ETHIO12.COM

መንግስት ለትግራይ ሕዝብ በዓየር ወረቀት በትኖ “መጨረሻው ነው” ሲል ማሳሰቢያ አደረሰ

የኢትዮጵያ መንግስት ትላንትና ዛሬ በተለያዩ የትግራይ ከተሞችና አካባቢዎች በትግርኛ ቋንቋ የተጻፉ በራሪ ወረቀቶችን ማደሉን መረጃው ያላቸው አመልከቱ። በራሪ ወረቆቶቹን ማድረስና ማሰራጨት የተፈለገው ሕዝቡ ከሚቀሰቀሰው “የተሳሳተ ነው” የተባለ መረጃ ራሱን እንዲከላከልና በርጋታ ባለበት እንዲቆይ ወይም ከመንግስት ሃይሎች የሚሰጠውን ምክር ወቅቱ ሲደርስ እንዲከተል ለማዘጋጀት ነው። ይህንን አስመልክቶ ከትህነግ በኩል የተባለ ነገር የለም።

አየር ሃይል ከሰማይ የረጫቸው በራሪ ወረቀቶቹ «የትግራይ ህዝብ ራሱን ከሽብር ቡድኑ እንዲያርቅ፣ ልጆቹን ወደ ጦርነት እንዳይልክ እና ከመንግስት ጎን በመቆም ሰላሙን እንዲያረጋግጥ» የሚጠይቁና አቅጣጫ የሚሰጡ መልክቶችን የያዙ መሆናቸውን ወረቀቱ እንደተበተነ የሰሙ ገልጸዋል።

ማምሻውን የተበተነው ወረቀት የደረሳቸው ጠቅለል አድርገው ” … የተከበርከው የትግራይ ህዝብ የኢትዮጵያ መንግስትና ህዝብ ጦርነቱን አጠናቆ የትግራይን ህዝብ ነፃ ለማውጣት የመጨረሻው ምእራፍ ላይ ደርሷል። ስለሆነም መላው የትግራይ ህዝብ እራሱን ከውጊያ ቀጠናዎች በማራቅ ሰላም በሰፈነባቸው አካባቢዎች ሆኖ እራሱን እንዲያድን ጥሪ እናቀርባለን” የሚል አሳብ እንዳለበት ገልጸዋል። አቶ ጌታቸው ከትናንት በስቲያ የጦርነቱን ዓላማ ሲያብራሩ ” የትግራይ ሕዝብን ማጥፋት፣ መቸረስ ነው። ይህ አይሳካም። የሚሆነውን እናያለን” ሲሉ ለትግራይ ሕዝብ መልዕክት ማስተላለፋቸው አይዘነጋም።

በሌላ በኩል የመጨረሻውን መጀመሪያ የሚያሳዩ የግንባር መረጃዎች እየወጡ ነው። በርካቶችም በተመሳሳይ ምስል አስደግፈው ይህንኑ አጋርተዋል። አንዱ የትህነግ ወዳጅ አሌክ ዲዎል ነው።

– የመከላከያ ሠራዊትና ጥምር ጦሩ በትህነግ ታጣቂ ላይ እየወሰዱት ባሉት ፀረ ማጥቃት እርምጃዎች የመጨረሻውን መጀመሪያ የሚያበስሩ የድል ዜናዎች እየተቀዳጁ እንደሆነ እየተገለጸ ነው። የትህነግ ቅርብና እስትንፋስ ከሆኑት አሌክስ ዲዎል “የትህነግ ሰራዊት ፈራርሷል። አቅም አልባ ሆኗል” ሲል ምስክሩን ሰቷል። የሽሬን መያዝ አስመልክቶም “ቁልፍ ተነጥቀዋል” አይነት አሳብ ሰንዝሯል። ሁሉም ነገር ያበቃለት አድርጎ ባሰራጨው ጽሁፍ “ድረሱላቸው” ሲል ጥሪውን አሰምቷል። የሰላም ንግግሩ ልክ ኡሁሩ እንዳሉት በአስገዳጅ ቅድመ ሁኔታ ተግባራዊ እንዲሆን ተማጽኗል። ይህ ካልሆነ ሲል ልክ አቶ ጌታቸው እንዳሉት በተመሳሳይ የዘር ማጥፋት ሊካሄድ እንደሚችል አስፈራረቷል። ኢትዮጵያ በኢኮኖሚ እየተኮንታኮተች መሆኗን አመልክቶ የጊዜ ጉዳይ እንጂ የምትፈርስ አገር መሆኗንም በጽሁፉ ማብቂያ ላይ አካቷል። ሱሌማን አብደላ የሚከተለውን የግንባር መረጃ አትሟል። መጠነኛ ማስተካከያና የአርትኦ ስራ በመስራት አትመነዋል።

– በደቡብ ግንባር በሰሜን ወሎ ግዳን ወረዳ ወትወት፣ ሲሞንዛ፣ ማሆጎ፣ጀመዶ፣ ግራኝ አገው እና ዶጊያት የነበረው የትህነግ ጦር ከፍተኛ ጉዳት ደርሶበታል።፤ ቀሪ ኃይሉን ወደ አላማጣ አየር ማረፊያ ሸሽቷል።

– በራያ አላማጣ ግንባርም ተሰልፎ የነበረው የትህነግ ሃይል የከረረ ምት ስላርፈበት ዋጃን እየለቀቀ እና ከአላማጣ ከተማ በ10 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ቢበተንም ጥምር ጦሩ እየተከተለ እርምጃ በመወሰድ ላይ ነው። አላማጣ የሰዓታት ጉዳይ ሆናለች።

– በሰቆጣ ግንባር ጥራሬ ወንዝ ማዶ ላይ በነበረው ኃይል ላይ በተወሰደ የማጥቃት እርምጃ ተፈረካክሷል። ቆዝባ፣ መረዋ እና ዛታ ከተማዎችን ለመልቀቅ መገደዱም ታውቋል።

– በምዕራብ ግንባር አዲአርቃይ ከተማን አልፎ መጥቶ በነበረው የጠላት ኃይል በደረሰበት ጠንካራ ምት ጠጣ፣ ሲምንዛ፣ አዲአርቃይ ከተማ፣ ጃማ ወንዝ፣ ማይለሃም፣ ማይቃጫን፣ ኮሎፊያን አባማር፣ አዲጉባይ እና ቡያን ለቆ ወደ አቄስብሎ፣ ማይፀብሪ እና ዜሮ ዜሮ እንዲሻገር ተገዷል። ጥምር ጦሩ ወደፊት እየሄደ ማይጸብሪ አፍንጫ ደርሷል።

– በሰሜን ምዕራብ የነበረው የትህነግ ኃይል ከአዲዳሮ ተገፍቶ ወጥቷል። በዛላምበሳ በኩልም ዛላምበሳን ለቆ ፋዒ የምትባል ትንሽ ከተማ ላይ ሰፍሯል። በመሆኑም በዚህ አቅጣጫ ጥምር ጦሩ የአዲግራት ከተማን በቅርብ ርቀት ላይ እንዳለ ታውቋል።

መከላከያ የሚመራው ጥምር ጦሩ በተቆጣጠራቸው አካባቢዎች ሕዝብ ነቅሎ እንዲወጣ መመሪያ ቢሰጥም በተፍለገው መጠን ህዝቡ ተግባራዊ እያደረገው ኧንዳልሆነ ለማወቅ መቻሉን የተለያዩ ወገኖች እየገለጹ መሆኑንን የሱሌማን የተገኘው መረጃ ያስረዳል።

አሌክስ ዲዎል በቅርቡ ድርድሩን ቀን መግዣ ያደርገው መንግስት ጦርነቱን ሊጨርስ እንደሚችል ስጋቱን አስቀምጧል። አቶ ጌታቸው አጅግ በተረበሸ ስሜት ” ዓለም ዝም አለን” ሲሉ ቀለበቱ እየጠበበ መምጣቱን ገልጸዋል። አሌክስ አምልጦት ይሁን ድንገት በጽሁፉ ላይ ጦርነቱ በሁሉም አቅጣጫ በዚህ ፍጥነት ከሄደ የትህነግ ሰዎች ሊደበቁ ስለሚችሉ ለድርድር እንኳን መገኘት የማይችሉበት ሁኔታ ይፈጠራል። ይህ የሚሆነው ሆን ተብሎ ነው ሲል ገልጿል። የአፍሪካ ህብረትን አበክሮ የዘለፈው አሌክስ “አብይ አሕመድ ድርጅቱን ያዙታል” ሲልም ወቅሷል። እጅግ ብስጭት የተሞላበት የአሌክስ ጸሁፍን እዚህ ላይ ያንብቡ

የአቶ ጌታቸው እረፍት ያጣና መረጋጋት የጎደለው ማብራሪያ፣ የአሌክስ “ትህነግ ሃይሉ ፈርሶ ተበታትኗል” ምስክርነት፣ የኢትዮጵያ መንግስት ድምጽ አጥፍቶ ያሰበውን ግፍቶበት ለትግራይ ወገኖች “ተረጋጉ” የሚል አሳብ በበራሪ ወረቀቶች ማድረሱ፣ አሜሪካ በቆቦ በኩል ትህነግ ዳግም ወረራ መጀመሩን በይፋ አውግዛ መጻፏና የሰላም ጥሪ ብቻ ማስተላለፏ፣ በትቅሉ ነገሮች ወደ መቋጫቸው እያመሩ ለመሆናቸው ማሳያ እንደሆነ ከእየአቅጣጫው እየተሰማ ነው።

ሱሌማን አብደላ

Exit mobile version