Site icon ETHIO12.COM

መከላከያ አየር ወለድና አየር ሃይልን ማዘመን ቀዳሚ ተግባሬ ነው አለ

የባህር በር የሌላት አገር ስለምን ባህር ሃይል ታደራጃለች? ለሚለው ጥያቄ ” ዘመኑንና የወደፊቱን እናስባለን” የሚል መልስ በተሰጠ ሳምናት ውስጥ “ለሀገር ሉዓላዊነትና ደህንነት ሲባል ኮማንዶ አየር ወለድና አየር ኃይልን ከምንጊዜውም በላይ ለማደራጀት ተዘጋጅተናል” ሲሉ ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ አታወቁ። በቱርክም የጦር ቴክኖሎጂና ተመሳሳይ ስምምነት ማድረጋቸው ይታወሳል። ኢትዮጵያን በሚመጥን ደረጃ የስልጠና አሰጣጥ ሒደቱን እያዘመነ ጠንካራ ተዋጊ ኮማንዶ አየር ወለድና ልዩ ኃይል ፀረ-ሽብር የማሰልጠን ስራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተመልክቷል።

አዛዡ ይህን ያሉት የኮማንዶና አየር ወለድ ዕዝ ማሰልጠኛ ማዕከል መሠረታዊ ኮማንዶዎችን አየር ላይና እሳት ውስጥ እየተምዘገዘጉ ብቃታቸውን ባሳዩበት የምረቃ ስነስርዓት ላይ ነው። ቀደም ባሉት ጊዜያት የአየር ሃይል አዛዥ ጀነራል ይልማ መርዳሳ የኢትዮጵያ አየር ሃይል በአጭር ጊዜ ውስጥ ከአፍሪቃ ቁንጮ እንደሆነና ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ዘመናዊ ቲክኖሎጂ የታጠቀና ዘመናዊ ቴክኖሎጂን መንቀሳቀስ የሚችሉ ባለሙያዎች ያፈራ መሆኑንን፣ ይህም ለኢትዮጵያ ኩራትና ለዜጎች መመኪያ እንደሆነ ጠቅሰው መናገራቸው ይታወሳል።


ተጨማሪ ዜናዎችን ያንብቡ


ከመከላከያ ከባህር ኃይልና ከፌዴራል ፖሊስ በአንድነት ስልጠና የወሰዱት የመሠረታዊ ኮማንዶዎች ምረቃ ላይ የተገኙት የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ “ለሀገር ሉዓላዊነትና ደህንነት ሲባል ኮማንዶ አየር ወለድና አየር ኃይልን ከምንጊዜውም በላይ ለማደራጀት ተዘጋጅተናል” ማለታቸውን የዘገበው የሚመሩት ተቋም ነው።

ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ “ከቁጥጥር ውጭ የሆነ ነገር ቢያጋጥም ያንን የሚመክት ኃይል በማሰልጠን ፣በማስታጠቅና በማዘጋጀት ረገድ መንግስት ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ነው” ሲሉ ለተመራቂዎች የሀገር አለኝታነታቸውን በተግባር ማረጋገጥ እንዳለባቸውም በማሳሰብ ነግረዋቸዋል። ሰላም ግን ሁሌም ቀዳሚ መርህ መሆኑንን አመልክተዋል።

የኮማንዶና አየር ወለድ ማሰልጠኛ ማዕከል የሪፐብሊካን ጥበቃ ኃይልን ከማሰልጠንና ከማጠናከር ባለፈ በህገ-መንግስቱ በተሰጠው ተልዕኮ መሠረት የፌዴራልና የክልሎችን የፀጥታ ኃይል አቅም በመገንባት ላይ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ ኮማንዶና አየር ወለድ ዕዝ ጠቅላይ መምሪያ ዋና አዛዥ ሌተናል ጀነራል ሹማ አብደታ ናቸው።

ሌተናል ጀነራል ሹማ ማሰልጠኛው ኢትዮጵያን በሚመጥን ደረጃ የስልጠና አሰጣጥ ሒደቱን እያዘመነ ጠንካራ ተዋጊ ኮማንዶ አየር ወለድና ልዩ ኃይል ፀረ-ሽብር የማሰልጠን ተግባሩን አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

የኮማንዶና አየር ወለድ ማሰልጠኛ ማዕከል ዋና አዛዥ ኮሎኔል ቦጃ አጋ ባቀረቡት የስልጠና ሪፖርት ሰልጣኞቹ በስልጠና ቆይታቸው በቡድንና በነፍስ-ወከፍ መሳሪያዎች ማንኛውንም ተንቀሳቃሽ እና ቋሚ ኢላማዎችን የመደምሰስና የማውደም በተለያዩ የመሬት ገፆችና መልከዓ ምድር በቀንና በለሊት ስልታዊ እንቅስቃሴዎችን በማድረግ መደበኛና መደበኛ ያልሆኑ ግዳጆችን መወጣት የሚችሉ መሆናቸውንና ይህም ብቃታቸው በምዘና መረጋገጡን ገልፀዋል።

ማዕከሉን ምቹና ዘመናዊ ለማድረግም በመሠረተ ልማት ረገድ የብላቴ ዲምቱና የማዕከሉ የውስጥ ለውስጥ አስፖልት መንገድ ግንባታ የኤርፖርት የመመረቂያ ወረዳ እና ከ10 ሺህ ሰው በላይ መያዝ የሚችል አንፊ ቲያትር በመገንባት ላይ መሆኑን ተናግረዋል።

አሰልጣኞች የስራቸውን እና የልፋታቸውን ውጤት የሚያረጋግጡበት ምረቃ ለደረሱት ሰልጣኞች መልካም ምኞታቸውን ገልፀው በቀጣይም ማዕከሉ የሚቀበላቸውን ሰልጣኞች ለማሠልጠን እና ለማብቃት ዝግጁ ነን” ማለታቸውን የመከላከያ ገጽ አመልክቷል። ትህነግ ኢትዮጵያን መግዛት ሲጀመር አየር ወለድን ሙሉ በሙሉ በትኖ የዘጋና አየር ሃይሉን አንኮታኩቶት እንደነበር ባለሙያዎች ምስክረነት ሰጥተው ማጋለጣቸው አይዘነጋም።

በሌላ የማብቃትና መከላከያን የማዝመን ዜና የጦላይ ባለ ሌላ ማዕረግተኞች ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት በመሰረታዊ ውትድርና ያሰለጠናቸውን ምልምል ወታደሮች አሰመርቋል። ይህም የሚሆነው በሁሉም መስክ የበቃ፣ ጥንካራና የተደራጀ ሃይል መገንባት እጅግ አስፈላጊ በመሆኑ እንደሆነ ተመልክቷል።

ውጊያ ጋብ ሲል አዲስ ሃይል ከማደራጀት ጎን ለጎን ነባሩ ሰራዊት ባለበት የግዳጅ ቀጠና ተከታታይ የጦር ትምህርት፣ የብቃት ማሻሻያ ልምምድና ሩጫ ሳያዛንፍ እንደሚሰራ በተደጋጋሚ መገለጹና አዲሱ አደረጃጀት እረፍት ብሎ መቅመጥን የማይፈቅድ እንደሆነ መገለጹ ይታወሳል።

በምረቃ ስነ-ሰርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የመከላከያ መሃንዲስ ዋና መምሪያ ሃላፊ ሌተናል ጄኔራል ደስታ አብቸ ሀገር ታፍራና ተከብራ መኖር እንድትችል በሁሉም ዘርፍ የበቃና የተደራጀ ጠንካራ መከላከያ ሰራዊት ያስፈልጋታል ብለዋል።

አሁን ላይ የተገኘው ሰላም በሰራዊታችን ብርቱ ተጋድሎና መሰዋዕትነት የተገኘ ከመሆኑ በላይ የህዝባችን ደጀንነት እና መልካምነት ለሠራዊታችን ጥንካሬ አይነተኛ ሚና ያለው መሆኑንም ገልፀዋል።

የተቋሙን የዘመናዊ ሰራዊት ግንባታ ፍላጎት ለማሟላት ማሰልጠኛ ትምህርት ቤቶች ትልቁን ድርሻ ይወሰዳሉ ያሉት ጀኔራል መኮንኑ ተመራቂ ሠልጣኝ ወታደሮችም ይዛችሁት የመጣችሁትን የሀገር ፍቅር ስሜት ከተማራችሀት ወታደራዊ ሳይንስና ጥበብ ጋር በማጣመር ሀገራችንን በቅንነትና በፍፁም ታማኝነት ልታገለግሉ ይገባል ብለዋል።

ወደ ውትድርና ሙያ የሚቀላቀለው ወጣት ሁሉ የሀገር ፍቅር ሰሜት በውስጡ ያነገበ መሆኑን በተሠማራባቸው ግዳጆች ማረጋገጥ መቻሉንም የዕለቱ የክብር እንግዳ ሌተናል ጄኔራል ደስታ አብቼ ተናግረዋል።

የጦላይ ከፍተኛ ባለሌላ ማዕረግተኞች ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት ዋና አዛዥ ብርጋዲዬር ጄኔራል ጡምሲዶ ፊታሞ ባቀረቡት የሰልጠና ሪፓርት የውትድርና ሙያ ራሰን ሰውቶ ሌሎችን ማኖርን የሚጠይቅ በመሆኑ ሰልጣኛችም በማሠልጠኛ ማዕከሉ የወሠዱት ሥልጠና የሚሰጣቸውን ተልዕኮ ከነባሩ ሠራዊት ጋር ተቀላቅለው ለመፈፀም ያሥችላቸዋል ሲሉ ገልፀዋል።

ተመራቂ የሰራዊት አባላት በበኩላቸው በቆይታቸው በጥብቅ ዲሲፕሊን ታንፀው ግዳጅን በጋራ መወጣትና ለሀገርና ለህዝብ ዋጋ መክፈል ክብር መሆኑን ተገንዝበው ቀጣይ በሚሰማሩበት የግዳጅ ቀጠና ሁሉ አመርቂ ውጤት ለማሰመዝገብ ዝግጁ መሆናቸውን ማርጋገጣቸውን የማሩ ግርማይ ዘገባ ያስረዳል።

Exit mobile version