ETHIO12.COM

በህዳሴ ሙሌት ዋዜማ ኢትዮጵያ ግብጽ ላይ የበላይ ሆነች፤ አገር በደስታ ዘለለ

ሳንጫወት በስነልቦና ይረቱን የነበሩት ግብጾች በኢትዮጵያ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ሁለት ለባዶ ተደቁሰዋል። ድሉ ለመላው ኢትዮጵያዊያን ልዩ ትርጉም ያለው ሆኗል። የህዳሴ ግድብ ማላዊ ላይ በራ ሲሉ በማሀበራዊ ገጾች ስሜታቸውን የገለጹ አሉ። የመንግስት ባለስልጣናት፣ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይን ጨምሮ ” ጀግኖች” ሲሉ ተቸዋቾቹን በማመስገን ድሉን አድምቀውታል።

ለኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊያን ከስኬት ዜና ይልቅ የለቅሶና የቁዘማ ትንተና በማቅረብ ላይ ከተጠመዱት መርዶ ፈልፋዮች በስተቀር ድሉ ከዳር እስከዳር ህዝብን አነቃንቋል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የግብፅ አቻውን በማላዊ ሜዳ 2 ለባዶ ማሸነፉን ተከትሎ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የ2 ሚሊዮን ብር የማበረታቻ ሽልማት እንደሚሰጥ አስታውቋል፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት አቶ ኢሳያስ ጂራ ” ይህ ከእግር ኳስ በላይ ብዙ ትርጉም ያለውን ጨዋታ በድል በማጠናቀቃችሁ ኩራት ተሰምቶናል” ብለዋል ባስተላለፉት መልዕክት፡፡
የፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ በአስቸኳይ ተወያይቶ ዛሬ በተገኘው ድል እና ቡድኑ ባለፈው ጨዋታ ላደረገው ሁሉ የ2 ሚልዮን ብር ሽልማት እንደሚያበረክት መወሰኑንም ፌደሬሽኑ አስታውቋል።
ኢትዮጵያን እናልማ፣እንገንባ፣እንዘጋጅ‼
ሀገርን በዘላቂነት እናልማ‼
የፈረሰውን አብልጠን እንገንባ ‼
ለማንኛውም ፈተና እንዘጋጅ‼
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡

“ለምን ውሃችሁን ተገድባላችሁ” በሚል ነውጠኞችን ስፖንሰር የምታደርገው ግብጽ የዛሬው ሽንፈቷ በካይሮ “ጥቁር ቀን” ተብሏል። እጅግ ተበሳጭተው “የዳግም ሽንፈታቸው” ማሳያ እንደሆነ የገለጹም አሉ።

ዛሬ ምሽት በተካሄደው የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ውድድር የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ግብፅ ላይ ሁለት ጎል ጭምሮ ማሸነፉ ሰሞኑንን በዓለም ዙሪያ መነጋገሪያ ከሆነው የስንዴ እርሻ ጋር ተዳምሮ ለኢትዮጵያ ተጨማሪ የትጋት ወጤት ዜና ሆኗል።

“ጀግኖቹ ልጆቻችን ላበረከቱልን ጣፋጭ ድል መላው ኢትዮጵያውያን እንኳን ደስ አላችሁ! እንኳን ደስ አለን!! የኢትዮጵያ ድል ገና አላለቀም፤ ተጀመረ እንጂ! ፈጣሪ ኢትዮጵንና ህዝቦቿን አብዝቶ ይባርክ!!” ሲሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ደስታቸውን ገልጸዋል።

የህዳሴው ግድብ መሪና ተደራዳሪ፣ በአሜሪካ ባለ ሙሉ ስልጣን አምባሳደር ኢንጊነር ስለሺ በቀለ ” የኢትዮጵያችን እግር ኳስ ቡድን ተጫዋቾች በጣም ጥሩ ተጫውታችሁ በማሸነፋችሁ እንኳን ደስ አላችሁ:: እኛም ደስ ብሎናል” ብለዋል።

በኳስ ደረጃቸው በአፍሪካ ሶሰተኛና አርባ ሶስተኛ ላይ የሚገኙት አገሮች በአንድ ተሰልፈው ይህ ድል መመዝገቡ ለውደፊት ኳሱን ከስር በአግባቡ ገንብቶ ለማስኬድ ታላቅ ስንቅ ሊሆን እንደሚገባ የገለጹ አሉ። ፍርዖኖቹን መቀጥቀጥ እንዳለ ሆኖ ከድሉ ባሻገር ቀጣይነት ያለው ድል እንዲኖር ለመስራት ባለስልጣናት ከወዲሁ እንዲዘጋጁ የሚያነሳሳ ድል ነው። አዲስ ዘመን ታሪክ ተሰራ ሲል ከታች ያለውን አስፍሯል።

ታሪክ ተሰራ

ኢትዮጵያና ግብጽ የአፍሪካ እግር ኳስ ጠንሳሾች ናቸው። ይህን ታሪክ ይጋሩት እንጂ ዛሬ ላይ የሁለቱ አገራት የእግር ኳስ ደረጃ ልዩነቱ ሰፊ ነው።

የደረጃ ልዩነቱ የቱንም ያህል ቢሰፋ ግን በተለያዩ ምክንያቶች የተቀናቃኝነት ስሜታቸው ለአፍታም ደብዝዞ አያውቅም።

ሁለቱ አገራት የአለም ብሎም የአፍሪካ ጥንታዊ ስልጣኔ መገለጫ ከመሆናቸው ባሻገር በተለያዩ የታሪክ አጋጣሚዎች የገጠሙት ጦርነትና የአባይ ወንዝ ትስስር በእግር ኳሱ መንደር ሲገናኙ ፍልሚያቸውን ይበልጥ ያጦዘዋል።

በተለይም ሁለቱ አገራት ከታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታና ውሀ ሙሌት ጋር በተያያዘ ከቅርብ አመታት ወዲህ የገቡበት ውዝግብ ባላንጣነታቸውን አደባባይ እንዳወጣው በርካቶች ይስማሙበታል።

ዋልያዎቹ ከፈርኦኖቹ፣ ሁለቱ አገራት ውጥረት ውስጥ ባሉበት፣ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታም ተጀምሮ ሶስተኛው ዙር የውሃ ሙሌት ሊከናወን በተቃረበበት በዚህ ወቅት ዛሬ በታላቅ የእግር ኳስ መድረክ ተገናኙ።

በ2023 ኮትዲቯር ለምታዘጋጀው የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ በማጣሪያ ጨዋታ በምድብ አራት የተደለደሉት ዋልያዎቹና ፈርኦኖቹ በገለልተኛ አገር ማላዊ ላይ ሁለተኛ የምድብ ጨዋታቸውን አከናወኑ።

ብርቅዬዎቹ ዋልያዎችም ያልተጠበቀ ድል በፈርኦኖቹ ላይ ተቀዳጅተው ለሁለቱም አገራት ከእግር ኳስም በላይ ትርጉም ባለው የክብር ፍልሚያ ታሪክ የማይረሳው ገድል ፈጸሙ።

ኢትዮጵያ ይህን ታላቅ ፍልሚያ በሜዳዋ ማስተናገድ አለመቻሏ ቁጭት ውስጥ የከተታቸው ዋልያዎቹ በጄነራላቸው ውበቱ አባተ እየተመሩ በፊት አውራሪዎቹ ዳዋ ሆጤሳና አቡበከር ናስር ቅንጅት የፈርኦኖቹን መረብ ለመድፈር 25 ደቂቃ እንኳን አልፈጀባቸውም።

በታሪክ አጋጣሚ ባለፉት በርካታ አመታት ፈርኦኖቹ ዋልያዎቹን በአስራ አንድ ጨዋታ ሙሉ በሙሉ ማሸነፍ ችለዋል።

ይህም ብቻ ሳይሆን ፈርኦኖቹና ዋልያዎቹ ሲገናኙ ዋልያዎቹ በሰፊ የግብ ልዩነት እንዳይሸነፉ ደጋፊው የሚጨነቅበት ዘመን የሚዘኘጋ አይደለም።

ዛሬ ግን ታሪክ ተቀየረ፣ ዋልያዎቹም ቀንዳቸው መዋጋት ጀመረ። የፈርኦኖቹን መረብ ዳግም ለመድፈር ጨዋታ አቀጣጣዩ ሽመልስ በቀለ ሁለተኛውን አርባ አምስት ደቂቃ መጠበቅ አላስፈለገውም።

ዋልያዎቹ በፍጹም የጨዋታ ብልጫ ፈርኦኖቹ የሚይዙትንና የሚጨብጡትን ሲያሳጡ ሁለቱ አገራት በአፍሪካ እግር ኳስ የደረጃ ሰንጠረዥ ሶስተኛና አርባ ሶስተኛ ላይ የሚገኙ ናቸው ብሎ ለማመን አይቻልም።

ይህን ተአምርና ጣፋጭ ድል ዋልያዎቹ በሜዳቸውና በደጋፊያቸው ፊት ማጣጣም ቢችሉ ምንኛ መልካም ነበር። ሆኖም ይህን ቁጭት ትርጉመ ብዙው ድል አካክሶታል።

ዋልያዎቹ ይህን ታሪክ ለመጻፍ ለአገራቸው ክብር ያላቸውን ሁሉ ሰጥተዋል።

በኢትዮጵያ ስፖርት “ታሪክ ተሰራ” ለአትሌቲክስ ጀግኖች ነበር የሚሰራው። ይህን የዋልያዎቹን ገድል “ታሪክ ተሰራ” ከማለት ውጪ ምን ሊገልጸው ይችላል?።

በቦጋለ አበበ

Exit mobile version