Site icon ETHIO12.COM

“የኢትዮጵያን ባህር ኃይል ለማዘመን ከሀገር ውጭና በሀገር ውስጥ የሚሠጡ ስልጠናዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ”

የኢትዮጵያ ባህር ኃይል በአዲስ መልክ ከተመሠረተ ጀምሮ የተለያዩ አቅም ፈጣሪ ስልጠናዎችን ከሀገር ውጭ እና በሀገር ውስጥ አባላቱን በማሠልጠን ላይ ይገኛል።

የኢትዮጵያ ባህር ኃይል ዋና አዛዥ ሬር አድሚራል ክንዱ ገዙ በብላቴ የኮማንዶ እና የአየር ወለድ ኃይል ማሠልጠኛ ማዕከል ተገኝተው የማሪን ኮማንዶ የሚሠለጥኑ የባህር ኃይል አባላትን ጎብኝተዋል።

ዋና አዛዡ የስልጠና ሂደቱን ተዘዋውረው ከተመለከቱ በኋላ እንደተናገሩት የማሪን ኮማንዶ ሠልጣኞች በማሠልጠኛ ማዕከሉ የሚሠጡ ስልጠናዎችን በድሲፒሊን፣ በሞራል እና በብቃት መወጣት አለባቸው።

እየተሠጠ ያለው ስልጠና ከሌሎች የሠራት ክፍሎች ጋር በመሆኑ የተሞክሮ እና የልምድ ልውጥ ለማድረግ ዕድል ይፈጥራል ያሉት ሬር አድሚራል ክንዱ ገዙ ያገኛችሁትን ዕውቀት ለሎች ለማካፈል ተግታችሁ ልትሠለጥኑ ይገባል ብለዋል።

ዋና አዛዡ አክለውም በስልጠና ላይ የሚገኙ የማሪን ኮማንዶ ሰልጣኞች ቀጣይ ለምንሠጣቸው ስልጠናዎች አቅም ፈጣሪ በመሆናችሁ ከማሰልጠኛው የምታገኙትን ዕውቀት አቅባችሁ ባህር ኃይልን ለማዘመን በምንሠራው ስራ ላይ የድርሻችሁን እንድትወጡ ከወዲሁ ልትዘጋጁ ይገባል ብለዋል።

የኮማንዶ እና አየር ወለድ ኃይል ማሰልጠኛ ማዕከል አዛዥ ኮ/ል ቦጃ አጋ በበኩላቸው የባህር ኃይል ማሪን ኮማንዶ ሰልጣኞች በድሲፕሊንም ይሁን በማንኛውም እንቅስቃሴ አርዓያ የሆኑ መሆናቸውን አንስተዋል።

በዕለቱም የባህር ኃይል ዋና አዛዥ ሬር አድሚራል ክንዱ ገዙ በኮማንዶ እና አየር ወለድ ኃይል ማሰልጠኛ ማዕከል ለሚገኙ አሠልጣኞች ምስጋና አቅርበዋል።

ተምትም ታደሰ
ፎቶግራፍ ገሰሰ ሙሉ

Exit mobile version