Site icon ETHIO12.COM

ትውልደ ኢትዮጵያዊው የፑንትላንዱ ዳኢሽ ታጣቂ ቡድን ኦፕሬሽን መሪ ተገደለ

የፑንትላንድ የጸጥታ ሃይሎች ትናንት ጥር 4 ቀን 2015 ባደረጉት ኦፕሬሽን ትውልደ ኢትዮጵያዊውን የዳኢሽ ታጣቂ ቡድን ኦፕሬሽን መሪ አቡ-አልባራ አል አማኒንን መግደላቸውን የፑንትላንድ ግዛት ፖሊስ አስታወቀ። 

ፖሊስ ባወጣው መግለጫው እንዳስታወቀው፤  በፑንትላንድ ደህንነት ሃይሎች አቡ-አልባራን የተገደለው፤ የታጣቂ ቡድኑ አባላት በምስራቅ ክልል በባሊ-ዲሂን አካባቢ በሚገኝ የጦር ሰፈር ላይ ያነጣጠረ ጥቃት ሲሰነዝሩ በተደረገ መልሶ ማጥቃት ነው።

የፑንትላንድ ግዛት ቴሌቭዥን የግዛቱን ፖሊስ ጠቅሶ እንደዘገበው፤ በዳኢሽ ታጣቂዎች የዳኢሽ ኦፕሬሽን ኃላፊ ሆኖ የተሾመው አቡ-አልባራ አል አማኒ ከፑንትላንድ የጸጥታ ሃይሎች ጋር ባደረገው ጦርነት መገደሉን ገልጿል።

መግለጫው አክሎም፤ አቡ አልባራ አል አማኒ በርካታ ኢትዮጵያውያንን በፑንትላንድ ግዛት የሚዋጋውን የዳኢሽ ቡድን እንዲቀላቀሉ በማስገደድ ኃላፊነቱን መስዶ እንደነበር ጠቁሟል።

ከዚህ ቀደም ፑንትላንድ የዳኢሽ ኦፕሬሽን ኃላፊ አቡ ዋሊድ አል ሙሀጅርን በካልሚስካድ ተራሮች አካባቢ መግደሏን ያስታወቀች ሲሆን፤ በዚህም ምክንያት ቡድኑ አቡ አልባራን፤ በአቡ ወሊድ ምትክ በፈረንጆቹ ሃምሌ ወር 2021 ላይ ሾሞ ነበር።

ISIL፣ Islamic State ወይም ISIS በመባል የሚታወቀው አሸባሪ ቡድን ክንፍ የሆነው የዳኢሽ ታጣቂ ቡድን፤ በአለም አቀፍ ደረጃ በአሸባሪነት የተፈረጀ ቡድን ነው። ቡድኑ እ.ኤ.አ በሚያዝያ 2015 በሊቢያ 28 ኢትዮጵያውያን እና ኤርትራዊያን ክርስቲያኖች ላይ አሰቃቂ በሆነ መልኩ አንገታቸውን በመቅላት ከተደረገው ግድያ ጀርባ እንደነበረ ይታወቃል።

Via Muktarovich ousman

Exit mobile version