Site icon ETHIO12.COM

በወልቃይት መከላከያን በመጎንተል ለቆ እንዲወጣ፣ የአጻፋ ምላሽ እንዲሰጥ እየተደረገ መሆኑ ተሰማ፤

በአማራ ክልል ማን እንደሚመራዊና ሃላፊነቱን የሚወድ አካል የሌለበት ሰልፍ እየተካሄደ ነው። በጨዋነት ተቃውሞ አሰምተው የተበተኑ መኖራቸውን ያህል መንገድ መዝጋት በተለያዩ ከተሞች ተስተውሏል። የከፋም ባይሆን በጥይት የሞካከር ሁኔታም እንዳለ ከወደ ቆቦ ተሰምቶ ነበር። ዛሬ ይፋ የሆነውና ከወልቃይት የወጣው ዜና ግን ለየት ይላል።

በመንግስትም ሆነ በክልል ደረጃ በግልጽ የተባለ ነገር ባይኖርም በአካባቢው የሚኖሩ እንዳሉት በወልቃይት መከላከያ የአጻፋ ምላሽ እንዲሰጥ ጥይት እየትኮሱ ጉንተላ የጀመሩ ሃይሎች አሉ። በስም ግን የትኞቹ ታጣቂ ሃይሎች እንደሆኑ አላስታወቁም።

ከስፍራው ጥሬ መረጃ በማቅርብ የሚታወቀው ቶማስ ጃጃው እንዳለው “ለአማራ ልዩሃይል የተቆረቆሩ መስለው በመከላከያ ላይ ጥቃት በመክፈት በወልቃይት ግንባር ያለው መከላከያ ለቆ እንዲወጣና ደጀን እንዲፈልግ አልፎም አፀፋዊ ምላሽ ወደ መውሰድ እንዲሸጋገር provoke “የሚያቆጣ” የሚያደርግ ዘመቻ የከፈቱ ሰዎች ለሚፈጠረው የትኛውም አይነት ችግር ኋላፊነት የምትወስዱ ይሆናል። አንድም ሰው ቢሆን ለሚከፍለው የትኛውም አይነት አላስፈላጊ ዋጋ ትጠየቁበታላችሁ። የጊዜ ጉዳይ ነው” ሲል ሁኔታውን በተረዳበት መተን ገልጿል።

ዓላማው ግልጽ ያልሆነውና በትክክል ማን እንደሚሾፍረው የማይታወቀው የኢትዮጵያ የተቃውሞ እንቅስቃሴ አካል የሆነው ይህ ችግር ውሎ አድሮ መልኩን እንዳይቀይር በርካቶች ይሰጋሉ። “ከላይ ሲመለከቷቸው ለወልቃይት ተቆርቋሪ ሲፍቋቸው ግን ወልቃይትን ሲስተማቲካሊ ለትህነግ አሳልፈው ለመስጠት አማራ መስለው ‘ሴራ አለ’ በሚል ሴራ እየተወኑ መከላከያ እንዲተነኮስና እንዲጠቃ የሚሰሩና መከላከያን የሚያጠቃን አካል ደግሞ እንደ ጀግና ለመቁጠር የሚታትሩ ቅጥረኞች ደመ-ነብሳዊያን ኮንትሮባንዲስቶች …” ሲል ቶማስ የሰበሰበውን መረጃ ጠቅሶ አስጠንቅቋል።


“እንዴት አንድ የአማራ ተቆርቋሪ የሆነ ሰው ወልቃይትን በእጁ ያስገባለትን አካል በወልቃይት ጠላት ከሚለው ትህነግ በላይ ጠላት አድርጎ ሊመለከተው ይችላል?” ይላሉ ብዙዎች፣ ቶማስም ጃጃው “ዶ/ር አብይን ገና ሊክደን ይችላል በሚል ስሌትስ እንዴት ቀድሞ ክዶ መነሳት ተመራጭ ስልት ይደረጋል? የያዙትን ለመጣል መጣደፍንስ የማን አጀንዳ ነው? እንደምን ያለ ፖለቲካ ግንዛቤስ ነው?” ለሚያስቡ ሁሉ ጥያቄ አስቀምጧል። እሱ ብቻ ሳይሆን ብዙዎች ጠቅላይ ሚኒስትሩም ሆነ የብልጽግና መንግስት በተለየ አምራው ላይ የፈጸሙት በደል ምን እንደሆነ ገለልተኛ አስረጂ ይፈልጋሉ።

ለዚህ ይመስላል የክልሉ ሰላም ያሳሰባቸው “አማራ ሕዝብ በአማራ ስም ተቆርቋሪ ከሚመስሉት በላይ በየትኛውም መመዘኛ ለአማራው የቀደመ ጠላት የለውም። ወደፊትም ተንጋሎ የሚተፋ ወይም ወደራሱ ሊተኩስ የሚችል በዚህ ደረጃ በመናጆነት የሚያገለግል ቀድሞ ጠፊ ሃይል ፈፅሞ ሊፈጠር ይችላል ብዬ አላስብም” ሲል ቁጣ ያዘለ ጥያቄና አስተያየቱን ቶማስ ጃጃው ያስቀምጣል።

አንዳንድ ከተሞች ወደ መደበኛ እንቅስቃሴያቸው መግባታቸው በሚሰማበት ወቅት ከወልቃይት የተሰማው ዜና የረበሻቸው ትህነግ በመከላከያ ላይ የፈጸመው ጥፋት እንዳይደገም አብዝተው ይሰጋሉ።

ዝግጅት ክፍላችን ባገኘው መረጃ የአገር ሽማግሌዎችና በሂደቱ ያመኑ የልዩ ሃይል አመራሮች ነገሩን ለማርገብ ከመከላከያ ጎን ሆነው እየሰሩ መሆኑንን አስታውቀዋል። ውጤቱንም በመከታተል እንደሚያስታውቁ ገልጸዋል።

በትናንትናው ዕለት ጎበዜ የሚባለው የቀድሞ ኢሳት ባልደረባ ቆቦ መሆኑንን ገልጾ፣ መከላከያ በታንክና በመድፍ ከተማዋን እያጠቃ እንደሆነ፣ መከላከያ በፈጸመው ደረጃ የራሱ ህዝብ ላይ ጨካኝ እርምጃ ሲወሰድ አይቶ እንደማያውቅ በመግለጽ አስራ አምስት ደቂቃ በላይ ጥሪ ሲያሰማ ነበር። በዩቲዩብ መረጃው እሱ ይህን ቢልም ቆቦ ከተማ አንድም መድፍና ታንክ እንዳልተተኮሰባት፣ ይልቁኑም መከላከያ እየጠበቃት እንደሆነ ነው ምስክሮች የገለጹት። “ምን አልባት ጎበዜ ቦታ ተሳስቶ ካልሆነ በስተቀር ቆቦ ከተማ ላይ ከባድ መሳሪያ ሲተኮስ አልሰማሁም። ነዋሪ ነኝ። አሁንም እዛው ነኝ” ሲል ምስክርነቱን የሰጠን ወጣት እንዳለው ይህ ነው የማይባል ተኩስ አልፎ አልፎ ይሰማ እንደነበር” ግን አልሸሸገም።

Exit mobile version