Site icon ETHIO12.COM

“ካይሮ ከሶስተኛው ሙሌት በኋላ ቀሪ ተስፋዋ ምንድነው?”

እስሌማን የአባይ ልጅ

“የካይሮ ቀጣይ ተስፋ አሜሪካ፣ ኢማራት እንዲሁም የተለያዩ ሀያላን ሀገራት የሚያሳድሩላት ጫና ነው፣ ግብፅ የኢትዮጵያን የተሳሳተ አቋም ለአለም አቀፍ የህዝብ አስተያየት እና ከኢትዮጵያ ጋር ጥሩ ግንኙነት ያላቸውን አሜሪካን፣ የአውሮፓ ሀገራት፣ ሩሲያና ቻይናን ጨምሮ በተፅእኖ ፈጣሪ ሀገራት ፊት በማጋለጥ ዲፕሎማሲያዊና የሚዲያ ዘመቻዋን ትቀጥላለች”

ከጽሁፉ የተወሰደ


ግብፃዊ ምሁራን በአልአህራም ጋዜጣ

የዓባይ ልጅ – እስሌማን ዓባይ

የግብፁ አህራም ጋዜጣ ማምሻውን ባወጣው ሰፋ ያለ ትንተናው በካይሮ ልሂቃን የተንፀባረቀው፤ የቢንዛይዷ ኢማራት ባለ ሁለት ስለት ቢላዋ እንደሆነችባቸው፤ በጣሙንም እንደሚሰጓት፤ በሰሞነኛው የአቡዳቢ መንግስት ደብዳቤ ክፉኛ መንገብገባቸውን፣ በተቃራኒው ኢማራት አንዳች ውለታ እእንድታደርግላት ህልምና ምኞት ላይ መሆናቸውን፤ ለአፍሪካ ባላቸው ንቀታቸው መቀጠላቸውን፣ አረብ ሊግ ላይ የነበራቸውን ተስፋ መጨረሳቸውን፤ በአሜሪካ ማእቀብና የሚዲያ ዘመቻቸው ቀሪ ተስፋቸው ስለመሆኑ…. ትንተና ዳሰሳ እና ምክረ ሐሳብ ያሉትን የሰፈሩበት ነው።

“ኢትዮጵያ በጅ አትለንም” የካይሮ ምሁራን

በአህራም ጋዜጣ የአፍሪካ ጉዳዮች የረጂም አመታት ኤክስፐርት አቲያ ኢሳዊ “ኢትዮጵያ በGERD ላይ የምታደርገውን የአንድ ወገን ተግባሯን የምታቆም አይመስልም” ሲሉ ለአህራም ተናግረዋል።

ታዲያ “ግብፅ የኢትዮጵያን የተሳሳተ አቋም ለአለም አቀፍ የህዝብ አስተያየት እና ከኢትዮጵያ ጋር ጥሩ ግንኙነት ያላቸውን አሜሪካን፣ የአውሮፓ ሀገራት፣ ሩሲያና ቻይናን ጨምሮ በተፅእኖ ፈጣሪ ሀገራት ፊት በማጋለጥ ዲፕሎማሲያዊና የሚዲያ ዘመቻዋን ትቀጥላለች” ሲል ነው ኢሳዊ የገለፁት።

ተመራማሪው “ግብፅ በዲፕሎማሲያዊና የሚዲያ ዘመቻዎች መቀጠሏ ሀገሪቱ በውሃ ጥቅሟ ላይ ሊደርስ የሚችለውን ስጋቷን ለአለም አጉልቶ ያሳይላታል” ያሉ ሲሆን “ይህም በፀጥታው ም/ቤትም ሆነ በአሜሪካ በኩል ለተጀመሩ ጥረቶች ሁሉም ወገኖች ወደ ድርድር ጠረጴዛ ይመለሱ ዘንድ የመፍትሄ መንገድ ይከፍታል” ሲሉ ነው ኢሳዊ የተናገሩት።

ኢሳዊ አክለው “ግድቡ አለማቀፉን የድንበር ተሻጋሪ ወንዞች ህግጋትን በመፃረር በናይል ውሀ ላይ ተመስርተው የተገነቡ ነባር የታችኛው ተፋሰስ ፕሮጀክቶችን መጉዳት እንደሌለበት የሚደግፉ ይዘቶችን የሚጥስ ነው” ብለዋል።

ዋሽንግተን (ባይደናሟ)

የአሜሪካ የአፍሪካ ቀንድ ልዩ ልዑክ ማይክ ሀመር በቅርቡ በግብፅ፣ ኢትዮጵያና የተባበሩት ኢማራት ባደረጉት ጉብኝት፣ ዩናይትድ ስቴትስ በ GERD ጉዳይ ጥረት መጀመሯን ገልፀዋል ያለው አህራም “ከ2019 ጀምሮ አሜሪካ በሶስቱ ሀገራት ያለውን አለመግባባት ለመፍታት ያደረገው ሙከራ የላቀ ደረጃ ላይ ቢደርስም ከሽፏል። በትግራይ የተፈጠረውን ግጭት ተከትሎ በአሜሪካና ኢትዮጵያ መካከል ውጥረቱ ቢጨምርም፣ የባይደን አስተዳደር በGERD ጉዳይ ያሳዩት አቋም የተለሳለሰ መሆኑ ግብፅን ውጤት አሳጥቷል” ብሏል።

“አሜሪካ በGERD ግብፅን የሚጠቅም ተፅዕኖ መፍጠር የምትችለው የካሮትና ዱላ ዘዴን ኢትዮጵያ በመጠቀም ነው” ያሉት ኢሳም “በዚህም ኢትዮጵያ በቀጣይ ድርድር ግትርነቷን ከተወችው የማዕቀብ ስጋቶችን የመተው፣ በአቋሜ እቀጥላለሁ ስትል ግን ተጨማሪ ማዕቀብ ይጣልባታል” በሚለው ዘዴ ሲሉ ኢሳዊ ተናግረዋል።

ኢማራት – አቡዳቢ

UAE በሚኖራት ሚና ላይ የተደበላለቀ ስሜት ያንፀባረቁ ሲሆን በተለይም በቀደሙ ጊዜያት ኢማራት ለኢትዮጵያ ወግናለች የሚለውም ድምፀት አቀዛቅዘውታል። በሌላ በኩል ከግብፅም ሆነ ከኢትዮጵያ የጠበቀ ግንኙነት ያላት መሆኗ ከባህረ ሰላጤው ሀገራት በግድቡ ድርድር ሚና እንድትጫወት አስችሏታል ሲሉ ገልፀዋታል። ከዚህ ቀደም ስጋት ያሏትን ሀገር እነሰደ መማለጃ መቁጠራቸው ሌሎች እንደ አረብ ሊግ እና ሳኡዲ ላይ የነበራቸው ተስፋ የመክሰሙ ማሳያ ነው። በተያዘው አመት ግንቦትና ሰኔ ላይ አቡዳቢ ያስተናገደችው ሁለት ዙር የግድቡ ቴክኒካል ውይይት ያለ ውጤት መቋጨታቸውን የገለፀው የአህራም ትንተና

“ኢትዮጵያ ግትር አቋሟን ትቀይር ዘንድ ኤማራት ትልቅ ሚና መጫወት ትችላለች” የሚለውን የኢሳዊ አስተያየት አስፍሯል።

አልአህራም “ኢማራት የግድቡን የድርድር ኳስ በአፍሪካ ህብረት ሜዳ አስቀምጣለች። ሦስቱ ሀገራት በአፍሪካ ህብረት ጥላ ስር በቅንነት እና ለአፍሪካ ችግሮች አፍሪካዊ መፍትሄዎች በሚለው መንፈስ እንዲቀጥሉ ጥሪ አቅርባለች” ያለ ሲሆን “በተመድ የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች ቋሚ ልዑክ በሶስቱ ሀገራት 2015ቱ የመርሆዎች መግለጫ ማጣቀሻነት ድርድሩ እንዲቀጥል መግለጿ ቀደም ሲል አፍሪካ ህብረት ስር የአውሮፓ ህብረት፣ የአሜሪካና የአፍሪካ ህብረት የህግና ቴክኒካል ባለሙያዎች በተሳተፉበት የGERD ድርድር ላይ ላለፉት ሁለት አመታት መፍትሄ ማምጣት እንዳልቻለ እየታወቀ ነው” ሲል አስነብቧል።

የግብፅ የቀድሞው መስኖና የውሃ ሀብት ሚኒስትር ሞሃመድ ናስር አላም “ሦስቱ ሀገራት በGERD ጉዳይ እኩል የመስማማት ፍላጎት ያላቸው አስመስላ ኢማራት ያወጣችው መግለጫ ኢትዮጵያ አለም አቀፍ ህግን አክብራ የስምምነት መንገዶችን የምታደናቅፍ መሆኗን እያወቀች ነው” ሲሉ የሰጡትን አስተያየት ያስነበበው አህራም “የተባበሩት አረብ ኢማራት የድርድሩን ሀላፊነት ለአፍሪካ ህብረት የወረወረችው ኢትዮጵያ በግብፅ፣ በሱዳን እና በአፍሪካ ህብረት የተደረጉ ሙከራዎችን ሁሉ ማደናቀፏን እያወቀች ነው” ሲሉ አላም መፃፋቸውን አክሏል።

የፀጥታ ም/ቤቱርምጃ ‘ተስፋ ቢሱ’ – ተስፋ

በካይሮ ዩኒቨርሲቲ የጂኦሎጂ እና የውሃ ሃብት መምህር አባስ ሻራኪ ምክር ቤቱ ካይሮ ጉዳዩን ከቴክኒካል ይልቅ ከደህንነት ስጋት አንፃር ማሳመን ካልቻለች በስተቀር ግብፅ በላከችው ሶስተኛው ደብዳቤዋ ተመስርቶ እጁን የሚያስገባ አይሆንም” ማለታቸውን አስፍሯል።

ፕሮፌሠር አባስ ሻራኪ “ኢትዮጵያ የህዳሴ ግድቡን የውሃ ቦምብ እያደረገችው ነው።” ማለታቸውን ያወሳው አህራም “ይህ የውሃ ቦንብ ለግብፅ ከኒውክሌር ቦምብ የበለጠ አውዳሚዋ ሊሆን ይችላል” ሲሉ ግብፃዊው ምሁር ማስጠንቀቃቸውንም አውስቷል።

በሌላ በኩል፣ በአህራም የአፍሪካ ጉዳዮች ተንታኝ ኢሳዊ “የፀጥታው ም/ቤት በGERD ጉዳይ ምንም አይነት እርምጃ እንደማይወስድ ይናገራል” ይህን ለማድረግ “ቢያንስ አምስት ቋሚ አባላቱ ሩሲያ፣ ቻይና እና አሜሪካ በጉዳዩ ላይ ስምምነት ላይ መድረስ ሲችሉ ብቻ ነው” ከዚህ አንፃር ሲታይ እጅግ የማይመስል ነገር ነው። የፀጠሰታ ምክር ቤቱ የውሀ ጦርነት እስካልተፈጠረ ድረስ ምንም አይነት እርምጃ ይወስዳል ተብሎ አይጠበቅም” ሲል ኢሳዊ ተናግሯል።

ግብፅ ስጋቷን ለማስወገድ ወታደራዊ ርምጃ ብትወስድ አለማቀፍ መብት አላት ያለው የአህራም ትንተና በተለይ አሁን ካለው ዓለም አቀፍ ተጨባጭ ሁኔታ አንፃር ግብፅ ግድቡ ላይ የኃይል ርምጃን እንዳትጠቀም የሚከለክለው የፀጥታ ምክር ቤቱን ጨምሮ በተለይም ሩሲያን ጨምሮ አንዳንድ ቋሚ አባላት በኢትዮጵያ ከፍተኛ የኢንቨስትመንትና የጸጥታ ፍላጎት ስላላቸው በምክር ቤቱ ድንጋጌ ምዕራፍ 7 መሰረት ሀገራቱ አይፈቅዱም” ሲሉ ገልፀዋል።

አህራም በማሳረጊያው “የካይሮ ቀጣይ ተስፋ አሜሪካ፣ ኢማራት እንዲሁም የተለያዩ ሀያላን ሀገራት የሚያሳድሩላት ጫና ነው” በማለት ፅሁፉን ቋጭቷል።

#የዓባይልጅ#eslemanabay#FinishTheGERD#HornofAfrica

Exit mobile version