Site icon ETHIO12.COM

ወልቃይት “የብረት መዝጊያ” ጀግኖቿን አመሰገነች!

“ወልቃይት እንዴት እንደኖረ ያውቃል። ምን እንዳሳለፈ ይረዳል። ወልቃይት ውስጧ ምን ሲከናወን እንደነበር አትዘነጋም። ታዲያ ማን ወደዛ ዳግም ያያል? ማንስ ያ ዳግም እንዲመጣ ይፈቅዳል? የውልቃይት ቃል ኪዳኗና የጀግኖቿ ህብረት ለዳግም ቀንበር ዕድል አይሰጡም። ደፍሮ በክፉ ምኞት የሚመጣ ካለ ዋጋው የሚታውቀ ነው። ይህን በመረዳት ወደ ቀናው መንገድ መመለስ፣ ከጥፋትና በድለ መማር የተሻለ ይሆናል። ህዝብና ህዝብ መካከል የተገነባውን የተንኮል አጥርም ማፍረስ የሚቻለው በዚ መልኩ ነው” ከቀድሞ የክልሉ ነዋሪዎች የተወሰደ

ጀግና ጀግናን ያውቃል፤ ጀግናን ያከብራል፣ይወዳል፣ ያወድሳል፣ ይሸልማል። ጎበዝ ጎበዝን እየወለደ በማሳደግ ለወገን አለኝታ ለሀገርም ዘብ ይኾን ዘንድ ያበረክታል። ጀግና ሁልጊዜም ሀቀኛ ነው። የሰው አይመኝም የራሱንም አይሰጥም። መከራ ይበዛበት ይኾናል እንጅ አንገቱን ሊያስደፋው ግን አይቻለውም። ለጦር አይንበረከክም፣ ወሬም በፍፁም አይፈታውም! ይሄንን ሀቅ ወልቃይት ላይ አየን።

ወልቃይቴው የአማራ ሕዝብ የዘመን መቀያየር የሚወልደው ክፉ እሳቤ ይፈትነው ይኾናል እንጅ ከቶውንም ለሀገር ያለውን ፍቅር እንደማይቀንስበት አስመስክሯል። በኢትዮጵያዊነት ስም ተሸፋፍኖ በሕዝብ ጫንቃ ላይ ተጭኖ የቆየው አሸባሪው የትግራይ ቡድን በተለይም ለወልቃይቴ አማራዎች ከአርባ ዓመታትም የላቀ የመከራ ዘመንን አስመዝግቦ አልፏል። ይኽ ፅኑ እና የተራዘመ መከራ ወልቃይቴ አማራዎችን እንደወርቅ እየፈተነ የሀገር ፍቅራቸውን የበለጠ አበራላቸው እንጅ ከኢትዮጵያዊነት ማማ ማንሸራተት ግን አልተቻለውም።

የወልቃይቴዎች አማራዊ ማንነትና ኢትዮጵያዊ መንፈስ በትሕነግ የክፋት መዶሻ ቢወቀርም የበለጠ መገለጥ እንጅ አልደበዝዝ አለ። የሀገር ፍቅር ተምሳሌት ከዚህ ወዲያ ላሳር ነው። ለዚኽ ሁሉ ግፍ እጅ ሰጥቶ አንገት አለመድፋትም የጀግንነት መለኪያ ሚዛንነት ነው።

ሚዛኑ የወልቃይት አማራ ለትዕግስቱና ለፅናቱ ፍሬ የሚኾን የሱ ቀን መጣለት። የኾነው ኹሉ ኾኖ ነፃነቱን በእጁ አስገባ። ዛሬ ወልቃይት ለዘመናት የተነጠቀ ሀቁን ዞሮ ተቆናጠጠ። በአማራዊ ማንነቱና በኢትዮጵያዊ ክብሩ መኖር ጀመረ።

ጀግና ለሌላው ክብርና ሞገስን አይነፍግም። ዛሬ ጀግናው የወልቃይት ሕዝብ ጀግኖቹን ሲያወድስ ውሏል። ዞኑ ወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ነው። ወረዳው ወልቃይት፤ በዋና ከተማዋ ወፍአርግፍ ከተማ በተዘጋጀ መድረክ የዞን ከፍተኛ አመራሮች፣ የሀገር መከላከያ ሠራዊት ከፍተኛ የጦር አመራሮች እንዲኹም የአማራ ልዩ ኃይል ከፍተኛ አዛዦች ተገኝተው ከወልቃይት ሕዝብና ከፍተኛ የሥራ ኀላፊዎች ምስጋና ቀርቦላቸዋል።

የመድረኩ ዋና ዓላማ የኢትዮጵያን ዳር ድንበር ለማስከበር ውድ ሕይወታቸውን የሚሰጡ የመከላከያ ሠራዊትና የልዩ ኃይል አባላትን ለማመስገንና ቀጣይ ደጀንነትን ለመግለፅ ነበር።

የወልቃይት የሀገር ሽማግሌዎች እና የሃይማኖት አባቶች በመድረኩ ተገኝተው የኢትዮጵያ ዘብ የሆኑትን የፀጥታ አካላት አመስግነዋል። “ወልቃይት ጠገዴን ብሎም መላውን ኢትዮጵያውያን ነፃ አውጥታችኋልና ክንዳችሁን አይቆርጥመው” ብለዋል።

የወልቃይት ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ክብረአብ ስማቸው ለጦር አመራሮች እንኳን ደኽና መጣችሁ በማለት የወልቃይት ሕዝብ በግንባርም ይሁን በደጀንነት በመሰለፉ ለድልና ለነፃነት መብቃትን ተናግረዋል። ሕዝቡ ከአማራ ልዩ ኃይልና ከመከላከያ ሠራዊት ጎን ለአፍታም የማይርቅና በተፈለገበት ግንባር ኹሉ ዝግጁ እንደኾነም አረጋግጠዋል።

የወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሸተ ደምለው ወልቃይቴነት ከአርባ ዓመታት በላይ በዘለቀው የትህነግ ስቃይ ሸብረክ ያላለ ከብረት የጠነከረ አማራዊ ማንነት እንደሆነ ገልፀዋል። የወልቃይት ነፃነት እንዲመጣ ለተፋለሙ መላው የፀጥታ አካላትም ምስጋና ሰጥተዋል።

“ትሕነግ የቀረው ብቸኛው ጉልበቱ ውሸትና ማምታታት ስለሆነ መላ ኢትዮጵያውያን ነቅተው መታገል አለባቸው” ብለዋል። አሁን ላይ የተገኘው ድል ሙሉ በሙሉ እንዲረጋገጥ የዞኑ ሕዝብ ከመከላከያ ሠራዊትና ከልዩ ኃይል ጎን ከመቆም በተጨማሪ የትሕነግ ተላላኪዎችን በመለየት እየታገለ ነው ብለዋል። “የታፈረችና የተከበረች ሀገር ለመመስረት ጠንካራ መከላከያ አስፈላጊ ነው” ያሉት አቶ አሸተ ወጣቶች መከላከያ ሠራዊትን በተለያዩ ሙያዎች በመቀላቀል ለሀገር ዘብ መኾን አለባቸው ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል።

የወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሑመራ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የሰላምና ደኅንነት መምሪያ ኀላፊ ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ በመድረኩ ተገኝተው ጀግናው የሀገር መከላከያ ሠራዊትና የአማራ ልዩ ኃይል ከሌሎች ሰላም አስከባሪዎች ጋር በመቀናጀት ላስገኙት ነፃነት ምስጋና አቅርበዋል። የወልቃይት ጠገዴ ሕዝብ ከመከላከያ ጎን ቆሞ ሀገሩን ለመጠበቅ አስፈላጊውን ሁሉ የደጀንነት ሥራ ማከናወኑን ገልፀዋል።

የወልቃይት ሕዝብ ያዘጋጀውን የአካባቢውን ሙሉ ባሕላዊ አለባበስ የሚያሳዩ አልባሳትና ቁሳቁስንም ለጦር አመራሮች በክብር አልብሰዋል።

የጦር አመራሮች የወያኔ ጉልበቱ ጥይቱ ሳይኾን የሀሰት ፕሮፓጋንዳው ነው ብለዋል። “ጠላት ወልቃይት የገባ አስመስሎ የሚያሰራጨው መረጃ የሀሰት ፕሮፓጋንዳው አንዱ ማሳያ ነው” ያሉት የጦር አዛዥ ይህ ፍፁም ከእውነት የራቀ በመኾኑ ሕዝቡ መምታታት የለበትም ብለዋል። የትሕነግን ተከዜን ተሻግሮ ወልቃይት የመግባት ህልም ባዶ የሚያስቀር የሠራዊት አቅም ተገንብቷል ሲሉም ተናግረዋል።

የወልቃይት ሕዝብ ወያኔን አምርሮ ታግሏል፤ አሁንም ቢኾን ለመከላከያና ለልዩ ኃይል ያለው ደጀንነት የሚያኮራ ነው ብለዋል። አሸባሪው ትሕነግ ወልቃይትን ተቆጣጥሮ ከውጭ ጠላት ጋር በመገናኘት ሀገር የማፍረስ ዓላማን ይዞ ስለሚባዝን ሁሉም ኢትዮጵያዊ በአንድነት ቆሞ መታገል ይገባል ሲሉ ከፍተኛ ጦር አዛዦች መልዕክት አስተላልፈዋል።

ዘጋቢ:- አሚናዳብ አራጋው


Exit mobile version