Site icon ETHIO12.COM

ተጨማሪ አገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ሊደረግ ነው

የኢትዮጵያን የማክሮ ኢኮኖሚ ክፍተት በማጥበብ የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ይበልጥ ለማሳደግ የሚያስችል ተጨማሪ አገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ሊደረግ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ ገለጹ።

በኢትዮጵያ የመጣውን ለውጥ ተከትሎ በተለይም የኢኮኖሚ እድገቱን የተሳለጠ ለማድረግ አገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ በማድረግ ተጨባጭ ውጤቶች መመዝገባቸው ይታወቃል።

በመሆኑም በዘርፉ የተገኘውን ውጤት በተሻለ መልኩ ለማስቀጠል ተጨማሪ አገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ለማድረግ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ ገልጸዋል።

ሚኒስትሩ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ የተጀመረውን የኢኮኖሚ እድገት ለማስቀጠል የሚያስችል ተጨማሪ ማሻሻያ አስፈልጓል ብለዋል።

በመሆኑም በቀጣይ ቁጥር ሁለት አገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ለማድረግ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

የኢኮኖሚ ማሻሻያውም የመልሶ ግንባታ ስራን ለማሳለጥና የማክሮ ኢኮኖሚውን ክፍተት በማጥበብ የግሉን ክፍለ ኢኮኖሚ ተሳትፎ ለማሳደግ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል።

በአገር ውስጥና በውጫዊ ምክንያቶች በኢኮኖሚው ላይ የተፈጠረውን ጫና ለመቀነስም የሚረዳ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስትሩ አብራርተዋል።

የኢኮኖሚ ጫናውን በመቋቋም የዋጋ ንረትን ለመቆጣጠር፣ የውጭ ምንዛሬ አቅምን ለማሻሻልና ኢንቨስትመንትን ለማሳደግ ቀጣይነት ያለው የፖሊሲ እርምጃ ይወሰዳል ብለዋል።

በሰው ሰራሽና በተፈጥሮ አደጋ ምክንያት በኢኮኖሚው ላይ የተፈጠረውን ጫና መቋቋም የሚያስችል የማሻሻያ ስራ እየተከናወነ መሆኑንም ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

በዘላቂ የፋይናንስ መርህ ተመስርቶ በቁልፍ የመሰረተ ልማት ግንባታና በከተማና ገጠር ሴፍቲኔት መርሃ ግብር የመንግስት ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

በግብርናው ዘርፍ በምግብ ራስን ለመቻል በስንዴ፣ በቆሎ እና በሌሎች የሰብል ምርታማነት ላይ የተገኘው ውጤት የበለጠ እንዲጠናከር ይሰራል ብለዋል።

በግብርና ምርቶች ከአገር ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ለውጪ ገበያ የማዋል ጥረቱም የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል።

ኢትዮጵያ ያለባትን የእዳ ጫና ወደ መካከለኛ ደረጃ እንዲወርድ በማድረግ የውጭ ምንዛሬ አስተዳደርን ማሻሻል የሚያስችል የፖሊሲ እርምጃ እንደሚወሰድ ሚኒስትሩን ጠቅሶ ኢዜአ ዘግቧል።

በካፒታል ገበያ ለሚሳተፉ ተዋንያን ከሶስት ወር በኋላ ፈቃድ መስጠት ይጀመራል – የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለስልጣን

የኢንቨስትመንት ባንኮችን ጨምሮ በካፒታል ገበያው ለሚሳተፉ የዘርፉ ተዋንያን ከሶስት ወር በኋላ ፈቃድ መስጠት እንደሚጀምር የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለስልጣን አስታወቀ፡፡

በኢትዮጵያ ካፒታል በማሰባሰብ የገንዘብ ስርዓቱን በአዳዲስ ፈጠራዎች በመደገፍ የአገሪቱን የኢኮኖሚ ልማት የሚያጠናክር የካፒታል ገበያ ‘በካፒታል ገበያ አዋጅ ቁጥር 1248/2013’ ተቋቁሟል፡፡

በዚህ አዋጅ መሰረት ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የሆነ “የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለስልጣን” መስሪያ ቤት ተቋቁሞ ወደ ስራ ገብቷል፡፡

የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለስልጣን የሰነድ መዋዕለ ንዋዮችን በማውጣት የግብይት ስርዓቱን ፍትሃዊ፣ ቀልጣፋና ግልጽ በማድረግ የተሟላ የካፒታል ገበያ ስነ- ምህዳር የመፍጠር ስልጣን ተሰጥቶታል፡፡

ኢንቨስተሮችን በመጠበቅና ከለላ በመስጠት ኢንቨስትመንቱን ለማበረታታት ምቹ ሁኔታን መፍጠርና የካፒታል ገበያው ተዓማኒነት እንዲኖረው የማድረግ ኃላፊነትም አለበት፡፡

የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ብሩክ ታዬ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ ባለስልጣኑ ቦርድና ኃላፊ ተሹሞለት ወደ ስራ በገባባቸው ሶስት ወራት በርካታ ስራዎችን አከናውኗል ብለዋል፡፡

የካፒታል ገበያ ለኢትዮጵያ አዲስ እንደመሆኑ የተለያዩ የሕግ ማዕቀፎችና መመሪያዎችን በማዘጋጀት፣ በገበያው ላይ ለሚሳተፉ የዘርፉ ተዋንያን ፈቃድ ለመስጠት የሚያስፈልጉ ግብዓቶችን በማሰባሰብ ላይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ከዚህም ባሻገር የካፒታል ገበያን ጽንሰ ሀሳብ፣ ጥቅሙንና እንዴት እንደሚሰራ ብሎም በገበያው የሚሳተፉ አካላት እንዴት መግባት እንደሚችሉ ውይይት ተደርጓል ብለዋል፡፡

በካፒታል ገበያው ለሚሳተፉ ኢንቨስተሮችና ለሌሎች የዘርፉ ተዋንያን ፈቃድ ለመስጠት የሚያስችሉ የተለያዩ መመሪያዎች መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል፡፡

በመሆኑም ብሔራዊ ባንክ በሚያወጣው መመሪያ መሰረት ለውጭም ሆነ ለአገር ውስጥ ኢንቨስተሮች ከሶስት ወራት በኋላ በካፒታል ገበያ የሚያሳትፋቸውን የኢንቨስትመንት ባንክ ፈቃድ መስጠት እንጀምራለን ብለዋል፡፡

በኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ስርዓት የውጭ ኢንቨስተሮችን የሚከለክል ሕግ የለም ያሉት ዶክተር ብሩክ፤ ነገር ግን የአገር ውስጥ ባለሃብቶችን ትተን የምናሳካው ግብ የለም ብለዋል፡፡

ባለስልጣኑ ገበያውን በአስተማማኝ ሁኔታ ከመገንባት ባለፈ የአገር ውስጥ ባለሃብቶችን የማበረታታት ኃላፊነት እንዳለበትም ገልጸዋል፡

Exit mobile version