Site icon ETHIO12.COM

ጋዜጠኛነትና አክቲቪስትነት የተደበላለቀባት ኢትዮጵያ – ተመስገን ደሳለኝ ታሰረ

ሰሞኑንን በርካታ “ጋዜጠኛ” የተባሉ ወገኖች መታሰራቸውን ራሱ መንግስት በይፋ አስታውቋል። ፍርድ ቤት የቀረቡና ጠንከር ያለ ክስ የተመሰረተባቸው አሉ። ዛሬ ደግሞ ” የደህንነት ምንጮቼ እንደምታሰር አስቀድመው ነግረውኛል” ሲል ለቢቢሲ አስታውቆ የነበረው ተመስገን ደሳለኝ መያዙ ይፋ ሆናል።

ተመስገን ዛሬ በሁለት መኪና የመጡ የመንግስት ሰዎች በቁጥጥር ስር እንዳዋሉት የስራ ባልደረቦቹን የጠቀሰው ቢቢሲ አመልክቷል። ስለ አያያዙ እንጂ ከዛ በሁዋላ ስላለው ሁኔታ ዝርዝር መረጃ አልቀረበም። ተመስገን “ከመከላከያ ውስጥ አዋቂዎች አገኘሁ” በሚለው መረጃ በተደጋጋሚ “የአገር መከላከያን ክብር ነክቷል” በሚል ከፍተኛ መኮንኖች ሳይቀሩ በግልጽ ወደ ህግ እንደሚሄዱ ሲያስታውቁ ነበር። የተቋሙን አገራዊ ክብርና ሃላፊነት አለማክበር “ቀይ መስመር” እንደሆነ ምክትል ኤታማዦር ሹሙ ጀነራል አበባው ማስታወቃቸውም ይታወቃል።

ተመስገን በግልጽ የተያዘበት ዋና ጉዳይ ምን እንደሆነ ባይሰማም ኤርትራ ከርመው እንደመጡ የሚነገርላቸውን ጀነራል ተፈራ ማሞን በተደጋጋሚ ማስተናገዱ፣ እሳቸው አሁን ላይ በአገር ክህደት ከመከሰሳቸው ስለመገናኘቱ ቢቢሲ ያለው ነገር የለም።

የፍትህ መጽሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር የሆነው ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ከቢሮው አዲስ አበባ ቢያዝም፣ ሰሞኑንን አብዛኞቹ ባህር ዳርና ከባህር ዳር ሲመለሱ መያዛቸው ” ባህር ዳር ምን እየሆነ ነው” የሚል ጥያቄ ያስነሳ ሲሆን በጥቅሉ አስራ አንድ የሚሆኑ ጋዜጠኞችና የሚዲያ ሠራተኞች በቁጥጥር ስር እንደዋሉ ይታወቃል። ይህም የሆነው በክልሉ የህግ ማስከበር ዘመቻ መጀመሩ በይፋ በተገለጸ ማግስት ነው።



በተደጋጋሚ እየታሰረ ሲፈታ የቆየው ተመስገን በመጽሄቱ ብቻ ሳይሆን በቃለ ምልልስ ደረጃ የኢትዮጵያ መከላከያ ከፍተኛ መኮንኖችን አቅምና ብቃት በመተቸት ይታወቃል። ተመስገን በመከላከያ ከፍተኛ አዝዦች የአቅም ችግር ላይ በሚሰጠው አስተያየት የሚያደንቁት አሉ። ” አግባንነት አለህ ወይ? ስለ ሚሊታሪ ሳይንስ ምን ታውቅለህ?” የሚል የበረታ ጥያቄና ቅሬታ የሚያቀርቡበት “ውሎውን ከተባረሩና በለውጡ ከተከፉ መኮንኖች ጋር ማድረጉ ለአሉባልታ ዳርጎታል” ሲሉ ከመከላከያ አካባቢ የሚደርሱትን መረጃዎች በተለይ በዛሬ ወቅት በጥንቃቄ ሊመለከት እንደሚገባ ምክር በማክበር ለመሰንዘር የሞከሩም ነበሩ።

ቢቢሲ የመንግስትን መረጃ ጠቅሶ በጥቅሉ በቁጥጥር ስር የዋሉት የዩቲዩብ መገናኛ ብዙኃን የሆኑት የአሻራ አምስት ጋዜጠኞች፣ አራት የቻናል ንስር ኢንተርናሽናል ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት፣ ኢትዮ ንቃት የተሰኘው ሚዲያ መስራችና አዘጋጅ መምህርና ጋዜጠኛ መስከረም አበራ እንዲሁም የገበያኑ ሚዲያ መስራችና ባለቤት አቶ ሰለሞን ሹምዬ መሆናቸውን ገልጿል። አያይዞም የአዲስ አበባና የፌደራል ፖሊስ ጽህፈት ቤቶች ተወካዮች ሃሙስ ግንቦት 18 ቀን 2014 ዓ.ም ለመንግስት መገናኛ ብዙሃን እንደተናገሩት በከተማዋ ባለፉት ሳምንታት ከ340 በላይ ግለሰቦች በሽብርና በሌሎች ወንጀሎች ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር መዋላቸውን መግለጻቸውን አመልክተዋል።

በጥቅሉ በኢትዮጵያ “ጋዜጠኛ” የሚለው ስምና ሙያው የሚጠይቀው ግዴታ አሳሳቢ ደረጃ መድረሱን፣ በተመሳሳይ ሙያዊ ሥነ ምግባር አክብረው የሚሠሩ ጋዜጠኞችን ከሚደርስባቸው ጥቃት መጠበቅ ደግሞ አግባብ እንደሆነ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃንና የዩኔስኮ ኃላፊዎች ሰሞኑንን ማስገንዘባቸው ይታወሳል።

ሕዝብ ከጸጥታ ጋር በተያያዘ ካሰማው ጩኸትና፣ አንድ መንግስት ቅድሚያ የዜጎቹን ደህንነት ማስጠበቀ የመጀመሪያ ግዴታው እንደሆን ተጠቅሶ ሲቀርብ የነበረውን አቤቱታ ተከትሎ መንግስት በምላው አገሪቱ የህግ ማስከበር መጀመሩን ማስታወቁ ይታወሳል። ከህግ ማስከበር ዘመቻ ጋር ተያይዞ ለእስር የተዳረጉት ጋዜጠኞች በአፋጣኝ እንዲፈቱ የዓለም የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት ሲፒጄ እንዲሁም ድንበር የለሹ የጋዜጠኞች መብት ተከራካሪ አርኤስኤፍ ጥያቄ ማቅረባቸው፣ አዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲም በተመሳሳይ ጋዜጠኞችና ማኅብረሰብ አንቂዎች በጅምላ እየታሰሩ መሆኑ ” አስጨንቆኛል” ማለቱ ይታወሳል። ኢሰመኮም በመግለጫው የጋዜጠኞችና ማኅበረሰብ አንቂዎች ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ለእስር እየተዳረጉ መሆኑን አግባብ እንዳልሆነ ማመልከቱ አይዘነጋም።

የፕሬስ ነፃነትን እንደ ሽፋን በመጠቀም በሃይማኖት፣ በብሔርና በተለያየ መንገድ አሳሳች መረጃዎች የሚያሰራጩና ችግር እየፈጠሩ ያሉትን ጋዜጠኞች ከድርጊታቸው መታቀብ እንደሚኖርባቸውም የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ምክር ቤት የዓለም ፕሬስ ነፃነት ቀን ምክንያት በማድረግ «ጋዜጠኝነት በዲጂታሉ ዓለም ውስጥ» በሚል መሪ ሃሳብ ከሳምት በፊት ባካሄደው ውይይት ላይ አስታውቆ ነበር። የነጻው ፕሬስ አባላትና የዩኔስኮ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር የተካተቱበት ይህ ስብሰባ በበጎም በክፉም በሙያው ዙሪያ ያሉት ችግሮች በራሳቸው አንደበት የቀረበበት እንደነበር በርካታ ሚዲያዎች መዘገባቸው ይታወሳል።



ለውጡን ተከትሎ ሙሉ በሙሉ ነጻ የሆነውን የፕሬስ ነጻነት ” በወጉ መጠቀም አልቻላችሁበትም” ሲሉ ባለሙያዎችና ዓለም አቀፍ ተቋማት ገና በጠዋቱ ማስታወቃቸው ይታወሳል። በዚህም ሳቢያ ነጻነቱን በአግባቡ አለመጠቀም መንግስትን ወደ አምባ ገነንነት ሊያሸጋገር የሚችል ግብአት ሊሆን እንደሚችል የተነበዩም ነበሩ።

በኢትዮጵያ የሃይማኖት፣ የብሄርና የዘር ጥላቻን በግልጽ ማራመድ እንደ መብት የተቆጠረና በውጤቱ ምንም ዓይነት አደጋ ቢደርስ ደንታ የማይሰጣቸው የሚዲያ አንቂዎችና “ጋዜጠኞች” መኖራቸው ገሃድ ነው። በተለይም መቀመጫቸውን ውጪ ያደረጉ “አንቂዎች” ሁሉንም እርግፍ አድርገው በመተው አማራ ክልል ላይ አተኩረው ዘመቻ እያካሄዱ ያለበት ምክንያትና ከጅርባ ያለው የትህነግ የዳግም ወረራ ዕቅድ ዜጎችን እርፍት የነሳ ጉዳይ እንደሆነ እየተገለጸ ነው። አካሄዱ ለበርካቶችም ግልጽ አልሆነም።



Exit mobile version