Site icon ETHIO12.COM

የምርመራ ሂደት በአብዛኛው መጠናቀቁንና ወደ ክስ ሂደት ለመግባት በዝግጅት ላይ መሆኑን የግብረ-ኃይሉ ጽ/ቤት ተገለጸ

በሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል በተከሰተው ግጭት የተፈጸሙ ወንጀሎችን አስመልክቶ ሲካሄድ የነበረው የምርመራ ሂደት በአብዛኛው መጠናቀቁ ተገለጸ

በሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል ከተከሰተው ግጭት ጋር በተያያዘ የተፈጸሙ ወንጀሎችን አስመልክቶ ሲካሄድ የነበረው የምርመራ ሂደት በአብዛኛው መጠናቀቁ ተገለጸ፡፡

በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል በትግራይ፣ በአማራና በአፋር ክልሎች በተከሰተው ግጭት አውድ ውስጥ፤ ከሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ጋር ተያይዞ የተፈጸሙ ወንጀሎችን ከማጣራት፣ ተጎጂዎችን ከመጠበቅና ከመደገፍ አንጻር ስራዎችን ለማስተባበር የተቋቋመውና በፍትህ ሚኒስቴር ሚኒስትር በዶክተር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ ሰብሳቢነት የሚመራው የሚኒስትሮች ግብረ-ኃይል፤ በዛሬው ዕለት አራተኛ መደበኛ ስብሰባውን አካሂዷል፡፡

በግጭቱ ወቅት በአፋርና በአማራ ክልሎች በሰብዓዊ መብት ጥሰቶችና ከጾታዊ ጥቃት ጋር በተያያዘ የተፈጸሙ ወንጀሎችን አስመልክቶ ሲካሄድ የነበረው የምርመራ ሂደት በአብዛኛው መጠናቀቁን እና ወደ ክስ ሂደት ለመግባት በዝግጅት ላይ መሆኑን የግብረ-ኃይሉ ጽ/ቤት ኃላፊ ዶክተር ታደሰ ካሳ ገልጸዋል፡፡

እንደ ዶክተር ታደሰ ገለጻ በምርመራና በክስ ኮሚቴ የሚመራው 158 አባላት ያሉት የምርመራ ቡድን በአፋርና በአማራ ክልሎች ሲያከናዉናቸው የነበሩ ተግባራት ዝርዝር ሪፖርት ለመድረኩ ያቀረቡ ሲሆን፤ ወንጀሎች በምን አይነት መልክ እንደተፈጸሙና የምርመራ ግኝቶቹንም ምን ምን እንደሆኑ በሪፖርታቸው ላይ አካተው አቅርበዋል፡፡

ቡድኑ በምርመራ ወቅት የተለያዩ ማስረጃዎችን በቪዲዮና በዶክመንት አደራጅቶ መያዙ የተገለጸ ሲሆን፤ በጦርነት አውድ ውስጥ በርካታ ንጹሀን ላይ ያለፍርድ ስለተፈጸሙ የግድያ ወንጀሎች፣ ከባድ የአካል ጉዳት እና በሁሉም የዕድሜ ክልል ውስጥ በሚገኙ ሰዎች ላይ ስለተፈጸሙ ጾታዊ ጥቃቶች እንዲሁም በግዳጅ የመሰወር ወንጀሎች ስለመፈጸማቸው በሪፖርቱ ላይ የተመላከተ ሲሆን በንብረት ላይ የደረሱ ጉዳቶችም በምርመራ ግኝቱ ላይ ተካተዋል፡፡

ግብረ-ኃይሉ በተባበሩት መንግስታት የሰብዓዊ መብት ከፍተኛ ኮሚሽንና በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ጥምር የምርመራ ቡድን፤ የሽግግር ፍትህ አማራጭን ማጤን እና ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባ በሰጡት ምክረ-ሀሳብ መሰረት፤ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ መነሻ ረቂቅ ሰነድ ተዘጋጅቶ በሶስተኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ውይይት ማድረጉ ይታወሳል።

በዛሬው ስብሰባ ለፖሊሲው ግብዓት የሚሆኑ ሀሳቦች ላይ ውይይት በማድረግ ግብዓት መሰብሰቡን የፍትህ ሚኒስቴር አስታውቋል።

Exit mobile version