Site icon ETHIO12.COM

“የጥላቻ ፖለቲካን የፈለፈለው የብሔር አስተሳሰብ ሃይማኖት ውስጥም ገብቶ ሌላ ትርምስ ሲፈጥር ዝም ሊባል አይገባም! ” ኢዜማ

የኢዜማ መግለጫ


የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የተፈጠረውን ችግር በአንክሮ እየተከታተለው ይገኛል፡፡ ጅማሬው ካሳደረበት ብርቱ ስጋት አንጻር ፓርቲያችን ጥር 23 ቀን 2015 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ ለማስገንዘብ እንደሞከረው የሃይማኖት ተቋማት ውስጥ የሚፈጠሩ ችግሮች መፈታት ያለባቸው በተቋሙ ህግና አሠራር መሠረት ሲሆን ይህን ውስጣዊ አሠራር አልፈው ውሳኔ የሚፈልጉ ጉዳዮች የሚኖሩም ከሆነ ያለምንም ፖለቲካዊ ጣልቃ ገብነት በሕጋዊ መንገድ ብቻ ውሳኔ ማግኘት ይኖርባቸዋል፡፡

በዚህ ሂደት ውስጥ የመንግሥት ድርሻ መሆን የሚገባው በሕገመንግሥቱ አንቀጽ 11 ድንጋጌ መሠረት ፍጹም ገለልተኛነቱን በሚያረጋግጥ መልኩ በእኩልነት መርኅ ላይ ቆሞ ህግና ሥርዓትን ማስከብር ሲገባው በገሃድ ያሳየው ወገንተኝነት በእጅጉ አሳዝኖናል፤ ለተፈጠሩ ቀውሶችም ተጠያቂነት እንዳለበት ማስገንዘብ  እንወዳለን።

በተቋሙ የተፈጠረውን ውስጣዊ ችግር ተከትሎ  የመንግስት ኃላፊዎች ያደረጓቸው ንግግሮች ሁኔታውን ለተወሳሰበ ችግር ዳርገውታል። ከመንግስት ሃላፊዎች አባባሽ ንግግሮች ባሻገር የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥትና የጸጥታ ኃይሉ በቤተክርስቲያኒቱ ውስጣዊ ጉዳይ ጣልቃ በመግባት በተግባር ካሳዩት ወገንተኝነት እና አድሎ በከፋ መልኩ ባልታጠቁ እና ፈጽሞ የጸጥታ ስጋት ባልሆኑ ምእመናን ላይ ጭካኔ የተሞላበት የኃይል እርምጃ በመውሰዳቸው የንጹሐን ዜጎች ሕይወት እንዲቀጠፍ እና አካል እንዲጎድል ምክንያት ሆኗል፡፡

በክልሉ በተደጋጋሚ የሚስተዋሉ የንጹሐን ዜጎችን ሞት፣ አስከፊ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችና መፈናቀሎችን ተቆጣጥሮ ሰላምና ደኅንነትን ማስከበር ያልቻለው የክልሉ መንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ ላይ ጣልቃ እየገባ እንደሀገር ያለንበትን ችግር ውስብስብ እያደረገው ይገኛል፡፡ የፌደራል መንግሥቱም ቢሆን ይህን ዐይን ያወጣ ጣልቃ ገብነት በገሀድ እያየ የዜጎችን ሰላምና ደህንነት ለማስጠበቅ ምንም ዓይነት እርምጃ ባለመውሰዱ ዋነኛው ተጠያቂ ያደርገዋል፡፡

በሌላ በኩል የእምነቱ ተከታዮች የሃይማኖት ተቋማቸውን ትዕዛዝ በማክበር ጥቁር በመልበሳቸው ምክንያት በየመንገዱ እና በቤተ እምነታቸው ቅጥር ግቢ መደብደብ፣ ማዋከብ፣ ማሠር እና ማስፈራራት ደርሶባቸዋል፤ በተለይ በኦሮሚያና በአዲስ አበባ በሚገኙ መንግስታዊ የአገልግሎት መስጪያ ተቋማት ጭምር ተመሳሳይ በደል ሲደርስባቸው ተመልክተናል፡፡

ይኽ የዜጎችን ነፃነት መጋፋት ስለኾነ በምንም መንገድ ተቀባይነት የለውም። በኦሮሚያ ክልል የእምነቱ ተከታዮች ላይ እና የሃይማኖት አባቶች ላይ የሚደረጉ ማዋከቦች፣ እስሮች እና ግድያዎች አሁንም እየቀጠሉ በመሆኑ በአስቸኳይ ሊቆሙ ይገባል። ኢዜማ አሁንም የሃይማኖት ጉዳይ ውስጥ መንግሥት እጁን መክተቱ መዘዙ ከፍተኛ መሆኑን ደጋግሞ ማስገንዘብ ይፈልጋል፡፡

ድርጅታችን ኢዜማም ጉዳዩን በከፍተኛ ትኩረት እና በጥንቃቄ እየተከታተለ መሆኑን እያሳወቀ ለዚህ ሁሉ ውጥንቅጥ የዳረገን ብሔር ተኮር ፓለቲካ መሆኑን ለአፍታም ቢሆን አንዘነጋውም፤ የጥላቻ ፖለቲካን የፈለፈለው የብሔር አስተሳሰብ ሃይማኖት ውስጥም ገብቶ ሌላ ትርምስ ሲፈጥር ዝም ሊባል አይገባም እንላለን!

በሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጪ ያሉ ጽንፈኛ የብሔር ኃይሎች ህዝባችን ተረጋግቶ ለችግሮቹ በሰከነ መንገድ መፍትሔ እንዳያበጅለት ባገኙት የልዩነት ቀዳዳ ሁሉ የሚያደርጉትን ግፊት በቅጡ ማስተዋል እንደሚኖርብን ለማሳሰብ አንወዳለን፡፡

ኢዜማ እንደ አንድ ፖለቲካ ተቋም ችግሮቹ ተወሳስበው ወደ አላስፈላጊ መንገድ እንዳይሄዱና ተጨማሪ የሰው ሕይወት እንዳያስከፍለን ብሎም እንደሀገር ወደማንወጣው የማያባራ ውጥንቅጥ ውስጥ እንዳያስገባን እንደ አንድ ሀገር ወዳድ ፓርቲ የምንችለውን ሁሉ ከማድረግ ወደ ኋላ እንደማንል ለማሳወቅ እንወዳለን፡

ይህን መግለጫ ባወጣንበት ዛሬ እንኳን በወሊሶ መስመር በወለቴ፣ አለምገና እና ሰበታ ቀውሱ ተባብሶ ቀጥሏል፡፡

በተለያዩ ቦታዎች ሕይወታቸውን ላጡ እና ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች  የተሰማንን ጥልቅ ኀዘን እየገለፅን ለቤተሰቦቻቸው መፅናናትን እንመኛለን፡፡

አሁንም በድጋሚ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተፈጠረው ችግር በቤተክርስቲያኗ ቀኖና ከዚያም ካለፈ በሕግና በሕጋዊ መንገድ ብቻ እንዲፈታ እያሳሰብን፤ በአሁኑ ወቅት ግልፅ በሆነ መንገድ ጣልቃ እየገባ ያለው መንግሥት ለሀገር ሰላምና ደህንነት ስጋት እየፈጠረ መሆኑን ተገንዝቦ ኃላፊነቱ ህግን አክብሮ ማስከበር መሆኑን በመረዳት እንዲንቀሳቀስ ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡

የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)
የካቲት 2/2015 ዓ.ም.

Exit mobile version