Site icon ETHIO12.COM

ወያኔ (ሕወኃት) አሁንም ?

አሁንም አለ።
አሁንም ጠላት ነው።
አሁንም ለኢትዮጵያ ዋና ስጋት ነው።
አሁንም የጠላቶቻችን ጉዳይ አስፈጻሚ ነው።
አሁንም ኢትዮጵያን ለማፍረስ የሚሰራ አሸባሪ ቡድን ነው።
ባንዳነቱን ለአፍታም ልንዘነጋ አይገባም። ከፊታችን ገለል ስላለ ጠላትነቱ የቀነሰ ወይም የተረሳ አይደለም። አንዳንዶች ጥፋቱን ሆን ብለው አቅልለው የሚያሳዩ ሲሆን አንዳንዶች ግን ከግንዛቤ ክፍተት በአካል የማይታዩ ጉዳቶችን እንደ ጉዳት ያለመገንዘብ አዝማሚያ ይታያል።
ዛሬም ከዚህ ወያኔ ዘራሽ ችግር እንዳልወጣንና በቀላሉም እንደማንወጣ መገንዘብ ግድ ይላል።

ይህ ማለት አሁን ያለው መንግሥት የሚጠበቅበትን ተወጥቷል የሚል አንድምታ በፍጹም የለውም። በራሱ ርእስ ከወያኔ ጉዳይ ሳይዛነቅ የሚታይ ይሆናል።

ወያኔ በቅርቡ ጦርነት ያደረሳቸውን ጥፋቶች ለሌላ ጊዜ አቆይተን ለዛሬ ከወያኔ የአገዛዝ ዘመን ትሩፋቶች በጥቂቱ እንመልከት፤

1ኛ ሀገራዊ የአንድነት መሠረታችንን ንዷል። ከሀገር በላይ ለለት ለምንኖርበት ክፍለ ሀገር እንድንቆረቆር ከማድረግ አልፎ ኢትዮጵያዊነትንና የኢትዮጵያን ሰንደቅዓላማ እና ስም ዝቅ ለማድረግ ሰርቷል።

2ኛ የነገድ ጥላቻን አበል እየከፈለ በማስተማር አስፋፍቶ በጥርጣሬና በስጋት እንድንተያይ አልፎም እስከመገዳደል አድርሶናል።

3ኛ ከትግራይ በስተቀር የሁሉንም ክልሎች ዞንና ወይም ወረዳ በጎሳ ስምና ድንበር ከፋፍሏል። በጎሳም ወይም ነገድ ልዩነት አጋጭቶ አገዳድሏል።

4ኛ ትምህርት ስርዓቱ እንዲወድቅ አድርጓል።

5ኛ ስነምግባር እንዲወድቅ ወጣቱም በሱስ እንዲጠመድ አድርጓል።

6ኛ የስራ እድሎች እንዳይከፈቱና የስራ ምቹ ሁኔታ ከአንድ ነገድ ለተውጣጡ ደጋፊዎቹና ከሌላ ነገድ ለመለመላቸው ግብረአበሮቹ ብቻ እንዲሆን አድርጓል።

7ኛ ሕገወጥነት ሌብነት (ሙስና) አስፋፍቷል። ሀብት ወደውጪ አሽሽቷል።

8ኛ የእምነት ተቋማት ውስጥ ሰርጎ በመግባት በመከፋፈልና በማጋጨት አማኞች ለእምነታቸው ያላቸው መሰጠት እንዲሸረሸር ከማድረግ አልፎ ተቋማቱ በነገድ የተከፋፈሉ በውስጣቸውም ሌብነት/ሙስና ሳይቀር እየተሰማባቸው እንዲቀጥሉ በማመቻቸት፤ የእምነቱን የመሪነት ቦታ ለመያዝ ነገድ ወይም የፖለቲካ ወገንተኝነት እንዲታይ አድርጓል። የተለያዩ የእምነት ተከታዮችም በጥላቻና በጥርጣሬ እንዲተያዩ ሰርቷል።

9ኛ በክልሎች መካከል ያልተመጣጠነ የልማትና የኢንቨስትመንት ስርጭት እንዲኖር አድርጓል። በተቃራኒው አሳቢ በመምሰል በአዳጊ ክልሎች ማሳደግ ስም ያለመያዣ የኢንቨስትመንት ብድር በማመቻቸት ባንኮች እንዲዘረፉ አድርጓል።

10ኛ አማራን በልዩ ሁኔታ በሁሉም ነገዶች በጥላቻ እንዲታይ አድርጓል። ለዘር ጭፍጨፋ ለማመቻቸት ተቀጥላ ስሞች ሰጥቶታል። በነገዱ ላይ የሀሰት ትርክት ፈጥሮበታል። አካባቢውን እንዳያለማ አድርጓል። የባህል ወረራ በማካሄድ በኪነጥበብ ሳይቀር አማራው ጎስቁሎ፣ ኋላ ቀር ሆኖ፣ ልብሱ አረንጓዴና ዛጎል ያለበት ብቻ መስሎ እንዲታይ፣ በተከታታይ የኪነጥበብ ስራዎች መሳለቂያ በማስመሰል መሳል፣ ያልተሰሩ ት/ቤቶች ሪፖርት በማድረግ በጭራሮ መሀልና በዛፍስር “ማስተማር”; ሆን ብሎ ኤችአይቪ እንዲስፋፋ በማድረግ በፖለቲካው የራሱ ያልሆኑና ጥላቻ ያላቸውን ብቃት አልባ ግለሰቦች ጭምር በማስቀመጥ ተዘርዝሮ የማያልቅ ግፍ ከመፈጸሙም በላይ ከክልሉ ውጪ የሚገኙ አማርኛ ተናጋሪዎች (አማራዎች) ላይ ለህሊና የሚከብዱ ግፎችን ፈጽሟል።

11ኛ መረጃ የሌለው የሀሰት የኢትዮጵያ ታሪክ (ትርክት) ፈጥሮ ጽፏል።

12ኛ የተለያዩ ቋንቋ ከሚናገሩ ወላጆች የተገኙ በ10 ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ (በአንዳንዶች ግምት የኢትዮጵያን ሕዝብ ግማሽ ያህል የሚጠጉ) የፍቅር ፍሬዎችን በማይመጥናቸው ነውረኛ ስም በመጥራትና ክልል አልባ በማድረግ የሀገር አልባነት ስሜት እንዲያድርባቸው አድርጓል።

13ኛ በኦሮሞ ልጆች ላይ በገፍ መፈናቀል፣ ስደትና እስር ፈጽሟል።

14ኛ እሱን ያልደገፉ ግለሰቦች ንብረት እንዲወድም እንዲሰደዱ አድርጓል።

15ኛ መከላከያ ሠራዊታችንን በመበተን በምትኩ የሀገር ሳይሆን የአንድ ቡድን አስተሳሰብ (አብዮታዊ ዲሞክራሲ) ዘብ የሚሆን ኃይል አደራጅቷል።

16ኛ ፕሮጀክቶች ቶሎ ተጠናቅቀው ወደ አገልግሎት እንዳይገቡ አድርጓል።

17ኛ እንደ አብዛኞቹ የአፍሪካ አምባገነኖች የፖለቲካ ተቃዋሚዎቹን አሰቃይቷል፣ ገድሏል፣ የደረሱበት እንዳይታወቅ አድርጓል፤ አኮላሽቷል፤ አምክኗል።

ሕወኃት (ወያኔ) የምንጊዜም የኢትዮጵያውያን ጠላት ነው።

Abebaw Bogale

Exit mobile version