Site icon ETHIO12.COM

የደብረፅዮን የጦርነት ታክቲክ 22

ታክቲክ 22 እዚጋ ነበር የተቀበረው። ከዛን ጊዜ ጀምሮ ደብረፂዮን አዘናግቶ የሚያርደው የዋህ በግ ሊገኝለት አልቻለም። በጣት የሚቆጠሩት ህወሃታዊ አዛውንቶች ምኞት ብቻ እስከ እለተ ቀብራቸው ይቀጥል ይሆናል፤ አርፋጁ የደብረፂዮን ታክቲክ-22 ውጤቱ የዜሮ ብዜት መሆኑን ድፍን ኢትዮጵያ ድምዳሜ ከሰጠበት ወራት ተቆጥረዋል።

የዓባይ፡ልጅ Esleman Abay

“the 48 Laws of power” የተሰኘው የደራሲ ሮበርት ግሪን መፅሐፍ፣ የአሸናፊነት 48 ዘዴዎችን ከፋፍሎ የያዘ ሲሆን፣ ደብረፂዮን የመዘዙት ቀቢፀ ተስፋዊ ካርታ ነው የሚባለው የሮበርት ግሪን ታክቲክ-22 የሚከተለውን ይዞ የምናገኘው ነው።

“ከባላጋራህ ስትነጻጸር ኃይልህ መዳከሙን በተገለፀልህ ማንኛውም ወቅት፣ ጦርነትህን አቁም፡፡ Use the surrender tactic: transform weakness into power የሥልጣን መወጣጫ መሰላልህ እንደተሰበረ ስታውቅ፣ እጅህን ስጥ! የሥልጣን ጆከር ካርታዎችህ እንደተበሉ ስታውቅ፣ ፈቅደህ ተማረክ፡፡
ለክብሬ፣ ለማንነቴ ብለህ አትዋደቅ፣ ቀን ካዘቀዘቀብህ እጅህን ስጥ፣ ዕድሜ ግዛ፣ እና አንሰራርተህ ውጋ!..የሚል..።
ይህ የደብረፂዮን ታክቲክ ነው ካልን ከዚሁ ጋር ጌታቸው ረዳ ከቀናት በፊት “ቂላቂል መግለጫ” እናስታውስ። ጌታቸው ረዳ ከሰማይ ጠቀስ የዛቻ ተራራው በአንዴ አቆልቁሎ ስለመሸነፍ ያወራበትን የቅርብ ጊዜ መግለጫው ታዲያ፣ በሮበርት ግሪን መፅሐፍ 21ኛው ታክቲክ ስር ልንመድበው የምንችለው ነው።
21ኛው የጦርነት ዘዴ ሮበርት ግሪን “በዙሪያህ ላሉት ቂል ምሰል፣ የዋህ ምሰል፣ ጮርቃ ምሰል፣ በምላስ የፈጠንክ፣ አላዋቂ ሰው ምሰል – Play a sucker to catch a sucker – seem dumber than your mark.”

“አንተ ከነሱ በላይ ውስብስብ ሴራ እንደምታውጠነጥን ማወቅ የለባቸውም፡፡ በተለይ በሥልጣን መሠላል ላይ እየወጣህ ባለህበት ወቅት ከበላይህ ያሉት ሰዎች ሁሉ አንተን ከእነርሱ የባሰ ባለዝቅተኛ አዕምሮ አድርገው እንዲገምቱ ብዙ ፍንጮችን ስጣቸው፡፡ ደካማ ጎንህን አሳያቸው፡፡ መጽሐፍ ስትጽፍ አስሩን ምዕራፍ ጻፉልኝ በላቸውና በስምህ አሳትም። በጀርባህ ይሳለቁብሃል፡፡ በጉራ ወዳድነትህ ያላግጡብሃል።”

“..ብዙውን ቀላሉን ነገር ጥራና ምን ባደርግ ይሻለኛል ብለህ አማክራቸው፡፡ የምትናገረውን ጻፉልኝ በላቸው፡፡ የምታውቀውን መንገድ ምሩኝ በላቸው፡፡ እንደዚያ ስትሆን ታማኝ ውሻቸው አድርገው ይስሉሃል፡፡ ይህንን አውቀህ ፍጹም ገራገርና ተላላኪ ደደብ ምሰል! የላቀ አዕምሮ እንዳለህ በፍጹም አይመጣላቸውም። ጨርሰው ይተዉሃል፡፡
አንተ ግን መጥረቢያህን ለመሞረድ በቂ ጊዜ ታገኛለህ፡፡ ምቀኛና ጠላት አይኖርብህም፡፡ እነሱ በአንተ ሲሳለቁ፣ በመጨረሻ ወቅቱን ጠብቀህ ትስቅባቸዋለህ..።” አሁን ወደ ደብረፅዮን የ22 ማዞሪያ የስልጣን ታክቲክ እንመለስ..
“..በጦርነት ወቅት እንደምትሸነፍ እያወቅክ የወታደሮችን ህይወት በከንቱ ማስፈጀት፣ ከአንተ ጋር ዳግም ማንም እንዳይሰለፍልህ ያደርጋል፡፡ በጅልነትህ ሲሳለቅብህ ይኖራልንጂ።”
“መሸነፍህ እርግጥ በሆነበት ጦርነት ኃይልህን ለማስጨረስ በእልክ ገብተህ አትፈራገጥ፡፡ እጅህን ስጥ! ለመማረክ የሚይዝህ ክብር አይኑርህ፡፡ ይህን የምታደርገው ውርደትን ተመኝተህ ሳይሆን፤ ራስህን ለነገ ለማትረፍ ነው፡፡ ሌላ አመቺ ጊዜ ለመጠበቅ…፡፡”

“..ትክክለኛ አጋጣሚውን ስታገኝ፣ ዛሬ ማርኮህ ምህረት ለሰጠህም ቢሆን አትራራለት፡፡ ባለውለታህ እንደሆነ በተግባር አረጋግጥለት፡፡ በቃል ደረጃ ተገዛለት፡፡ እሱን የሚያስቆጣ ነገር ላይ በፍፁም አትገኝ፡፡ የኃይል አሰላለፉን አጥና፡፡ ሙሉ ትጥቆችህን አደራጅ፡፡ የተሸነፈ ሰው ከመመኘት ይታቀብ የሚል ህግ የለም። በግላጭ የማትጋፈጠውን፣ በህቡዕ ታከናውነዋለህ፡፡ እጅ መስጠት የሥልጣን ማግኛ ታክቲክ ነው እንጂ የዘለዓለም ቃልኪዳን አይደለም፡፡ መጀመሪያ እጅህን ስጥ፡፡ ከዚያ ኃይልህን በህቡዕ ዘርጋ፡፡ በዚህም በዚያም የማይታዩ ገመዶችን እየሳብክ አሸናፊህን እረፍት ንሳው..”

“..ላይ ላዩን ለጠላትህ አጎንብሰህ ስገድለት፡፡ ልብህን ግን እንደ ብረት አጠንክር። ይህን ዘዴ በሚገባ ከተወንከው ጠላትህን ልቡን ትማርከዋለህ፤ ይዘናጋል። ያኔ የምታደርገውን ታውቃለህ! ይህን ታክቲክ ስታውቅ፣ ይህን አንተ የምትተውነውን ትወና የሚተውንብህ ሌላ አሸንፈኸው ምህረት ያደረግክለት የቀድሞ ባላንጣህ ቢሆንስ ኖሮ? ብለህ አስበው፡፡ ለሚያንሰራራ ጠላት፣ በፍጹም እጅህን ለምህረት አትዘርጋ፤ እንደጀመርከው ጨርሰው!
ይህ ሕወሃታዊ ታክቲክ የአገልግሎት ጊዜው ያበቃው ሰሜን እዝን ባጠቃበት 2013 ላይ ነበር። ለሶስት አስርት አመታት የፈፀማቸው ወንጀሎች ችላ ተብለውለት፤ ምርጫም ሆነ ቅርጫ ልቡ እንዳዘዘው ከማድረግ የከለከለው አልነበረም። አራት ኪሎ እንደ ጓደኛ ስታናግረው ከመቀሌ የነበረው የሕወሃት አፃፋ የሳይቦርጅ አይነት ነበር። ተከታታይ ዛቻው ሰሞን እዝን ወደ ማጥቃት ተሻገረ። በሶስት ሳምንት ይዞታውን ቆላ ተምቤን ለማድረግ ተገደደ። የተውሶ ጉልበት ተላብሶ በከፈተው ዳግም ወረራ ብዙ ጥፋትና ውድመትን ወለደ….የህወሃት ታክቲክ 22 እዚጋ ነበር የተቀበረው። ከዛን ጊዜ ጀምሮ ደብረፂዮን አዘናግቶ የሚያርደው የዋህ በግ ሊገኝለት አልቻለም። በጣት የሚቆጠሩት ህወሃታዊ አዛውንቶች ምኞት ብቻ እስከ እለተ ቀብራቸው ይቀጥል ይሆናል፤ አርፋጁ የደብረፂዮን ታክቲክ-22 ውጤቱ የዜሮ ብዜት መሆኑን ድፍን ኢትዮጵያ ድምዳሜ ከሰጠበት ወራት ተቆጥረዋል።

እስሌማን ዓባይ የዓባይልጅ

SurrenderTactic

Exit mobile version