Site icon ETHIO12.COM

አዊ – መቶ ሰላሳ ነብስ ገዳዮችን ጭምሮ ከአንድ ሺህ በላይ ተጠርጣሪዎች ተያዙ

እየተወሰደ ባለው ሕግ የማስከበር እርምጃ በአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር ከ1 ሺህ በላይ ተጠርጣሪዎች ለሕግ ቀረቡ፡፡ እየተወሰደ ባለው ሕግ የማስከበር እርምጃ 1 ሺህ 1 መቶ 13 ተጠርጣሪዎችን ለሕግ ማቅረቡን የአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር አስታወቀ።

ከተጠርጣሪዎቹ መካከል 130 የሚሆኑት በሰው ነፍስ ማጥፋት ወንጀል ተጠርጥረው በህግ ሲፈለጉ የነበሩ ናቸው ተብሏል፡፡

የአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንግዳ ዳኛው በብሔረሰብ አስተዳደሩ በቡድንና በተናጠል የተደራጁ ኀይሎች የኅብረተሰቡን መደበኛ እንቅስቃሴ በማስተጓጎል ሕዝቡ በመንግስት ላይ አመኔታ እንዳይኖረው ሲሰሩ መቆየታቸውን ተናግረዋል፡፡

የሕግ የበላይነት እንዲከበር ከኅብረተሰቡ በተነሳው ብርቱ ጥያቄና በመንግስት ቁርጠኝነት በተወሰደ እርምጃ እስካሁን ድረስ በብሔረሰብ አስተዳደሩ 1ሺህ 1መቶ 23 የወንጀል ተጠርጣሪዎች ለህግ ማቅረብ ተችሏልም ብለዋል ዋና አስተዳዳሪው፡፡

በቁጥጥር ስር ከዋሉት የወንጀል ተጠርጣሪዎች መካከል 130 የሚሆኑት በነፍስ ማጥፋት ወንጀል ተጠርጥረው በህግ ሲፈለጉ የነበሩ ሲሆን ቀሪዎቹ በመግደል ሙከራ፣ በተደራጀ ዝርፊያ፣ በህገ ወጥ የገንዘብ ዝውውር፣ በአስገድዶ መድፈርና በልዩልዩ ወንጀሎች የተጠረጠሩ መሆናቸውን ዋና አስተዳዳሪው ተናግረዋል፡፡

በፀጥታ ኀይሎች ላይ ጥቃት ለማድረስ ከሞከሩ ውስን ተጠርጣሪዎች በስተቀር በህግ ጥላ ስር የሚገኙ ሁሉም ተጠርጣሪዎች ሰብዓዊ መብታቸው ተጠብቆ ተገቢውን የፍርድ ውሳኔ እንዲያገኙ በየደረጃው በሚገኙ የወረዳ አስተዳዳሪዎች የሚመራ ግብረ ኀይል ተቋቁሙ እየተሰራ ስለመሆኑንም ገልፀዋል፡፡

ህግ የማስከበር እርምጃው የታሰበውን ግብ ሙሉ በሙ አሳክቷል ያሉት ዋና አስተዳዳሪው ኅብረተሰቡ በህግ የሚፈለጉ የቤተሰብ አባላትን ሳይቀር አሳልፎ በመስጠት ለህግ የበላይነት በከበር ቁርጠኝነቱን አሳይቷል ብለዋል፡፡

ህግ የማስከበር እርምጃው ኅብረተሰቡ በሰላም ወጥቶ በሰላም የመግባት ነፃነቱን እስኪጎናፀፍ ድረስ ተጠናክሮ ይቀጥላል ያሉት ዋና አስተዳዳሪው የብሔረሰብ አስተዳደሩ ሕዝብ ተጨማሪ ተጠርጣሪዎችን ለህግ ለማቅረብ በሚደረገው ጥረት የተለመደ ትብብሩን አጠናክሮ እንዲቀጥልም ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል ፡፡

ዘጋቢ፦ሳሙኤል አማረ – አሚኮ

Exit mobile version