Site icon ETHIO12.COM

ጀነራል ክንፈ ዳኘው በእስራትና በገንዘብ ተቀጡ

ከመርከብ ግዢ ጋር በተያያዘ የተከሰሱት የቀድሞ የብረታ ብረትና ኢንጂነሪግ ኮርፖሬሽን የሕግ ክፍል ኃላፊ በ6 ዓመት ከ6 ወራት ጽኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጡ ተወሰነ።

የቅጣት ውሳኔው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ የሙስና ጉዳዮች ወንጀል ችሎት ነው የተወሰነው።

የቅጣት ውሳኔ የተወሰነባቸው ተከሳሽ በወቅቱ ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ቀርተው በሌሉበት ጉዳያቸው ሲታይላቸው ቆይተው ከሁለት ዓመት በኋላ ፍርድ ቤት የቀረቡት የቀድሞ የብረታ ብረትና ኢንጂነሪግ ኮርፖሬሽን የሕግ ክፍል ኃላፊ የነበሩት ኮሎኔል መሐመድ ብርሃን ናቸው።

ዐቃቤ ሕግ በጥር 6 ቀን 2011 ዓ/ም የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ድርጅት አባይ እና አብዮት ከተባሉ ሁለት መርከቦች ግዢ ጋር በተያያዘ ከ544 ሚሊዮን ብር በላይ ጉዳት ደርሷል በሚል ሜጀር ጀኔራል ክንፈ ዳኘውን ጨምሮ ከ10 በላይ ተከሳሾች ላይ የሙስና ወንጀል ክስ መመስረቱ ይታወሳል።

ክሱ ከቀረበ በኋላ ኮሎኔል አዜብ ታደሰ ሀይሉ ፣ ሻምበል ይኩኑ አምላክ ተስፋዬ ፣ ሻምበል ሰመረ ኃይሌ ሐጎስ እና አቶ ሰሎሞን ኃይለሚካኤል ክሱ ተቋርጦላቸዋል፡፡

ሌሎች ማለትም በክሱ ተካተው የነበሩ ኮሎኔል ሙሉ ወልደገብርኤል ፣ ብርጋዴር ጄኔራል ጠና ቁሩንዲ እና ኮሎኔል ተከስተ ኃይለማርያም ደግሞ በፍርድ ቤቱ ተላልፎባቸው የነበረውን ፍርዳቸውን ጨርሰው ከእስር ተፈተዋል።

በ7ኛ ተራ ቁጥር በተከሳሽነት የተቆጠሩት በመርከብ ግዢ ኮሚቴ ነበሩ ተብለው በክሱ ተካተው የነበሩት እና በወቅቱ ባለመቅረባቸው ምክንያት በሌሉበት ጉዳያቸው ሲታይ ቆይቶ ከሁለት ዓመት በኋላ ፍርድ ቤት ቀርበው ክርክር ያደረጉት ኮሎኔል መሐመድ ብርሃን በሚመለከት ዓቃቤ ሕግ የቀረበባቸውን የሰው ምስክር እንዲከላከሉ ብይን ተሰጥቶ ቆይቷል።

በብይኑ መሰረት በተለያዩ ቀናቶች የመከላከያ ማስረጃዎቻቸውን ያቀረቡ ቢሆንም ፍርድ ቤቱ የዐቃቤ ሕግ ማስረጃን በተገቢው ማስተባበል አልቻሉም ሲል በአንቀጽ 411/ንዑስ ቁጥር 2 መሰረት የጥፋተኝነት ፍርድ ተላልፎባቸዋል።

ተከሳሹ ኮሎኔል መሐመድ ብርሃን በሠላም ማስከበር ዘርፍ ለሀገር ያበረከቱትን አስተዋኦ እና ሀገራዊ ልማት ላይ ያደረጉትን ተሳትፎ ጨምሮ ሰባት ቅጣት ማቅለያ አስተያየት በጽሑፍ አቅርበው ተይዞላቸዋል።

እንደ ኤፍቢሲ ዘገባ፤ ዐቃቤ ሕግ ድርጊቱ በስምምነት የተፈጸመ መሆኑን ጠቅሶ ቅጣቱ ከፍ ብሎ እንዲጣልለት ያቀረበው የቅጣት ማክበጃ አስተያየት የተያዘለት ሲሆን በቅጣት አወሳሰን መመሪያ ቁጥር 2/2006 መሰረት ፍርድ ቤቱ በ6 ዓመት ከ6 ወራት ጽኑ አስራትና በ10 ሺህ ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲቀጡ ወስኗል።

በዚሁ መዝገብ ክስ ቀርቦባቸው የነበሩት የቀድሞ የሜቴክ ዋና ዳይሬክተር ሜጀር ጀነራል ክንፈ ዳኘውን በሚመለከት ግን በቀረበባቸው ክስ ላይ የመከላከያ ማስረጃዎቻቸውን በማሰማት ሂደት ላይ ናቸው።

EPA

Exit mobile version