Site icon ETHIO12.COM

ትህነግ ትጥቅ ለመፍታት ወሰነ – ቴዎድሮስ አድሃኖም አብይ አህመድን በስልክ ተማጸኑ፤ አዲግራት መከላከያ መዳፍ ገባች

አደራውን ለባለ አደራው ሰጥተው የልማት ስራዎችን እየተዘዋወሩ የሚመለክቱትና የአረንጓዴ ዘመቻ መመሪያ እየሰጡ ያሉ አብይ አሕመድ ከአድሱ ዓመት ጀምሮ የወትሮ ጭንቀትና ያለመመቸት ስሜት ፊታቸው ላይ አይታይም። በመግስት የዘመኑ ዕቅድ ላይም በተያዘው ዓመት አስተማማኝ ሰላም እንደሚሰፍን ተመልክቷል። አብይ አህመድ ለበዓላት ባስተላለፉት መልዕክቶቻቸውና በፕሮጀክት ምረቃ ላይ “አትተራተሩ የሰሜኑ ጦርነት ያበቃል” ብለዋል።

“አሁን” ሲሉ መረጃ የሰጡ ወገኖች ” አሁን የሰኞው ንግግር ልክ እንደ 1991 ድርድር ዋጋ የለውም። ምክንያቱም የትህነግ አመራሮች ጊዜ የሚፈጁበት አንዳችም የድርድር ቀብዲ የላቸውም” እነዚህ ወገኖች ምን አልባትም ውጪ ያለው አካል ካልሆነ በስተቀር ከትርግራይ ወደ ደቡብ አፍሪካ የሚያመራ ሃይል የለም ባይ ናቸው። ቢኖርም ለውጥ አያመጣም። ቴዎድሮስ አድሃኖም ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ ጋር ደውለው መማጸናቸርው ተስምቷል። ምላሽም አግኝተዋል።

ከመቀሌ ውጪ ቀሪዋ ትልቅ ከተማ አዲግራት መከበቧን የሚናገሩ ወገኖች ዛሬ ማለዳ ላይ በጥምር ጦሩ እጅ መውደቋን እየገለጹ ነው። ይህንኑ ተከትሎ በአዲስ አበባና በውጭ አገራት የሚገኙ የትህነግ ደጋፊዎች ” ለዚህ ነው እንዴ ይህ ሁሉ ስው ያለቀው” የሚል ጥያቄ የትህነግ አመራሮች ላይ እያነሱ እንደሆነም ተሰምቷል። ጥያቄው እየተነሳ ያለው ትህነግ ዋስትና ጠይቆ በሰላም ትጥቅ ለመፍታት እየተማጸነ መሆኑንን በውስጥ ለውስጥ ግንኙነታቸው መስማታቸውን ተከትሎ ነው።

የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ቴዎድሮስ አድሃኖም ” የዲፕሎማሲ ቃላቶች አልቀውብኛል። እኔ ተጋሩ ነኝ። ጄኖሳይድ ጠብቁ …” ሲሉ በተናገሩና ቪዲዮው በተሰራጨ የቀናት ልዩነት ውስጥ ስልክ ደውለው በሰላም ትጥቅ የሚፈቱበትን ሁኔታ እንዲመቻች መጠየቃቸው ትህነግ በአቋም ደረጃ ትጥቅ ለመፍታት መወሰኑንን ተከትሎ ነው። ጠቅላይ ሚንስትሩ ጥቂት አድምጠው ለዶክተር አድሃኖም ምላሽ ሳይሰጡ እንዳሰናበቷቸው በስፍራው የነበሩ ለኢትዮ12 ነግረዋል።

የመንግስት ሃይሎች በገቡባቸው ከተሞች ሕዝቡ ከተነገረውና ይሆናል ብሎ ከጠበቀው በተቃራኒ ስለተደረገለት፣ የተቋረጡ አገልግሎቶች ዳግም እንዲጀመሩ ርብርብ መጀመሩ፣ በየመጋዘኑ የተከማቸ እህል እንዲከፋፈል መደረጉ፣ በትግራይ ነገሮችን እንደቀየረና ከአካባቢው የሚወጡ መረጃዎች ይጠቁማሉ።

“ከውጭም ሆነ ከውስጥ በትህነግ ተስፋ የቆረጡ ቁርጠኛ አቋማቸውን በገሃድ ባያስታውቁም፣ ነገሮች ሁሉ መገለባበጣቸውን እያመኑ ነው” ሲሉ የሚናገሩ፣ በዚህ ስሜት ላይ የመንግስት ጦር አዲግራትን ከተቆጣጠረ በደቡብ አፍሪካው ንግግር ትህነግን ከሚወክሉ አካላት ጋር ምን ዓይነት ስምምነት እንደሚደረግ ከወዲሁ መገመት አዳጋች እንዳልሆነ እየገለጹ ነው።

ትህነግ ዛሬ ላይ መሟገቻ፣ ማኩረፊያ ወይም መነጋገሪያ አጀንዳ ሊያቀርብ አለያም ሊመርጡ እንደማይችሉ በመረዳት ነገሩ እንዳበቃለት የሚገልጹ እ ኤ አ 1991 ለንዶን ላይ ከኢህአዴግ ጋር ድርድር ሲደረግ አሜሪካኖች በጓሮ የኢትዮጵያ ጦር ጠመንጃውን እንዲያወርድ አስደርገው ነበር። ድርድሩ ሲደረግ ከሰሜኑ አካባቢ ውጭ ያለው የአገሪቱ ክፍል ሰላም ነበር። ነገር ግን መንግስት ራሱ ላይ ሽንፈት እንዲያውጅ ተደርጎ የትህነግ ሃይሎች በቀላሉ ሰላምና መረጋጋት ኮሚቴ በማቋቋም ስልጣናቸውን እንዳጠነከሩ በማስታወስ በርካቶች የነገሮችን መመሳሰል ከልዩነቱ ጋር አጣምረው እየገለጹ ነው።

ልዩነቱ መንግስት የትግራይን ሰባ ከመቶ በላይ ተቆጣጥሮ ነጻ የማውጣት ስራውን እየገፋበት ነው። አሁን ላይ ጥምር ጦሩ አዲግራትን ተጠግቷል። ከትህነግ ወገን በይፋ መግለጫ ባይወጣም አክሱምና አደዋ አልተያዙም የሚል ማስተባበያ ቢያንስ በቢቢሲና በቪኦኤ ወይም በጀርመን ድምጽ አላሰማም።

ጦሩ አሁን ላይ ካለው ግስጋሴ አንጻር በደቡብ አፍሪካ በሚካሄደው ንግግር ትህነግን የሚወክሉ ሃይሎች ማስቀረት የሚችሉት ነገር ቢኖር ሞት እንዲቀንስ በይፋ ትጥቅ በማውረድ የትግራይ ህጻናት ወደ ሰላማዊ ኑሯቸው እንዲመለሱ ጥሪ ማድረግ ብቻ እንደሆነ በስፋት እየተሰማ ነው። ይህንንም ለማድረግ ምን አልባትም በውይይቱ ይሳተፋሉ የተባሉት የውጭ ክንፉ አመራሮች እነ አምባሳደር ብርሃነና የቲዲኤ ሃላፊ አቶ አክሊሉ ከዚህ አንጻር ለራሳቸው የሚሆን ታሪካዊ ውሳኔ ሊያስተላለፉ እንደሚችሉ ይጠበቃል።

የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር በሚል ስያሜ ሃያ ሰባት ዓመታት ስልጣን ላይ የነበረው ትህነግ፣ ያለው ተዋጊ ሃይል መወላለቁን አሌክስ ዲዋል ማስታወቁ አይዘነጋም። አቶ ጌታቸው ረዳ ግን “አደገኛ ምት አሳርፈናል|” ሲሉ የትህነግ ሰራዊት በመልካም ቁመና ላይ እንደሚገኝም በመናገር ሲያሻቸው ቆቦን ዳግም፣ ወይም ደሴን መያዝ እንደሚችሉ ሲናገሩ እንደነበር የሚያስታወሱ ” መቀለ ያሉ አመራሮች ለጊዜው መሸሸጊያ ወደሚሉት አካባቢ እየሸሹ እንደሆነ ሰምተናል” ብለዋል።

በመጨረሻም እየወጡ ያሉ መርጃዎች እንደሚሉት ትህነግ ትጥቅ ለመፍታት መስማማቱ ነው። ትህነግ ከዚህ ውሳኔ የደረሰው ቀደም ሲል ተይዞ የነበረው የንግግር መርሃ ግብር ትህነግ መንግስትን ከነሙሉ ህገ መንግስታዊ ባህሪው ጋር እንዲቀበል በአደራዳሪዎች የቀረበለትን ጥያቂ “አልቀበልም” ማለቱ ስለማያዋጣ ” እኔም እንደመንግስት በእኩል ደረጃ ልታይ” ሲል ያቀርበው ጥያቄ ውድቅ ከተደረገበት በሁዋላ ነው።

መጀመሪያ ለንግግር ተይዞ የነበረው ዕቅድ የተሰረዘው ትህነግ ከመንግስት እኩል ደረጃ ተቆጥሮ ለንግግር እንዲሰየም ያቀርበውን ጥያቄ መንግስት ህግ ጠቅሶና ምክንያት ሰጥቶ እንደማይቀበል፣ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጽህፈት ቤት በትግራይ በህግ የተቋቋመ አስተዳደር አለመኖሩን፣ የነበረውም ጊዜው ያበቃና በአገሪቱ ህግ መሰረት ምርጫ ያላካሄድ ህገወጥ አካል በመሆኑ “የትግራይ አማጺ” ተብሎ እንደሚጠራ በይፋ ያስታወቀው ከዚሁ ከትህነግ ጥያቄ በመነሳት ነው።

” የትግራይ መንግስት፣ የትግራይ የውጭ ግንኙነት …” የሚሉ ስያሜዎች ዳግም ስራ ላይ እንዳይውሉ፣ ይህን ማድረግ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት መጋፋት እንደሆነ ጠቅሶ ለዓለምና አህጉር አቀፍ ተቋማትና አገራት የስያሜ ማስተካከያ ደብዳቤም መበተኑ ይታወቃል። የመጀመሪያው ንግግር የተደናቀፈበትን ምክንያት የገለጹልን እንዳሉት የመንግስትን ምላሽ ተከትሎ በዳኝነት የተመደቡት አካላት የትህነግን “እኩል ልታይ” ጥያቄ ውድቅ ማድረጋቸውን አመልክተዋል።

በጦር ሜዳ ውሎ መከላከያ የሚመራውን የጥምር ጦር መቋቋም ያቃተው የትህነግ ሃይል እየተበተነ ባለበት በአሁኑ ወቅት የአዲግራት መያዝ ንግግሩ ላይ ብዙም የሚነሳ መከራከሪያ እንደማይኖር አመላካች ሆኗል።

የፌደራል መንግሥቱ በትግራይ የሚያደርገውን የአየር ማረፊያዎችንና የፌደራል ማዕከላት የመቆጣጠር ወታደራዊ ዘመቻውን እንደሚቀጥል በገለጸበት መግለጫው የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት በውይት ለመፍታት አሁንም ቁርጠኛ ነኝ ሲል ግዛቱን እንደሚያሰፋ አመልክቷል።

የትግራይ አማጺ ሃይሎች ከፍተኛ አመራር ፕሮፌሰር ክንድያ በጽሁፍ ለአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ እንዳስታወቁት በአፍሪካ ህብረት አነጋጋሪነት ሰኞ ጥቅምት 14 ቀን በደቡብ አፍሪካ ሊደረግ ቀጠሮ በተያዘለት የሰላም አማራጭ ንግግር መድረክ ላይ እንደሚገኙ አረጋግጠዋል። ያረጋገጡትም በጽሁፍ እንደሆነ ታውቋል። ይሁን እንጂ እነማን በንግግሩ ላይ እንደሚወከሉ ቀድሞ ከተነገረው ውጪ ያስታወቁት ነገር ስለመኖሩ ኤኤፍፒ በጽሁፍ ደረሰኝ ባለው መረጃ ላይ ስለመካተቱ ያለው ነገር የለም። ይህንኑ ዜና ተከትሎ ከትግራይ ለንግግር የሚወጡ አማራሮች እንደማይኖሩ እየተገለጸ ነው። በሌላ ቋንቋ ሰኞ ንግግሩ ላይ የትህነግ ሰዎች በውጭ አገር ክንፎቻቸው አማካይነት ካልሆነ በስተቀር የመወከላቸው ጉዳይ ያመነመነ ነው።

በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል እየተካሄደ ያለው ደም አፋሳሽ ጦርነት በሰላም ለመቋጨት ያስችላል የሚል ሰፊ ግምት በተሰጠው ንግግር መልካም ዜና ለመስማት ዜጎች በጉጉት ይጠብቃሉ። ትግራይም ዳግም ወደ ነበራት ሰላም ተመልሳ ከጎረቤት ክልሎች ጋር በመልካም መንፈስ እንድትቀጥል፣ አገሪቱም ወደ ልማት ፊቷን እንድታዞር መንግስት ከአሸናፊነት ስሜት ወጥቶ ለሰላም ያለውን ቁርጠኛነት እንዲያረጋግጥ የሚያሳስቡ ” በምንም ይሁን በምን ጦርነት ይብቃን” እያሉ ነው። ትህነግን እዛም እዚህም በውክልና የሚያራምደውን ሽብር እንዲያቆም ቢያንስ እያስጨረሰው ላለው የትግራይ ሕዝብ ሲል እንዲያበቃ ሕዝብ ትናንትና ዛሬ አደባባይ ወጥቶ ጠይቋል።

አሜሪካ በአፍሪካ ህብረት የበላይነት የሚካሄደውን የሰላም ንግግር እንደምትደግፍ ስታስታውቅ ” እልባት ይመጣል፣ ሰላም ይወርዳል” የሚል እምነት እንዳላት በማስታወስና ሙሉ ድጋፍ እንደምታደርግ በማረጋገጥ ነው።

የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ የብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ የሆኑት አቶ ሬድዋን ኢትዮጵያ በንግግሩ ላይ እንደምትገኝ ሲያስታውቁ የአገር ሉዓላዊነት የማስጠበቁ ተግባር እንደሚቀጥል ጎን ለጎን መግለጻቸው ይታወሳል። እሳቸው ይህን ካሉ በሁዋላ አክሱምና አደዋን ጨምሮ ጥምር ጦሩ ይዞታውን እያሰፋና ወደ መቀለ ማምራቱ ቀጥሏል። አዲግራት እስካሁን ውጊያ ያልተደረገበት በመሆኑ የትህነግ ሃይሎች የመጨረሻ አቅማቸው እዛ ላይ እንዳለ አሰላለፉን የሚያውቁ ግልጸዋል። ይሁን እንጂ የመንግስት ሃይሎች አዲግራት ለመግባት ብዙም እንዳልተቸገሩ አመልክተዋል። አሁን ባለው ቀሪ የመቀለ ኦፕሬሽን ላይ ምን አላባትም የንግግሩ ጠቀሜታ ፋይዳ ሊኖረው ይችላል። እየተገፋና ቀለበቱ እየጠበበት ተከማችቶ ከተማ ውስጥ ያለው ሃይል እጁን በሰላም እንዲሰጥ ማድረግ ትህነግን ወክለው ከሚገኙት ሃይሎች የሚጠበቅ መንግስትም የሚጠይቀው ጥያቄ ነው።

“ትግራይ ሰላም ካልሆነች ኢትዮጵያ ሰላም አትሆንም” ሲል ያስታወቀው ትህነግ ትጥቅ እንዲፈታ ከመንግስት በአገሪቱ ህግ መሰረት የቀረበለትን ጥያቄ መቀበሉን እንደሰሙ የሚገልጹ ወገኖች መልካም ዜና ይጠብቃሉ። የትግራይ እናቶችና ሕጻናትም የሰላም አየር ናፍቋቸዋል። አዛውንቶች እረፍት ናፍቋቸዋል። አፋርና አማራ ክልልም ነገ ከዛሬ ዳግም ወረራ ስጋት እየሆነባቸው መኖር መሯቸዋል። የውክልና ነውጥ የሚፈጥሩ አካላት በየአካባቢው ዘር እየለዩ የሚያደርሱት ጥቃት እንዲቆም ህዝብ ጠይቋል። እናም ተነጋጋሪዎች ቢያንስ በህይወታቸው ለመጀመሪያ ጊዜ ከስልጣን ጥማትና እብደት ነጻ ሆነው ለህዝብ ስቃይ መፍትሄ እንዲያበጁ የሁሉም ዜጎች ጥሪ ነው። ባከተመ ጨዋታ መንፈራገጥ አሁን ላይ ህይወት ከማጥፋት፣ ንብረት ከማውደምና ጣርን ከማስቀጠል የዘለለ ረብ አይስገኝም።

የሰላም አማራጭ ንግግሩ ሰፊ እድል ይዞ እንደሚመጣ ከወዲሁ የሚተነብዩ ኢትዮጵያ ሌቦችን ታድናለች። ተከፋዮች ወደ መደበኛ ህይወታቸው ይመለሳሉ። መንግስት ከሰላም ባሻገር ራሱን ያጸዳል። የጸረ ሌብነት ዘመቻው ሰይፉን ያነሳል። ይህ እንዳይሆን ሲያሴሩ የነበሩ ሁሉ ተስፋ ይቆርጣሉ። እዛም እዚህም ሽብርና ግድያ ላይ የተሰማሩ ያበቃላቸዋል።

ዘግይቶ በተሰማ ዜና ትግራይ አውሮፕላን እንዳረፈና ለንግግር የተወከሉትን ይዞ በናይሮቢ በኩል ወደ ደቡብ አፍሪካ ለማምራት ዕቅድ መያዙን ነው። ገን ሁሉም መረጃ በገለለተኛ ወገኖች አልተጠቀሰም።

Exit mobile version