Site icon ETHIO12.COM

“በወልቃይት ጠገዴ ላይ የሚነሳ ማንኛውም ጠላት በብቃት ይመከታል፤ በጀግኖች ክንድ ይመታል”

ጀግኖች የሚበቅሉባት፣ ልበ ሙሉዎች ትጥቃቸውን የማይፈቱባት፣ ጠላቶች በቅናት፣ ወዳጆች በስስት የሚያዩዋት የጀግና ምድር ናት ወልቃይት። አሸባሪው ሕወሓት ሁሉጊዜ ይመኛታል። ወረራ ይፈፅምባት ዘንድ ተደጋጋሚ ሙከራ ቢያደርግም በወገን ጦር እና በሕዝቡ የጋራ ቅንጅት ከሽፏል።

በኢትዮጵያ ላይ ለሦስተኛ ጊዜ ጦርነት የጀመረው የሕወሓት ቡድን በወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ በተለያዩ አቅጣጫዎች ወረራ ፈጽሟል።

የወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞን ዋና አሥተዳዳሪ አሸተ ደምለው የወልቃይት ሕዝብ የሕወሓትን ፀረ ሕዝብነት ጠንቅቆ የሚያውቅና ለሽብር ቡድኑ የመረረ ጥላቻ እንዳለው ገልጸዋል። የወልቃይት ሕዝብ ዳግም ለባርነት እንዳይጋለጥ ሁልጊዜ በተጠንቀቅ እና በበቂ ዝግጅት እንደሚኖር ነው የተናገሩት።

የሽብር ቡድኑ ትንኮሳ ሲጀምር ሕዝቡ በቁጣ በመነሳት ከወገን ጦር ጎን እንደተሰለፈም ተናግረዋል።

የወልቃይት ጠገዴ ሕዝብ እፎይ የሚለው ጠላት ሙሉ ለሙሉ ሲጠፋ ብቻ እንደኾነም ገልጸዋል።

የወልቃይት ጠገዴ ሲተት ሁመራ ሕዝብ “ሞት አይቀርም ስም አይቀበርም” በማለት ጠላቱን አይቀጡ ቅጣት ለመቅጣት መነሳቱንም ተናግረዋል። ሕዝቡ ለጥምር ጦሩ አስተማማኝ ደጀን ሆኖ ታግሎ እያታገለ መሆኑንም ገልጸዋል።

የወልቃይት ጠገዴ ሕዝብ አካባቢውን በንቃት እንደሚጠብቅም ተናግረዋል።

ሊያጠፋው የመጣውን ጠላት ለመመከት በከፍተኛ ጥንቃቄ አካባቢውን እየጠበቀ መሆኑንም አስታውቀዋል።

የወልቃይት ጠገዴ ሕዝብ ጠላት የፈለገውን ወሬ ቢያወራ አይረበሽምም ነው ያሉት። የጠላትን ውሸትና ፕሮፖጋንዳ ጠንቅቆ የሚያውቅ መሆኑንም ገልጸዋል።

ባለፈው ዓመት ከ25 ጊዜ በላይ ሙከራ አድርጎ ሁሉም እንደከሸፈበት ያስታወሱት ዋና አስተዳዳሪው የወልቃይት ጠገዴን መሬት ጠላት ቢረግጥ ኖሮ ኢትዮጵያ አደጋ ውስጥ ትወድቅ እንደነበርም ተናግረዋል።

አሸባሪው የሕወሓት ቡድን እስከመጨረሻው ድረስ መጥፋት ይገባዋልም ነው ያሉት። መንግሥት ለሰላም የሰጠው አማራጭ የሚደነቅ ነው፤ ነገር ግን ሰላም የማይወደው ቡድን ለጦርነት መነሳቱንም ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ነቀርሳ ተነቀለ የሚባለው ሕወሓት ሲጠፋ ነው ያሉት ዋና አሥተዳዳሪው ሀገርን ለማዳን ጠላትን ለሚከላከለው ሠራዊት መላው ኢትዮጵያውያን ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።

ኢትዮጵያ እፎይ እንድትል የሽብር ቡድኑን ማጥፋት ግድ ይላልም ብለዋል። የወልቃይት ጠገዴ ሕዝብ ከወገን ጦር ጋር በመቀናጀት በየትኛውም አቅጣጫ የሚቃጣን ትንኮሳ ለመመከት ዝግጁ ነው ብለዋል። ትግሉ ኢትዮጵያን ለማዳን መሆኑንም ተናግረዋል።

በወልቃይት ጠገዴ ላይ የሚነሳ ማንኛውም ጠላት በብቃት ይመከታል፣ በጀግኖች ክንድ ይመታል ነው ያሉት።

ዘጋቢ:- ታርቆ ክንዴ ሁመራ: ነሐሴ 28/2014 ዓ.ም (አሚኮ)

Exit mobile version