Site icon ETHIO12.COM

“በራማና ባድመ አካባቢ ትህነግ ከኤርትራ ኃይሎች ጋር ውጊያ ተካሂዷል”

የትግራይ ኃይሎች ከኤርትራ ጋር አዋሳኝ በሆኑት አካባቢዎች ላይ የከባድ መሳሪያ ጥቃት ከፍተው ለአጭር ጊዜ የቆየ ወታደራዊ ግጭት መካሄዱን ታማኝ ምንጭ ለቢቢሲ አረጋገጡ። ጥቃቱ ተፈጸመ የተባለው እሁድ ሚያዚያ 30/2014 ዓ.ም. ሲሆን በራማ እና ባድመ አካባቢ ባለው የኤርትራ ጦር ላይ ሲሆን፣ ጥቃቱን ተከትሎ በትግራይ ኃይሎችን በኤርትራ ጦር መካከል የተኩስ ልውውጥ መደረጉ ተገልጿል።

መቀለ የሚገኙ የቢቢሲ ምንጮች እንዲሁ ክልሉ ከኤርትራ ጋር በሚዋሰንበት ድንበር አካባቢ ግጭት ተቀስቅሶ እንደነበር ለቢቢሲ አረጋግጠዋል። ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ባለሥልጣን ለቢቢሲ እንደተናገሩት፤ የከባድ መሳሪያ ጥቃቱ ከትግራይ ኃይሎች በኩል መከፈቱን ተከትሎ በስፍራው “ውጊያ ተካሂዷል” ብለዋል። ነገር ግን የተኩስ ልውውጡ ለአጭር ጊዜ የቆየ መሆኑን እና ከፍተኛ ቁጥር ያለው እግረኛን ያላካተተ በከባድ መሳሪያ የተደረገ እንደነበር ምንጩ ጨምረው ገልጸዋል።

የከባድ መሳሪያ ጥቃቱን ተከትሎ ለአጭር ጊዜ በተደረገው የተኩስ “የትግራይ ኃይሎች ወደ ኋላ አፈግፍገው ውጊያውም ቆሟል” ሲሉ ተናግረዋል። ጨምረውም ይህ ጥቃት “የህወሓትን ተንኳሽ ባሕሪይ የሚያሳይ ነው” ሲሉም አክለዋል። ቢቢሲ ተፈጸመ ስለተባለው ጥቃት ከኤርትራ መንግሥት በኩል ይፋዊ ምላሽ ለማግኘት ሙከራ ቢያደርግም እስካሁን አልተሳካለትም።

የህወሓት ሊቀመንበር ደብረፂዮን ገ/ሚካኤል (ዶ/ር) ባለፈው ሳምንት ለዓለም አቀፍ ተቋማት በጻፉት ይፋዊ ደብዳቤ ላይ በሰሜን ኢትዮጵያ ላለው ጦርነት አስቸኳይ መፍትሔ በማፈላለግ እንዲያግዙ እና በትግራይ ላይ ተጥሏል ያሉት ከበባ እንዲያበቃ ካልተደረገ “ሌላ አማራጭ” ለመፈለግ እንደሚገደዱ ገልፀው ነበር።

ነገር ግን ይህ “አማራጭ” ያሉት ምን እንደሆነ በደብዳቤው ላይ አልተብራራም። ከአንድ ዓመት ተኩል በላይ ባስቆጠረው የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ውስጥ የኤርትራ ሠራዊት ተሳታፊ የነበረ ሲሆን፣ በጦርነቱ ጅማሬ ወቅት የህወሓት ኃይሎች ተደጋጋሚ የሮኬት ጥቃቶችን በኤርትራ ላይ መፈጸማቸው ይታወሳል። የትግራይ ኃይሎች በኢትዮጵያ ሠራዊት የሰሜን ዕዝ ላይ ጥቃት መፈጸማቸውን ተከትሎ የተቀሰቀሰው ጦርነት ወደ አማራና አፋር ክልል ተስፋፍቶ ለወራት የቆየ ሲሆን አስካሁን መቋጫ አላገኘም።

ከፌደራልና ከክልል ኃይሎች ጋር ፍጥጫ ውስጥ የሆኑት የህወሓት ኃይሎች፤ መንግሥት ሰብአዊ እርዳታ ያለገደብ ወደ ትግራይ ክልል እንዲገባ ያወጀውን ተኩስ አቁም ተከትሎ ጦርነቶች ጋብ ያሉ ቢመስሉም በድንገት ሊቀሰቀስ ይችላል የሚል ስጋት አለ።

ባለፈው ቅዳሜ ጠቅላይ ሚኒስትር ወደ ሰሜን ምዕራብ ኢትዮጵያ ተጉዘው የሠራዊቱን ዝግጁነት መጎብኘታቸው የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

በቅርቡ ህወሓት በሰሜኑ የኢትዮጵያ ጦርነት ለመሳተፍ ፍቃደኛ ያልሆኑ ልጆች ወላጆችን እያሰረ መሆኑን የቤተሰብ አባላት ለቢቢሲ ተናግረው ነበር።

Bbc Amharic

Exit mobile version