Site icon ETHIO12.COM

ጉቦ ስትቀበል እጅ ከፍንጅ የተያዘችው የመሬት ልማት መኔጅመንት ባለሙያ ክስ ተመሰረተባት

160 ሺ ብር ጉቦ ስትቀበል እጅ ከፍንጅ የተያዘችው የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ መሬት ልማት መኔጅመንት ባለሙያ ክስ ተመሰረተባት

ዐቃቤ ህግ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ መሬት ልማት መኔጅመንት ባለሙያ ሆና ስትሰራ 160 ሺ ብር ጉቦ በመቀበል ከባድ የሙስና ወንጀል በፈፀመች ግለሰብ ላይ ክስ መስርቷል::
ወ/ሮ ሃብታምነሽ ሊሞና የተባለችው ተከሳሽ የሙስና ወንጀል ለመደንገግ የወጣውን አዋጅ ቁጥር 881/2007 አንቀፅ 10 (2) ላይ የተመለከተውን በመተላለፏ ነው በጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ዘርፍ የሙስና ወንጀል ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ጄነራል ዐቃቤ ህግ ክስ የተመሰረተባት።

ተከሳሿ በን/ስ/ላፍቶ ክ/ከተማ መሬት ልማት ማኔጅመንት ጽ/ቤት የሰነድ አጣሪ ባለሞያ ሆና ስትሰራ በስራ ኃላፊነቷ ማድረግ የማይገባትን ለማድረግ በን/ስ/ላፍቶ ክ/ከተማ ወረዳ 02 በተበዳይ ስም ተመዝግቦ ይገኝ የነበረ ይዞታ በሽያጭ ወደ 4ኛ የዐቃቤ ሕግ ምስክር በመተላለፉ የሥም ዝውውር እንዲደረግ ለጽ/ቤቱ በቀረበው የአገልግሎት ጥያቄ መሰረት አስፈላጊ መስፈርቶች ሁሉ ተሟልተው እያለ ሚያዝያ 03 ቀን 2014 ዓ.ም የሥም ዝውውር ከተፈጸመ በኋላ ገዢዎችን በመወከል ጉዳዩን ሲከታተል የነበረው 1ኛ የዐቃቤ ሕግ ምስክርን “ካርታው ተሰርቷል ገንዘብ ካላመጣህ ግን ወጪ አድርገን አንሰጥህም” በማለት 160,000 (አንድ መቶ ስልሳ ሺ) ብር ጉቦ በመጠየቅ ሚያዝያ 10 ቀን 2014 ዓ/ም ከቀኑ በግምት 7፡30 በን/ስ/ላፍቶ ክ/ከተማ ወረዳ 12 ላፍቶ ቪው ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በ1ኛ የዓቃቤ ሕግ ምስክር ስም የተቆረጠ ቼክ 160,000 (የአንድ መቶ ስልሳ ሺ ) ብር ካሽ የተጻፈበት መኪና ዉስጥ ሆና ስትቀበል እጅ ከፍንጅ የተያዘች በመሆኑ በፈፀመችው ጉቦ መቀበል ከባድ የሙስና ወንጀል በጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ዘርፍ የሙስና ወንጀል ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ጄነራል ዐቃቤ ህግ ክስ ተመስርቶባታል ፡፡

ተከሳሿ ዛሬ ግንቦት 03/2014 ዓ.ም በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ሙስና ወንጀል ችሎት ቀርባ የክስ ቻርጅ አንዲደርሳት ከተደረገ በኋላ ክሱ በንባብ ተሰምቷል።

በዚህም መሰረት ፍርድ ቤቱ ተከሳሽ በክሱ ላይ የምታቀርበው የክስ መቃወሚያ ካለ ለመጠባበቅ ለግንቦት 05/2014 ዓ.ም ቀጠሮ ሰቷል ።

Via attorney general

Exit mobile version