Site icon ETHIO12.COM

የምሁራን ባለሙያዎች ለኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን ጉቤኤ ጠሩ

በኢትዮጵያ ዘላቂና አስተማማኝ ሰላም በሚሰፍንበት ሁኔታ ላይ የሚመክር ጉባዔ ሊያካሂድ መሆኑን የኢትዮጵያ ምሁራንና ባለሙያዎች መድረክ አስታወቀ። የመድረኩ ዋና ጸሐፊ ዶክተር አሸናፊ ጎሳዬ “ሰላም ማስፈንና ሰላም ግንባታ” በሚል ርዕስ የሚካሄደውን ጉባዔ ያዘጋጁት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ የጥናት ተቋም ጋር በመተባበር እንደሆነ ተናግረዋል።

በጦርነት ምክንያት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎች ሕይወታቸውን ባጡባት፣ሌሎች በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ከመኖሪያ ቀዬአቸው በተፈናቀሉባትና በርካታ የመሠረተ ልማት አውታሮቿ በወደሙባት ኢትዮጵያ፣ የሠላም ጉዳይ አንገብጋቢ አጀንዳ መሆኑን ዶክተር አሸናፊ አመልክተዋል።

በመሆኑም፣የኢትዮጵያ ምሁራንና ባለሙያዎች መድረክ፣በኢትዮጵያ ሰላም ማስፈን በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ውይይት ለማካሄድ ሲዘጋጅ መቆየቱን፣ የጉባዔው አስበባባሪ የሆኑት ዶክተር አሸናፊ ተናግረዋል።

“ፕሮግራሙ የተዘጋጀው እውነት ለመናገር፣በደቡብ አፍሪካና በኬኒያ የተደረሱት ስምምነቶች ውይይቶቹም ከመታሰባቸው በፊት ነው። እኛ የጥናት ወረቀት ጥሪ አውጥተን ሰዎችን ጋብዘን በዙህ ጉዳይ ላይ ልንወያይ ይገባል የምሁራን አስተያየት ማቅረብ ይገባናል ብለን ይህንን ነጻ መድረክ የፈጠርነው ቀደም ብለን ነው።”

ዶክተር አሸናፊ እንደሚሉት፣የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት ብቻ ሳይሆን በሌሎች አካባቢዎች ያለውም ግጭት ትኩረት የሚሻ ነው።

“በኢትዮጵያ ባለፉት ሁለት ዓመታት፣የነበሩት ግጭቶች በሰሜኑ የነበረው ጦርነት ብቻ አይደለም።ከእዛም ቀደም ብሎ፣ሃገራችን ከግጭት ነጻ ሆና አታውቅም።ከሰሜኑ ውጭ፣በሌሎችም አካባቢዎች በደቡብ፣በቤንሻንጉልም በኦሮምያም በጋምቤላም ኃይለኛ ግጭት ነው ያለው ሰብዓዊ ቀውሱ ከፍተኛ ነው።የሰው ህይወት በሰፊው ነው የጠፋው።እንግዲህ በሰሞኑ ሪፖርት እንደሰማኸው፣እንግዲህ በሰሜኑ ግጭት ብቻ፣ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ሕዝብ አልቋል ነው የሚባለው፤ያ ከሌሎች አካባቢዎች በታጣቂዎች የሚደርሱ ጥፋቶች ጋር ሲደማመር ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሰዎች አጥተናል።”

የፊታችን እና በቀጣዩ ሳምንት ቅዳሜ ለግማሽ ቀን በበይነ መረብ በሚካሄደው በዚሁ 12ኛ ጉባዔ፣በሰላም ማስፈንና ሰላም ግንባታ ላይ ያተኮሩ የጥናትና ምርምር ስራዎች እንደሚቀርቡ ዋና ጸሐፊው ጠቁመዋል።

“በዘርፉ ልምዱ ያላቸው፣ምርምር ያደረጉ ምሁራንን ባለሙያዎችን፣ቀድሞ ባለስልጣን የነበሩ ሰዎችን በተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማት የሰሩ፣ልምዱ ያላቸውን እንጋብዝና እስኪ ዐሳብ እስኪ እንወርውር በዐሳብ እንኳን እንፍታ ራሳችን ይህንን ነገር በቀጥታ ማቆም ባንችል እንኳን እነዚህ ዐሳቦች ሲደማመሩ ጥሩ ነገር ያመጣሉ ነው።”

በኢትዮጵያ ጦርነት በዘላቂነት በሚቆምበት ሁኔታ ላይ የምሁራንን ዐሳብና ምልከታ ማቅረብ ለነገ ተብሎ የሚተው ጉዳይ አይደለም ያሉት የመድረኩ ዋና ጸሐፊ፣ ሁሉም ወገን ሊረባረብበት እንደሚገባም አስገንዝበዋል።

“የሰላም ማስፈኑ ነገር ዋና ዩኤንም ዲፋይንድ እንደሚያደርገው፣በዲፕሎማቲክ ጫናው በምኑም ይኼ የግጭት ማቆም ስምምነት እሱን ማድረግ ከባድ ቢሆንም፤ቀጥሎ ከሚመጣው ጋር ሲነጻጸር፣ቀለል ይላል ማለት ይቻላል።ዋናው ነገር በዘላቂነት ሰላሙን ማስቀጠሉ ላይ ነው።በደቡብ አፍሪካ በተደረሰው ስምምነት መሠረት ሁላችንም እንደምንረዳው ተኩስ ማቆም ላይ ተደርሷል።በጣም ትልቅ እርምጃ ነው።ግን ቀጥሎ የሚመጣው ላይ ነው ፈተና።ኬኒያ ላይ የመጀመሪያው እርምጃ ተወስዷል ቢያንስ በወረቀት ላይ።እንዲሁም በመሬት ላይ የሚሰሩ ብዙ ከባድ ጉዳዮች አሉ።በእነሱ ላይ ሁላችንም መረባረብ ይኖርብናል።መደገፍ ይኖርብናል።እነዚህ አሁን የምንሰራቸው ስራዎች ለእዛ ሁሉ ጥሩ ግብአቶች ይሆናሉ ብለን እናምናለን።”

የኢትዮጵያ ምሁራን እና ባለሙያዎች መድረክ፣ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ጥናት ተቋም ጋር በጋራ ባካሄደው 11ኛ ጉባዔው፣ሃገራዊ ብሔራዊ ምክክሩን አጀንዳ አድርጎ መወያየቱ ይታወሳል። 

Dw news

Exit mobile version