Site icon ETHIO12.COM

ታሪኩ (ባባ) ቃሉ ተፈፃሚ መሆኑን የዓይን ባንክ አሳወቀ፤ ዓይኑን ሰጠ

የኢትዮጵያ የዓይን ባንክ ፤ ዛሬ ከሰዓት ባወጣው መግለጫ ፤ በታዋቂው እና ተወዳጁ አርቲስት ታሪኩ ብርሃኑ (ባባ) ህልፈት ሀዘን እንደተሰማው ገልጿል።

በመግለጫው ፤ አርቲስት ታሪኩ ብርሃኑ (ባባ) በህይወት በነበረበት ወቅት የዓይን ባንኩ አምባሳደር እንደነበርና ህልፈት በሚያጋጥምበት ጊዜ የዓይን ብሌኑን ለመለገስ ቃል ገብቶ እንደነበር ጠቁሟል።

የኢትዮጵያ ዓይን ባንክ ፤ አርቲስት ታሪኩ ብርሃኑ (ባባ) ” ስሙንም ብርሃኑንም ከመቃብር በላይ ህያው አድርጎ ያለፈ መልካም አርቲስት ” ሲል ጠርቶታል።

አርቲስቱ በገባው ቃል መሰረትም በቤተሰቦቹ እና በጓደኞቹ ቀና ትብብር ቃሉ ተፈፃሚ መሆኑን ባንኩ አሳውቋል።

በሌላ በኩል ፤ የአርቲስት ታሪኩ ብርሃኑ (ባባ)ን ስርዓተ ቀብር ለማስፈፀም ኮሚቴ ተዋቅሮ እየሰራ ሲሆን ይኸው ኮሚቴ የአርቲስቱ ስርዓተ ቀብር ነገ ታህሳስ 3 ቀን 2015 ዓ/ም ከቀኑ 9:00 ሰዓት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ወዳጅ ዘመዶቹ በተገኙበት እንደሚፈፀም ገልጻል።

ከስርዓተ ቀብሩ ቀደም ብሎ ከጠዋቱ 5:00 ሰዓት ጀምሮ በኢትዮዽያ ብሔራዊ ቴአትር ሽኝት ይደረጋልም ተብሏል።
(ቲክቫህ ኢትዮጵያ)

Exit mobile version