Site icon ETHIO12.COM

ካድሬዎች በዛብን በቃን !! አገርም ጫንቃዋ ይርዳል፤

ታላቁ መጥሃፍ ” የማያስተውሉ ይገለበጣሉ ይላል” ሲቀጥልም “ውሻ ወደ ትፋቱ እንደምኪመለስ …” ሲል ያስጠነቅቃል። እስካሁን በብሄር ቆዳ ተጠቅልለው ማስተዋላችንን ሰርቀው ካድሬዎች አባሉን። እያባሉን ዘረፉን። አገራችንን አነተቧት። አሁንም “ልታልቅ ነው” ነው እያሉ ወገንን እየማገዱ ነው። “በቃን” እንበል። ለማን ሲባል ነው ትውልድ የሚረግፈው? የትግራይ ሕዝብ ምን ስለሆነ ነው ዙሪያው ሁሉ ጠላት እንደሆነበት አምኖ እንዲኖር የሚፈረድበት? ትናንት ፣ ዛሬም፣ነገም ሆነ ወደፊትም የትግራይ ሕዝብ አካል ነው። የተለየ ወዳጅ፣ የተለየ ጠላት የለውም። ካድሬዎች እባካችሁን በቃችሁ፤ ይህ ህዝብ ከወዳጆቹ ጋር ይኑርበት። ቃዥታችሁ በማይሆን ምኞት አታማቁት። ነገሩ እያከተመ ነውና ለሰላም እጃችሁን አንሱ። መንግስትም ለሰላም ግፋበት። ሁሉም ወገን ለሰላም አርበኛ ይሁን!! እንተባበር!!

ካድሬ ትናንት ባለው የማያፍር፣ ሚዛኑ የወለቀ ባዶ ነገር ነውና ሁሌም ይጮሃል። በሰዓታት ውስጥ ከራሱ ጋር ሲጣላና ሲዘባርቅ ላፍታ እንኳን አይሰማውም። ምክንያቱም ሚዛኑ ወልቋል። ካድሬዎች ሚዛናቸው ስለወለቀና በተሰበረ ሚዛን ባዶ ሆነው ስለሚኖሩ ሁሉም እንደ እነሱ ይምስላቸዋልና በየቀኑ ይተረተራሉ። ትውልድ ግን ይሰማል። እናቶች ይሰማሉ። አባቶቻችን ይሰማሉ። ይታዘባሉ። ይንቃሉ። እንደ ምናምንቴ ቆጥረው “እበት ውስጥ እንደሚፈጠር ትል” አድርገው በልቡናቸው ይፈርጃሉ። ከነዚህ ሁሉ ቀልባና ፍርድ፣ እርግማንና ጥላቻ ማለጥ የሚቻል የሚመስላችሁ ከቀን ተማሩ። የትናንት ሃያሎች ተዋርደዋል። የትናንት ነበሰ በላዎች ወድቀዋል። ዓለም ትዕቢተኞችና የደም ባለ ዕዳዎች አወዳደቃቸው እንዴት እንደሆነ በቅርብም በርቀትም አሳይታለችና ነገም ምንም አዲስ ነገር የለም።

በግልጽ ቋንቋ የኢትዮጵያ ህዝብ ሚዲያ የለውም። የሚዲያ ባለሙያ የለውም። በሳልና አሳብ ያላቸው ፖለቲከኞች የሉትም። እሪ በከንቱዎች እንጂ ተስፋ የሚጣልባቸውና ያሻግራሉ የሚባሉ አማራጭ ተቀናቅኝ ድርጅቶች የሉትም። ከዘለፋና ከሴራ የጸዱ ፖለቲከኞች አለመኖራቸው ሳያንስ የእከሌ ከከሌ ሳይባል በየዕመነት ቤቱ የሚታየው ሁሉ እንደ አገር የመክሸፋችን ማሳያ እንጂ ተስፋ የሚሰጡ አይደሉም። እናም የአገሪቱ ፖለቲካ ብቻ ሳይሆን በጎ እሴቶቿ በአመራር ደረጃ ነትቧል። ጥቂት እጅግ ጥቂት እዛም እዚህም ከሚታዩት በቀር በጅምላ “ሁሉም ዜሮ” ነው። ያልጠፋነው በህዝብ ጥንካሬና የኖረ መስተጋብር እንጂ እንደ ተቋሞቻችን ቢሆንማ ኖሮ ይህኔ አመድ ነበርን።

በኢትዮጵያ ከዘጠና ሰባት ምርጫ ጀምሮ ሚዲያው ጠንባራ ነው። የመንግስቱ የካድሬ ቦቲ አድርጎ የሚዳፍቅ፣ የግል የሚባለው ተቃዋሚ ወይም ተላላኪ፣ ሻል ያሉ የሚባሉት ደግሞ አጅንዳ ቀራጮች እንደነበሩ መካካድ አይቻልም። አሁንም ጥቂት በግለሰብ ደረጃ “አበጃችሁ” የሚባሉ ከመኖራቸው ወይም ከመታሰባቸው በቀር እንደ ሚዲያ መሃል ላይ መቆም እንኳን ባይቻልም ለመቆም የመሞከሩ ፍላጎት እንኳን አለልነበረም። ይህ እንደ አገር አሳዛኝ ነው። ዛሬ ደግሞ ብሶበታል።

ማንም እየተነሳ ተንታኝ፣ አስተንታኝ በመሆን ሚዲያን የዲጂታል ልመና መድረክ አድርገውታል። መረዳት የሚገባቸው የሉም ባይባልም፣ አሁን አሁን የምናየው እለት እለት መንግስትን ብቻ እያሙ መቀለብ የለመዱ ” ዲጂታል የኔ ቢጤዎች”፣ የአገርና የብሄራዊ ጥቅም ጉዳይ ከከርስ አሳንሰው በክፍያው መጠን ብሄር ውስጥ ተወሸቀው መርዝ የሚረጩ፣ የአቅም ማነስና ጨዋነት እላያቸው ላይ ቤት የሰራባቸው፣ በድምሩ ሟርትና ለቅሶ የሚራራቡ መበራከታቸውን ነው። እንዲህ ሲባል መንግስት ለምን ይነካል ለማለት ሳይሆን ሚዲያውና የሚዲያው ደረጃ ያለበትን ለማመላከት ነው።

እርግጥ ሰላም በአንድ ወገን ፍላጎት ብቻ አይመጣም። ቢትዮጵያ ጉዳይ ፈትፋቹ ብዙ ነው። ዋናዎቹ የዓለም ባለውቃቢዎችና የአናው መንፈስ ጌቶች፣ የተገዛው ፣ የግዢ ግዢው፣ ልክስክስ ተከፋዩ … የማይወራረድ ሃብት የሚዘው ቀበኛ … ሰላም እንዲሰፍን ትግሉ ከባድ የሚሆነው ለዚህ ነው። ተያያዥ ፈንጂው በየሰፈሩ ተቀብሮ ስለኖረና አሁንም ለመቅበር እየተሞከረ በመሆኑ ሁሉም ዜጋ ለሰላም ሲል “እምቢ ሊል ይገባል። አለያ አይሆንምና እምቢታችን መዳኛችን ነው።

ከሁሉም በላይ በመረጃ እጥረት የሚደናበረውና የጀግና ጥማት ያለበት ዲያስፖራ የተሳፈረበትን የቅዠት ጀላባ ላስተዋለ ነገሩ አሳሳቢነቱ ይብሳል። ከአገር ቤት የመጣውን ሁሉ በሚዲያ ስም እያጀገነ ሲሸልምና ሲቀልብ የሚኖረው ዳያስፖራ፣ አድሮ እነማን ጉድ እንዳደረጉት አይቶ እንኳን አይነቃም። ላፍታ ከማሰብ ይልቅ ዝም ብሎ እየተነዳ አገር አልባ ሊያደርጉት ለተነሱ እባቦች መርዝ መጋቻ ሃብት ይሰጣል። ይህ አካሄድ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን ቀውስ የሚያባብስ እንደሆነ ለማስታወስ እንጂ ንብረት ሸጠው የሰጡና ስልጣን ቃል የተገባላቸው እንደነበሩ የሚያውቅ ያውቃል። ዛሬ ባዷቸውን የሚያጨበጭቡትን ቤታቸው ይቁጠረው። ይህ ሲባል አብዛኞች የሚኮራባቸው የኢትዮጵያ ልጆች መኖራቸው ሳይዘነጋ ነው።

ላለፉት አራት ተከታታይ ዓመታት ኢትዮጵያ ሞትን በየዓይነቱ አስተናግዳለች። እድሜ ለዘመኑ ሁሉም ዓይነት የሞት፣ የስቃይ፣ የስደት… ቡፌ በኩራትና በንግድ፣ በሴራና ሴረኞች፣ በገባቸውና ባልገባቸው፣ በተኩላዎችና ዲቃላዎቻቸው፣ በተገዙና የግዢ ግዢ በሆኑ … እንደየ ቁማናቸውና ዓላማቸው ተሰፍሮ ተረጭቶልናል። ታልሞና ታቅዶ የምስኪኖች ሞት በኩራት ሲቆመበት አይተናል። ይህ ታሪክ አይደለም። ይህ ትውልድ እያየ፣ እየሰማ፣ እየኖረው ያጣጣመው ሃቅ ነውና ተዋናዮቹ ሊክዱት አይችሉም። በፍጹም። ተውንያኖቹ ብቻ ሳይሆኑ ተዋንያኖቹን የሚቀልቡትም ከዚሁ የግፍ መዝገብ ሊፋቁ አይቻላቸውም።

በብሄር ስም ህዝብ ጉያ ውስጥ ተወሽቆ በደም የሚጫማለቅን አውሬ ማንም ይሁን ማን መታገስ ሰላምን አያመጣም። ይልቁኑም ሌላ ትውልድን ይማግዳል። እናም ፍትህ ያለበት ዕርቅ ይሰፍን ዘንድ ፍትህ ወዳዶች እንሁን። ፍትህ አካባሪዎች እንሁን እንጂ በዘር ቆጠራ ወንጅልን ይማናሰላ ከሆነ ከደም አዙሪት እስከወዲያኛው አንወጣም። ማንም ሆነ ማን በሰራው ወንጀል መጠን፣ ከሃጂም ከሆነ በክህደቱ ልክ ትውልድ እንዲማርበት ፍት እንዲበየን አቋም እንያዝ። በዚህ ጉዳይ ልምድ ያላቸው ዜጎቻችን አሉና እነሱን ወደ መድረክ እንጋብዝ። ከሰበር ዜና ጫጫታ በማላቀቅ ሰላም ፍትህን ታነግስ ዘንድ ጫና እንፍጠር

ምስንኪኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ እገሌ ከገሌ ሳይባል በመርዘኞች ሞት እየተመረተለት፣ ስደት እየተፈርደበት ተሰቃይቷል። ያልተሰደዱትም ዜጎች ቢሆኑ በሚሰሙት ልባቸው ተሰብሯል። መፈጠርን እስኪጠሉ ድረስ የጭካኔ ጥግ በየዕለቱ እየተጫነባቸው ኢኮኖሚውን ሰንጎ በያዘው የሴራ ድር ሳቢያ የኑሮው ክብደት ጋር አጉብጧቸዋል። እውነት እንነጋገር ከተባለ ኢትዮጵያ ላይ የተፈጸመው ሁሉ አሳፋሪ፣ አንገት የሚሰብር፣ ረብ የለሽ፣ የከርስና የዝርፊያ አበላ ውጤት ነው። የህዝብን ስቃይ፣ ሞትና ስደት፣ የህጻናትን ዋይታና ጠኔ ለከርስና ለስልጣን መጠቀሚያ ከማድረግ በላይ ወራዳነት የለም። እገሌ ከገሌ ሳይባል በደም የሚነግዱ ህሊና ቢሶች ምንም በማያወቀው ህዝብ ልቡና ላይ ጥላቻ የሚያመርቱ ሁሉ ከዚህ ዘመን ትውልድ ህሊና አይጠፉም። ያልፋል ግን አይረሳም። እንደውም ያስፈራል።

ከለውጡ ጊዜ በፊትም ሆነ በሁዋላ እጃቸው በደም አበላ የተነከረ፣ ከደምና ከደም አዙሪት ውጭ ምንም ሌላ ነገር ማስብ የማይችሉ፣ መቼ ከደም አበላ ውስጥ እንደሚወጡ፣ ወይም ” ደም በቃን” እንደሚሉ ሲታሰብ ጭላንጭሉም አይታይም። እንደውም አጀንዳቸውን እያሰፉና ድራማ ቀጣይ፣ የማይቆም፣ ተከታታይ መዝናኛ ፊልም እያደረጉ በምዕራፍ እየከፋፈሉት ነው። እገሌ ከገሌ ሳይባል የደም ነጋዴዎችን ግብርና ትራፊ እየቃረሙ በንጹሃን ስቃይ የሚያተርፉ፣ የአገር እድፎች ልክ እንደ ኳስ ግጥሚያ እከሌ እዚህ ገባ፣ እከሌ እዚህ ደረሰ በሚል ሚና ለይተው የወገንን ደም በሰበር ዜና የዩቲዩብ ሳንቲም መልቀሚያ አድርገውታል።

ካድሬ ትናንት ባለው የማያፍር፣ ሚዛኑ የወለቀ ባዶ ነገር ነውና ሁሌም እንደ ይጮሃል። በሰዓታት ውስጥ ከራሱ ጋር ሲጣላና ሲዘባርቅ ላፍታ እንኳን አይሰማውም። ምክንያቱም ሚዛኑ ወልቋል። ካድሬዎች ሚዛናቸው ስለወለቀና በተሰበረ ሚዛን ባዶ ሆነው ስለሚኖሩ ሁሉም እንደ እነሱ ይምስላቸዋልና በየቀኑ ይተረተራሉ። ትውልድ ግን ይሰማል። እናቶች ይሰማሉ። አባቶቻችን ይሰማሉ። ይታዘባሉ። ይንቃሉ። እንደ ምናምንቴ ቆጥረው “እበት ውስጥ እንደሚፈጠር ትል” አድርገው በልቡናቸው ይፈርጃሉ። ከነዚህ ሁሉ ቀልባና ፍርድ፣ እርግማንና ጥላቻ ማለጥ የሚቻል የሚመስላችሁ ከቀን ተማሩ። የትናንት ሃያሎች ተዋርደዋል። የትናንት ነበሰ በላዎች ወድቀዋል። ዓለም ትዕቢተኞችና የደም ባለ ዕዳዎች አወዳደቃቸው እንዴት እንደሆነ በቅርብም በርቀትም አሳይታለችና ነገም ምንም አዲስ ነገር የለም።

ምን ይሁን?

ይብቃ!! የፈሰሰው ደም፣ የጎደለው አካል፣ የረገፈው የሰው ዘር ቀላል አይደለም። የሰው ልጅ ረግፏል። አሁን ይብቃ!! ፍትህ ወደሚሰፍነበት አግባብ እናምራ። ወንጀል የሰሩ ሁሉ የሚዳኙበት ዕርቅ ይካሄድ ዘንድ ጫና እናድርግ። በአንዱ ሞት እየስቁ በሌላው ማልቀስ የትም አይደርስምና ንጹሃንን ከሴረኞች እንለይ። በእውነት ኢትዮጵያ ላይ የሆነው እጅግ ክፉ ነው። አገሪቱም ታንቃለች። ኢትዮጵያ በርታቷ ይደንቃል። ግን ለሁሉም ገደብ አለው። የትግራይ ህዝብ፣ ከወንድምህ በላይ ወዳጅ የለህም። አማራው፣ ኦሮሞው፣ ሶማሌው፣ ደቡቡ፣ ጋምቤላው ወዘተ ሁሉም ክትግራይ ህዝብ የሚብስበት ሌላ ወንድም የለውም። የትግራይ ህዝብ እንደ ህዝብ ኢትዮጵያ ነው። ትግራይ እንደ አገር ኢትዮጵያ ናት። ኢትዮጵያ ስንል ትግራይም፣ የትግራይም ህዝብ ነው። ለትግራይ ህዝብ ድፍረትን በማላበስ ከተዘራበት ፍርሃቻ እናድነው። ከዚህ ህዝብ የወጣችሁ ምሁራንና አክቲቪስቶች ተባብረን እንስራ። የኢትዮ12 ዝግጅት ክፍል ይህን ጥሪ ያቀርባል። የተዘራውን የክፋት ዘር እናምክን። ሰላም ይወርድ ዘንዳ ተናበን እንስራ። የካድሬዎችን ረብ የለሽ ቅጥፈት ከመጋት እንለይ። አሁንም ይበቃ ዘንድ አንትጋ። የትግራይ፣ የአማራ፣ የአፋር እናቶች “እፎይ” ይበሉ። እነሱ እፎይ ይበሉ። እነሱ እፎይ ካሉ ወደፊት ችግሩ ራሳቸው ይፈቱታል።

መረን የወጣውን ሚዲያም ልጓም ያብጅ። በውጭ ሆናችሁ በየቀኑ የፈጠራ ትርክት የምታመርቱ እባካችሁን አቁሙ። ሰራትችሁ ብሉ። ለልጆቻችሁና ለሚስቶቻቸሁ የልመና ገንዘብ እየቀለባችሁ ወደፊት “የለማኝ ልጅ” የሚል ስም ባለቤት ታደርጓቸዋላችሁና ይብቃችሁ። እስካሁን የሰበሰባችሁት ይበቃል። ምን እንኳን ሚዛነ ሰባራ ባዶ ካድሬ ብትሆኑም ከሴት ተወላዳችኋልና ነብሰ ጡሮች ያሳዝኗችሁ። እየለመናችሁ የማትሽቀረቅሯቸው ሚስቶች አሏችሁና ሴቶች ያሳዝኗቹህ። ለቀሪው ህይወታችሁም ወደ ቀልባችሁ በመመለስ ቀሪውን ጊዜያችሁን እንደሰው ሚዛናችሁን በመጠገን ደግ ስራ ሰርቶ ለማለፍ ተጠቀሙበት። ሞት ይበቃ ዘንድ፣ ገዳዮች ለፍርድ ይቀርቡ ዘንዳ ሚዲያዎች ከሰበር ዜናና ከሳንቲም ለቀማ በላይ የሆነውን ህዝብ እናስብ። ኢትዮጵያ ተጫጭኗታል። ኢትዮጵያ የልብ ምቷ አይሏል። ኢትዮጵያ ከውስጥም ከውጭም እየተለበለበች ነው። ከሳቸውን ያስቀደሙ በየአቅጣጫው እየበሏት ነው። በጥቂቶች ድካምና በአብዛኛ ህዝቧ ጸሎትና ደግነት ተደግፋ እንጂ … ሰላም ይስፈን!! በቃ!!

Exit mobile version