Site icon ETHIO12.COM

ትግራይ ክልል የሚገኙት ዩኒቨርስቲዎች ወደ አገልግሎት ለመመለስ ኮሚቴ ተቋቋመ

ከፊታችን ሰኞ ጀምሮ ስድስት አባላት ያሉት የባለሙያዎች ቡድን ወደ አክሱም ዩኒቨርሲቲ በማቅናት ምልከታ ሊያደርግ ነው፡፡

በግጭቱ ምክንያት ሥራ ያቋረጡትን አክሱም፣ ራያ፣ አዲግራት እና መቐለ ዩኒቨርሲቲዎች ወደ አገልግሎት ለመመለስ ኮሚቴ ተቋቁሞ እየተሠራ መሆኑ ተገልጿል።

እስካሁን ባለው ሁኔታ አክሱም እና ራያ ዩኒቨርሲቲዎች ዳግም ወደ አገልግሎት በሚመለሱበት ሁኔታ ላይ ንግግር መጀመሩን በትምህርት ሚኒስቴር የአስተዳደር እና መሰረተ ልማት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሰለሞን አብርሃ (ዶ/ር) ለፋና ተናግረዋል።

በቀጣይም ከመቐለ እና አዲግራት ዩኒቨርሲቲዎች ጋር ግንኙነት እንደሚጀመር ኃላፊው አመላክተዋል፡፡

በአክሱም ከተማ የተፈጠረውን ምቹ ሁኔታ ተከትሎ፤ ስድስት አባላት ያሉት የባለሙያዎች ቡድን ከሰኞ ጀምሮ የአክሱም ዩኒቨርሲቲ ዋናውን ግቢ ጨምሮ አድዋ እና ሽረ ግቢዎችን በስፍራው በመገኘት ምልከታ ያደርጋል ብለዋል፡፡

ቡድኑ ተቋማቱ በሰው ኃይል፣ በመሰረተ ልማት፣ በቤተ ሙከራ፣ በኔትወርክ፣ በመኝታና መማሪያ ክፍሎች፣ በማስተማሪያ ሆስፒታል፣ በቤተ መጻሕፍት እና ሌሎች አገልግሎቶች ዩኒቨርሲቲው የመማር ማስተማር ሥራውን ለማስጀመር የሚያስችለውን ሁኔታ ይመለከታል፡፡

Exit mobile version