Site icon ETHIO12.COM

የአዋሽ-ወልዲያ-ሀራ ገበያ የባቡር ፕሮጀክትን ሥራ እንቅስቃሴ መጀመሩን ኮርፖሬሽን አስታወቀ

በአሸባሪው ህወሓት ውድመት እና ዘረፋ የደረሰበትን የአዋሽ-ወልዲያ-ሀራ ገበያ የባቡር ፕሮጀክትን ወደ ሥራ ለማስገባት እንቅስቃሴ ተጀምሯል

በአሸባሪው ህወሓት ጉዳት፣ ውድመት እና ዘረፋ የደረሰበትን የአዋሽ-ወልዲያ-ሀራ ገበያ የባቡር ፕሮጀክትን ወደ ሥራ ለማስገባት እንቅስቃሴ መጀመሩን የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን አስታወቀ።

የባቡር መስመሩ የሽብር ቡድኑ በከፈተው ጦርነት ምክንያት ከፍተኛ ጉዳት የደረሰበት በመሆኑ ፕሮጀክቱን እያከናወነ ያለው ተቋራጭ ለተበላሹ፣ ለተዘረፍት እና ለወደሙ ንብረቶቹ ካሣ መጠየቁን ኮርፖሬሽኑ አስታውቋል።

ኮርፖሬሽኑ የተቋራጩን ጥያቄ ለመመለስ ብሎም አጠቃላይ የባቡር ሥራውን ለማስቀጠል ቅርንጫፎችን በመክፈት እና የጠፉ እና የወደሙ ንብረቶችን በመለየት በየአካባቢው ጥናት እያደረገ መሆኑን ዛሬ በሰጠው መግለጫ አስታውቋል።

270 ኪሎ ሜትር የሚሸፍነው የአዋሽ-ኮምቦልቻ የባቡር መስመር በአሸባሪ ቡድኑ በከፋ ሁኔታ ጉዳት እንደደረሰበት ተገልጿል።

የአዋሽ-ኮምቦልቻ የባቡር መስመር 99 በመቶ ከ3 ዓመት በፊት ተጠናቆ የነበረ፣ ነገር ግን በኃይል እጥረት ምክንያት የዘገየ መሆኑንም በኮምቦልቻ በተሰጠው በመግለጫው ተጠቅሷል።

እስካሁን በተደረገው ጥናት የአዋሽ-ኮምቦልቻ የባቡር መስመር በአሸባሪው የህወሓት ቡድን ከፍተኛ ዘረፋ፣ ውድመት እና ጉዳት እንደደረሰበት ተገልጿል።
50 በመቶ ተጠናቅቆ የነበረው ከወልዲያ መቀሌ የሚወስደው የባቡር መስመርም ጉዳት እንደደረሰበት በጋዜጣዊ መግለጫው ተጠቅሷል።

የደረሰውን ውድመት አስተካክሎ ወደ ሥራ እንዴት መግባት ይቻላል በሚለው ላይ ጥናቶችን በማካሄድ በየአካባው ያሉ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶችን እየከፈቱ ዳግም ሥራ ለማስጀመር በንግግር ላይ መሆናቸውን የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ምክትል ሥራ አስፈጻሚ መግለፃቸውን ኢቢሲ ዘግቧል።

Exit mobile version