት ቀዳምዊ እመቤት ዝናሽ ጠፉ” በሚል የሚጮህ ዕረእስ የተጀመረው ትንተና ባድመ ወታደር እያሉ መገናኘታቸውን አስታውሶ በመጨረሻ ” የጠፉት አዲስ መዝሙር ለማውጣት በልምምድ ተጠምደው ነው” ሲል ማጠናቀቁን፣ “ዝናሽ ታዬ ጠፉ” የሚለውን ርዕስ ያዩ በርካታ ወሬ አፍቃሪዎች ይህን ፍሬ አልባ ወሬ ላይክና ሼር እንዳደረጉ አስታውሰዋል። ይህን ያስታወሱት ዛሬ አብይ አህመድ የአቅመ ደካማ ጎጆዎችን ክረምት ሳይገባ ማደስ ማስጀመራቸውን ተክትሎ የጀመሩትን ነቀፌታ ለማሳየት ነው።

ዛሬ ማለዳ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ አዋሬ አካባቢ የሚኖሩ አቅመ ደካሞችን ቤት የማደስ ዓመታዊ መርሃ ግብርን ማስጀመራቸውን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ዥንጉርጉር አስተያየት እየተሰጠ ነው።

ሰው እዚህ ውስጥ ይኖራል። ይህን የአቅመ ደካሞች ቤት አፍርሶ መጠገን ክቡር ተግባር መሆኑንን የሚያውቀው ውስጡ ያለና ቀና አሳቢ የሆኑ ብቻ ናቸው

ጽህፈት ቤቱ በማህበራዊ ትስስር ገጹ ይፋ እንዳደረገው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን ዓመታዊ እንቅስቃሴ ያስጀመሩት ከአራት ዓመታት በፊት የጠቅላይ ሚኒስትርነት ኃላፊነትን በተቀበሉበት የመጀመሪያ ዓመት ሲሆን በተመሳሳይ የአቅመ ደካሞችን ቤት የመጠገን እርግማኑ እንደዚሁ አራተኛ ዓመቱን ይዟል።

የአቅመ ደካሞችን ቤት የማደስ ዓመታዊ መርሃ ግብር አላማ የአረጋውያን፣ የአቅመ ደካሞች፣ የአካል ጉዳተኞችና በኢኮኖሚ የተቸገሩ የህብረተሰብ ክፍሎችን መኖሪያ ቤት ማደስ ሲሉን ንጽሁ መኝታና መቀመጫ ይሰጣቸዋል። በየዓመቱ ክረምት ከመግባቱ በፊት የቤት እድሳት መርሃ ግብር የሚከናወንላቸውና ንጽህ ቤት የሚረከቡ ግን ” ሳንሞት ይህን ማየታችን” ደስታቸውን የሚገልጹበት መንገድ ልብን የሚነካ ነው።

በያዝነው ዓመት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ‘የመደመር መንገድ’ ከተሰኘው መጽሃፋቸው ሽያጭ በተገኘ ገንዘብ በአዋሬ አካባቢ ተለይተው ለታወቁ 23 ግለሰቦች የመኖሪያ ቤት ግንባታ የሚደረግበትን ሂደት ማስጀመራቸውን ነው ጽህፈት ቤታቸው ያመለከተው።

ይህንኑ መርሃ ግብር ተከትሎ የንግድ ድርጅቶች ማኅበራዊ ኃላፊነትን በመወጣት በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን ኑሮ ማሻሻል ይችላሉ ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ተናግረዋል። “ግለሰቦች፣ የንግድና የመንግሥት ተቋማት ክረምት ከመግባቱ በፊት በአካባቢያችን ላሉ በርካታ ሰዎች ምቹና ሰብአዊ ክብርን መሠረት ያደረገ የኑሮ ሁኔታን ለመፍጠር በሚደረገው ዓመታዊ ክንውን የበኩላቸውን እንዲወጡ ጥሪዬን አቀርባለሁ” ብለዋል። አክለውም በተለይም የንግድ ድርጅቶች ማኅበራዊ ኃላፊነትን በመወጣት በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን ኑሮ ማሻሻል እንደሚችሉ አመልክተዋል።

Exit mobile version