Site icon ETHIO12.COM

የ20/80ና 40/60 የቤት እድለኞች ከጥር አንድ ጀምሮ ውል መዋዋል ይጀምራሉ

የ14ኛ ዙር 20/80 እና 3ኛ ዙር 40/60 የቤት ልማት ፕሮግራም የጋራ መኖሪያ ቤቶች የቤት እድለኞች ማሟላት የሚጠበቅባቸውን ቅድመ ሁኔታዎች በማሟላት ከጥር 1 ቀን 2015 ጀምሮ ዘወትር በሥራ ሰዓት ባሉት 60 የሥራ ቀናት ውስጥ ባለእድለኛው ወይም ወኪሉ ቀርበው ውል መዋዋል እንደሚጠበቅባቸው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቤቶች ልማት ኮርፖሬሽን አሳሰበ።

የኮርፖሬሽኑ የሕዝብ ግንኙነትና ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ጋሻው ተፈራ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደገለጹት፤ ከተማ አስተዳደሩ በ14 ኛ ዙር የ2080 የቤት ልማት ፕሮግራም 18 ሺ 930 ቤቶች፣ በ40/60 ደግሞ 6 ሺ 843 ቤቶች እንዲሁም ተጨማሪ 18 ስቱዲዮ ቤቶች በድምሩ 25 ሺ 791 ቤቶችን እጣ የማውጣት መርሃ ግብር በቅርቡ አካሂዷል።

ውል የመዋዋያ ቦታው መገናኛ በሚገኝው የቦሌ ክፍለ ከተማ ቅጥር ግቢ የአንድ ማእከል አገልግሎት መስጫ ውስጥ መሆኑን ጋሻው ጠቁመዋል፡፡
የቤት እድለኞች ውል ለመዋዋል ሲመጡ ማሟላት የሚጠበቅባቸው ቅድመ ሁኔታዎች እጣው የደረሰው ግለሰብ ውል ለመፈፀም በአካል መቅረብ፣ በውጭ የሚኖሩ ጉዳያቸውን በውክልና ለማስጨረስ በውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ተረጋግጦ (አውታንቲኬት) ሆኖ የመጣ ውክልና ማቅረብ፣ የታደሰ የነዋሪነት መታወቂያ ዋና እና 2 ፎቶ ኮፒ፣ የጋብቻ የምስክር ወረቀት ዋና እና 2 ፎቶ ኮፒ፣ ያላገባ/ች ከሆነ/ች 6 ወር ያላለፈው የምስክር ወረቀት፣ ያገባ/ች ከሆነ/ች የትዳር አጋር የታደሰ መታወቂያ ዋና እና ፎቶ 2 ኮፒ፣ የምዝገባ ማረጋገጫ (print out) ዋና እና 1 ፎቶ ኮፒ፣ የምዝገባ የምስክር ወረቀት ዋና እና 1 ፎቶ ኮፒ፣ የባንክ ምዝገባ ማረጋገጫ ከተመዘገቡበት ባንክ የሚቀርብ ዋና እና 1 ፎቶ ኮፒ፣ የባንክ የቁጠባ ደብተር ዋና እና 2 ፎቶ ኮፒ (ፎቶ ባለው በኩል)፣ የግብር ከፋይነት መለያ ቁጥር (TIN) ዋና እና 2 ፎቶ ኮፒ፣ ቅጽ -09 (ከወረዳ ተሞልቶ ታሽጎ የሚላክ) ዋና እና 1 ፎቶ ኮፒ፣ የጠፋ ሰነድ ካለ የፖሊስ ማስረጃ ዋና እና 1 ፎቶ ኮፒ፣ 4×4 የሆነ ጉርድ ፎቶ ግራፍ 4፣ ፍቺ ካለ በፍ/ቤት የፀደቀ ፍቺ ዋና እና 2 ፎቶ ኮፒ፣ የንብረት ክፍፍል ዋና እና 2 ፎቶ ኮፒ፣ ባለ ዕድለኛው በሞት ከተለየ የውርስ አጣሪ ሪፖርት ዋና እና 2 ፎቶ ኮፒ፣ የወራሽነት ማስረጃ ዋና እና 2 ፎቶ ኮፒ ባለ እድለኛው ወይም ወኪሉ ይዞ መቅረብ እንዳለበት አሳስበዋል።
ከላይ የተዘረዘሩትን ቅድመ ሁኔታዎች ሳያሟላ የሚመጣ ማንኛውም ባለጉዳይ እንደማይስተናገድ የጠቀሱት ዳይሬክተሩ፤ በውጭ አገር የሚኖሩ ትውልደ ኢትዮጵያውያን እና ኢትዮጵያዊ ከላይ የተጠቀሱትን ማሟላት የግድ ሆኖ የታደሰ ፓስፖርት ወይም ቢጫ ካርድ (yellow card) የታደሰ፣ በውክልና ከሆነ የውክልና ወረቀቱ በጀርባው በውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ማህተም የተረጋገጠና የተወካይ የታደሰ መታወቂያ ይዞ መቅረብ ይጠበቅበታል ብለዋል፡፡

ሆኖም በመመሪያ ቁ/3/2011 አንቀጽ 1 እና 2 መሰረት ባለእድለኞች ወይም ወኪላቸው ምዝገባ ከተጀመረበት ቀን አንስቶ ባሉት 60 የሥራ ቀናት ውስጥ ቀርበው ካልተዋዋሉ ቤቱን እንዳልፈለጉት ተቆጥሮ ተመላሽ እንደሚደረግ አጽንኦት ሰጥተው አሳስበዋል።
ለአዳዲስ ፈጣን ወቅታዊ መረጃዎች የቴሌግራም ቻናላችንን Join በማለት ይከታተሉ

Exit mobile version