Site icon ETHIO12.COM

በሳምንቱ

🇪🇹 የጣልያን ጠቅላይ ሚኒስትር ጆርጂያ ሜሎኒ የሁለት ቀን ይፋዊ የሥራ ጉብኝት በአዲስ አበባ አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በማህበራዊ ገጻቸውም፤ ጉብኝቱ የሁለቱን ሀገሮች ግንኙነት የበለጠ ለማጠናከር አጋዥ ነው ሲሉ ገልጸዋል።

🇪🇹 የሶማሊያው ፕሬዝዳንት ሐሰን ሼክ መሐሙድ በኢትዮጵያ ይፋዊ የስራ ጉብኝት አድርገዋል። “ለሁለት ቀናት የሥራ ጉብኝት ወደ ኢትዮጵያ የመጡትን የሶማሊያውን ፕሬዝዳንት ሐሰን ሼክ መሐሙድን ተቀብያለሁ” ሲሉም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ገልጸዋል።

🇪🇹 ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ከጣሊያን ጠቅላይ ሚኒስትር ጆርጂዮ ሜሎኒ እና ከሶማሊያ ፕሬዚዳንት ሀሰን ሼክ መሐሙድ ጋር ተወያይተዋል፡፡ ውይይታቸው በዋናነት የአገራቱን የሶስትዮሸ ግንኙነት ይበልጥ ማጠናከር በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ ውይይቱን የተከታተሉት በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የፕሬስ ሴክሪታሪያት ሃላፊ ቢልለኔ ስዩም እንዳሉት፤ መሪዎቹ ከሶስትዮሸ በተጨማሪ በባለ ብዙ ወገን ዲፕሎማሲ ላይ ያላቸውን አጋርነት በማጠናከር ረገድ ፍሬያማ ውይይት አድርገዋል፡፡

🇪🇹 ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ለጣሊያን ጠቅላይ ሚኒስትር ጆርጂያ ሜሎኒ በታላቁ ቤተ መንግሥት የክብር እራት ግብዣ አድርገዋል።

🇪🇹 የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ መንግስት ሰሞኑን በሱዳን ጦር እና በፈጥኖ ደራሽ ሃይሎች/ልዩ ሀይሎች/ መካከል በካርቱም መዲና እና በሌሎች የሱዳን ከተሞች የተፈጠረውን ግጭት በከፍተኛ ስጋት እየተከታተለው እንደሚገኝ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ በማህበራዊ የትስስር ገጻቸው በአረብኛ ቋንቋ ባስላለፉት መልእክት አመልክተዋል፡፡

🇪🇹 በስሎቬኒያ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ታንጃ ፋጆን የተመራው ልኡክ በአዲስ አበባ ይፋዊ የሥራ ጉብኝት አድርጓል። ልኡካን ቡድኑ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ እና ሌሎች ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች አቀባበል አድርገውለታል።

🇪🇹 ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ከስሎቬኒያ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ታንጃ ፋጆን ጋር ውይይት አድርገዋል። በማህበራዊ ገጻቸውም፤ “በኢትዮጵያና በስሎቬንያ የሁለትዮሽ ግንኙነት ላይ ከስሎቬንያ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ታንጃ ፋጆን ጋር ዛሬ ውጤታማ ውይይት አድርገናል።” ሲሉ አስታውቀዋል።

🇪🇹 ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን በስሎቬኒያ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከተመራው የልኡካን ቡድን ጋር ተወያይቷል። አቶ ደመቀ ስሎቬኒያ የአውሮፓ ህብረት አባል ሆና ለኢትዮጵያ ስታደርግ ለቆየችው እና እያደረገች ላለችው አስተዋፅኦ አመሥግነዋል። የስሎቬኒያ መንግሥት ባለሃብቶችን በንብ ማነብ፣ በኬሚካል ምርት፣ በቱሪዝም እና በሌሎች ዘርፎች ኢንቨስት በሚያደርጉበት ሁኔታ ላይ ውጤታማ ውይይት ማድረጋቸው ተገልጧል፡፡

🇪🇹 ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን የህንድ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ሱብራህማንያም ጃይሻንካርን በጽህፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል። በውይይታቸውም ስለፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት አተገባበር፣ ግጭት በነበረባቸው አካባቢዎች እየተደረገ ስላለው ሰብአዊ ድጋፍና መሰረታዊ አገልግሎቶችን የማስጀመር ሂደትን በተመለከተ አቶ ደመቀ ገለጻ አድርገውላቸዋል።

🇪🇹 ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት የህፃናት አድን ድርጅት ዩኒሴፍ ተወካይ ከሆኑት ዶ/ር አቡበከር ካምፓ ጋር ዛሬ በጵ/ቤታቸው ተወያይተዋል። በውይይቱ ላይ እንዳሉት ዩኒሴፍ በኢትዮጵያ ልማት ላይ ቁልፍ ድጋፍ እያደረገ ያለ አጋር መሆኑን ቅሰው፣በህፃናት የተመጣጠነ ምግብና ትምህርት እንዲዳረስ እየተገበራቸው ያሉ መርኸግብሮችን አድንቀዋል።

🇪🇹 የኢፌዲሪ የገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ ከዓለም ባንከ ፕሬዝዳንት ዴቪድ ማልፓስ ጋር ውይይት አድረገዋል። ሁለቱ ወገኖች በዚሁ ቆይታቸወም፤ የኢትዮጵያ መንግስት የፕሪቶሪያውን ስምምነት በመተግበር ላይ ያሳያቸውን መሻሻሎች አንስተው የተወያዩ ሲሆን፤ በቀጣይም ለዘላቂ ሰላምና ብልጽግና ሲባል የሚወሰዱ እርምጃዎን ፕሬዝዳንቱ ማበረታታቸው ተገልጿል።

🇪🇹 የሴቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተሥፋዬ (ዶ/ር) የስሎቬኒያ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ታንጃ ፋጆን ጋር ተወያይተዋል፡፡ በውይይታቸውም በኢትዮጵያ ሴቶችን በማብቃት የቤተሰብ ብልፅግናን ማረጋገጥ በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ መክረዋል።

🇪🇹 ስሎቬኒያ በኢትዮጵያ ኤምባሲ ለመክፈት በሚያስችላላት ሁኔታ ላይ የሃገሪቱ የውጭ ጉዳይ ልዩ መልዕክተኛ ሬናታ ቬልባር ከኢፌድሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዲኤታ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ ጋር ተወያይተዋል። በውይይታቸው ስሎቬኒያ ኤምባሲዋን እንድትከፍት ኢትዮጵያ ድጋፍ እንደምታደርግ ሚኒስትር ዲኤታዋ አረጋግጠዋል።

🇪🇹 አምባሳደር ተፈራ ደርበው በቻይና የኢፌዲሪ ልዩ መልዕክተኛና ባለ ሙሉ ስልጣን ከቻይናው የሲኖማ ኢንተርናሽናል ሊቀመንበር እና የሲ ኤን ቢ ኤም ሊሚትድ (CNBM Limited) ሲሚንቶ ኩባንያ ዋና ዳይሬክተር ከሆኑት ሊዩ ያን ጋር በቤጂንግ ተወያይተዋል፡፡ አምባሳደር ተፈራ በዚሁ ወቅት፤ ሲኖማ ሲሚንቶ ፋብሪካ በአገራችን ባሉት የሲሚኒቶ ፋብሪካዎች ከዲዛይን ጀምሮ በግንባታ ረገድ ላበረከተው አስተዋጽኦ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

🇪🇹 የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ ከአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ሙሳ ፋኪ ማህመት ጋር በተለያዩ ጉዳዮች ዙርያ ተወያይተዋል። በውይይቱ በአፍሪካ ህብረት መሪነት የተደረሰው የሰላም ስምምነት ስለማገኝበት ሁኔታ አምባሳደር ምስጋኑ ገለፃ አድርገዋል ።

🇪🇹 የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶ/ር ኢ/ር ሃብታሙ ኢተፋ በኢትዮጵያ ከሩሲያ አምባሳደር አቪግኒ ተርኪሂን ጋር በኢነርጂ ኢንቨስትመንት ዙሪያ ተነጋገሩ፡፡ በውይይቱ የሩሲያ መንግስትና ህዝብ ከኢትዮጵያ መንግስትና ህዝብ ጋር የቆየ ጠንካራ ወዳጅነት መኖሩን ፤ ይህም በአለም አቀፍ መድረኮች መታየቱን ፤ በልማቱ መስክም የመልካዋከና የውሃ ሀይል ማመንጫ ፕሮጀክት ግንባታ ላይ የተደረገው አስተዋጽኦ ላይ ዶ/ር ኢ/ር ሃብታሙ ኢተፋ አብራርተዋል።

🇪🇹 በኒውዮርክ በተካሄደው የተባበሩት መንግስታት የህዝብና እድገት ኮሚሽን 56ኛ መደበኛ ጉባኤ ላይ በፕላንና ልማት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴታ አቶ ሳንዶካን ደበበ የተመራ ልዑክ ቡድን ተሳትፏል፡፡ በመድረኩ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዲኤታ አቶ ሳንዶካን ደበበ የትምህርት ተደራሽነትን በማስፋት ሀገራዊ የህዝብ እድገትን ከዘላቂ የኢኮኖሚ እድገት ጋር ማስተሳሰር የሚቻልበት አግባብ ላይ በሰፊው እየተሰራ መሆኑ አብራርተዋል።

🇪🇹 በገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሺዴ የተመራ ልዑክ ከተለያዩ ዓለም አቀፍ የገንዘብ ተቋማት የስራ ሃላፊዎች ጋር መወያየቱ ተገልጿል። ውይይቱ ከፀደይ ወቅት ስብሰባ ጎን ለጎን የተካሄደ ሲሆን ከዓለም ባንክ፣ ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም (አይ ኤም ኤፍ) እና ከዓለም አቀፉ የፋይናንስ ኮርፖሬሽን (አይ ኤፍ ሲ) ፕሬዚዳንቶች እና ዳይሬክተሮች ጋር መደረጉ ተገልጿል።

🇪🇹 የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ በዓለም ባንክ አዘጋጅነት “ዕዳን ማሸነፍ፤እድገትን ማፍጠን” በሚል ርዕስ በተዘጋጀው የፓናል ውይይት ላይ ተሳትፈዋል፡፡ ዓለም አቀፍ ተቋማትና የግሉ ዘርፍ ኢትዮጵያ እያካሄደች ለምትገኘው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንዲቀጥሉ የገንዘብ ሚንስትሩ ጥሪ አቅርበዋል።

🇪🇹 በቻይና የኢትዮጵያ አምባሳደር ተፈራ ደርበው ከቻይና የአፍሪካ ልማት ፈንድ ዋና ስራ አስፈፃሚ ሺ ዌንጁ ጋር በኢንቨስትመንት አማራጮች ዚሪያ ተወያይተዋል፡፡ አምባሳደር ተፈራ ደርበው በኢትዮጵያ በሚካሄደው የኢንቨስትመንት ፎረም እና በኢትዮጵያ ባሉ የኢንቨስትመንት አማራጮች ዙሪያ ለቻይና የአፍሪካ ልማት ፈንድ ዋና ስራ አስፈፃሚ ሺ ዌንጁ ገለጻ አደረጉ።

🇪🇹 የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ የግሎባል ሴኩሪቲ የዳይሬክተሮች ቦርድ አባል ሆኖ የተመረጠው በቻይና ናንጂንግ ከተማ ሚያዚያ 3 እና 4 ቀን 2015 በተካሄደው የዓለም አቀፍ የህዝብ ደህንነት ትብብር ፎረም (Global public security Cooperation Forum) ላይ መሆኑ ተገልጿል።

Ena

Exit mobile version