ETHIO12.COM

የአልሻባብ መስራች የነበረው አብዱላሂ ናድር ተገደለ

አሜሪካ በጥብቅ ስትፈልገው የነበረውና ያለበትን ለጠቆመ ሶስት ሚሊዮን ዶላር ለመሸለም የመደበችበት
አብዱላሂ ናድር በሶማሊያ ጦር መገደሉን የሀገሪቱ መንግስት አስታወቀ።

ሶማሊያ አልሻባብን ለማጥፋት መጠነ ሰፊ ጥቃት የከፈተች ሲሆን የሽብር ቡድኑ መስራች የነበረው አብዱላሂ ናድር መግደሏን አስታውቃለች።

የሶማሊያ መንግስት የጸጥታ ሀይል እየወሰደ ባለው ጥቃት ከዚህ በፊት በሽብር ቡድኑ ይዞታ ስር የነበሩ ቦታዎችን አስለቅቋል ተብሏል።

ከአልቃይዳ ጋር ግንኙነት እንዳለው የሚገለጸው አልሸባብ መስራች የነበረው አብዱላሂ ናድር ከዚህ በፊት የሽብር ቡድኑን ሲመራ የነበረው እና በቅርቡ የተገደለው አህመድ ድርዬን ለመተካት በሂደት ላይ እንደነበር ሮይተርስ ዘግቧል።

የሶማሊያ የኢንፎርሜሽን ሚንስቴር ባወጣው መግለጫ የአብዱላሂ ናድር መገደል አልሻባብ ከሶማሊያውያን ላይ እንደ እሾህ ተነቅሎ እንዲወጣ ያደርገዋል ብሏል።

ይህ የሽብር ቡድኑ አመራር እንዲገደል የሶማሊ ህዝብ እና ለዓለም አቀፍ ወዳጆች ላደረጉት ድጋፍ ምስጋናውን የሶማሊያ መንግስት አቅርቧል።

አልሻባብ ባለፉት 20 ዓመታት ውስጥ በ10 ሺህ የሚቆጠሩ ዜጎችን እንደገደለ የገለጸው የሶማሊያ መንግስት፤ ዓላማው ሶማሊያን እና ጎረቤት ሀገራትን ማወክ እንደነበርም ተገልጿል።

አልሻባብ ባሳለፍነው ሳምንት ብቻ ባደረሳቸው ሁለት የአጥፍቶ ማጥፋት ጥቃቶች የ16 ሰዎች ህይወት አልፏል።

በቅርቡ በተካሄደ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ወደ ስልጣን የመጡት ፕሬዝዳንት ሀሰን ሼክ መሀመድ አልሻባብን እንደሚያጠፉ ቃል ገብተው ነበር።

ይሁንና የአሁኑ የአልሻባብ የሽብር ቡድን መሪ የተገደለው በማን አጋዥነት እንደሆነ የሶማሊያ መንግስት የገለፀው ነገር የለም።

Via . Muktarovich

Exit mobile version