Site icon ETHIO12.COM

ኢራን በስለላ የከሰሰቻቸውን የቀድሞ ምክትል የመከላከያ ሚኒስትሯን በሞት ቀጣች

ኢራን ውስጥ የሞት ፍርድ የተበየነባቸው የብሪታኒያ እና የኢራን ጥምር ዜግነት የነበራቸው አሊሬዛ አክባሪ መገደላቸውን የኢራን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

ባለፈው ረቡዕ የአክባሪ ቤተሰቦች “ለመጨረሻ ጉብኝት” ወደ እስር ቤት ሄደው እንዲጠይቋቸው ተነግሯቸው እንደነበር እና አክባሪ ለብቻቸው ታስረው እንደቆዩ ሚስታቸው ገልጸው ነበር።

የቀድሞው የኢራን ምክትል የመከላከያ ሚኒስትር አሊሬዛ አክባሪ የታሰሩት ከሦስት ዓመት በፊት ነበር። እሳቸው ቢያስተባብሉም ለዩናይትድ ኪንግደም በመሰለል ተከሰው ሞት ተፈርዶባቸዋል።

ዩናይትድ ኪንግደም (ዩኬ) ኢራን በአሊሬዛ አክባሪ ላይ ልትፈጽም ያቀደችውን የሞት ፍርድ በመተው በአስቸኳይ ግለሰቡን እንድትለቅ ስትጠይቅ ቆይታለች።

አርብ ዕለት የዩኬ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የሆኑት ጄምስ ክሌቨርሊ “ኢራን ጭካኔ በተሞላበት የግድያ ማስፈራሪያዋ መቀጠል የለባትም” ሲሉ አስጠንቅቀው ነበር።

ባለፈው ረቡዕ ክሌቨርሊ በትዊተር ገጻቸው ላይ እንዳሉት “ይህ ፖለቲካዊ ትርፍ ለማግኘት የሚወሰድ ኋላቀር የጭካኔ ቅጣት ነው፤ ኢራን ሰብአዊ መብት ግድ አይሰጣትም” ሲሉ ጠንከር ያለ ትችት ሰንዝረው ነበር።
ቢቢሲ

Exit mobile version