Site icon ETHIO12.COM

ለውጭ ዜጎች ባልተፈቀደ ስራ የተሰማሩት የትርምስ ምንጮች ተለዩ

በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል ትህነግ የከፈተውን ጦርነት ተገን በማድረግ በከፍተኛ ኮንትሮባንድ ንግድና ለውጭ ዜጎች ባልተፈቀደ የንግድ ስራና ገንዘብ አጠባ ላይ የተሰማሩ መለየታቸው ተሰማ። የኢትዮጵያና የኤርትራን ዕርቅ ተከትሎ መርህና ህግ እየተጣሰ መሆኑን በማስረጃ የሚገልጹ ወገኖችም እየበረከቱ ነው።

ለክትትሉና ቁጥጥሩ ስራ ቅርብ መሆናቸውን የገለጹ እንዳሉት ከሰላም ስምምነቱ በሁዋላ መንግስት ሙሉ ትኩረቱን ወደ ህገወጥ ንግድ አክትሮችና በህግ ለውጭ አገር ዜጎች ባልተፈቀደ ስራ የተሰማሩትን ለቅሞ ጨርሷል። መረጃውም ተደራጅቷል። ህገወጥ ንግድ መነገድ ብቻ ሳይሆን የውጭ ምንዛሬን በመልቀም በስም በሚታወቁ ዲፕሎማቶች የማሸሽ ስራ የሚሰሩትም ታውቀዋል። እጅ ከፍንጅም የተያዙ አሉ።

አሁን ላይ ጊዜው ስላልሆነ ስምና አካባቢን ጠቅሶ መረጃ መስጠቱ አግባብ እንደማይሆን የሚጠቁሙት ወገኖች ” ህዝብ ከየአቅጣጫው የሚያሰማው ድምጽና ጥቆማ መበርከቱ ለመንግስት እርምጃ አጋዥ ይሆናል” ብለዋል።

” አዲስ አበባ ግቡና በአጭር ጊዜ ክበሩ” በሚል የትስስር ገበያ በኮንትሮባንድ አገሪቱን ሊያሰጥሙ የተነሱትን ወገኖች የመለየቱ ስራ በሚመለከታቸው አካላት ተጠናቆ ለሚመለከታቸው የመንግስት ሃላፊዎች ቀርቦ አመራር እንደሚሰጥበት የመረጃው ምንጮች አመልክተዋል።

ጦርነቱ ከቆመ በሁዋላ በየአቅጣጫው ተቃውሞና አመጽ የሚደራጀው ይህ ተግባራዊ እንዳይደረግና ሲደረግም ብሄርና ሰፈር ውስጥ በመግባት አፈጻጸሙን ለማኮላሸት እንደሆነ እነዚሁ ወገኖች አመልክተዋል።

በተለይም ከቅባት እህል ኤክስፖርት ጋር በተያያዘ መንግስት መውጫውን በመከላከያ ሰራዊት መዝጋቱ ብስጭት እንደፈጠረና የትስስሩን ተጠቃሚዎች ያበሳጨ በመሆኑ የትርምስ አጀንዳውን ለማስፋት ሌት ተቀን ድጋይ እየተፈነቀለ መሆኑንንም አመልክተዋል።

“ስግብግብ ፖለቲከኞችና፣ በዝርፊያ ላይ የተመሰረተ ጉርብትናን ቅድመ ሁኔታ አድርገው የጀመሩት ማግበስበስ ጣጣው ለሰላማዊ ዜጎች እንዳይተርፍ ስጋት አለን” የሚሉ ወገኖች ቀደም ሲል የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት መነሻው ህገወጥ የኢኮኖሚ የበላይነት የመያዝ በተደረገ ትንቅንቅ ሳቢያ መሆኑንን ያስታውሳሉ። አንድ ዕግር ቡና የሌላት አገር ቀዳሚ ቡና ላኪ ሆና መመዝገቧ፣ በኢትዮጵያ ለውጭ አገራት ባልተፈቀደ የፋይናንስ ግብይት ውስጥ በመግባት ባንክ በማቋቋም የተሰራው ወንጀል እንደሆነ አክለው ይገልጻሉ።

እነዚሁ ወገኖች እንደሚሉት ዛሬም በርካታ የማያስደስቱና ዳግም ግጭት ሊያስነሱ የሚችሉ ሩጫዎች እየተስተዋሉ መሆናቸውን ገልጸው፣ ” ይህ አካሄድ መልካሙን ግንኙነት እንዳያበላሸው ስጋት አለን። የኤርትራ ንጹህ ዜጎችም እንዲህ ያለውን ሁኔታ በቀናነት ሊያወግዙ ይገባል። አንድም ኢትዮጵያዊ በኤርትራ ህገ ወጥ ተግባር ላይ ተሰማርቶ እንደማይገኝ ሁሉ ጥቂት ኤርትራዊ የሆኑ ህገወጦች ራሳቸውን ወደ ህጋዊ መስመር ሊመልሱ ይገባል። ይህ ካልሆነ ቀይ መስመር ሲሰመር ጉዳቱ እንደ ከዚህ ቀደሙ የንጽሃንና ምስኪኖች ይሆናል” ሲሉ አሳስበዋል።

መንግስት አስተማማኝ የጸጥታ ሃይል ስላለው በሙሉ ሃይሉ ወደ ቁጥጥርና ቅጣት፣ እንዲሁም መስመር ወደማስያዝ እንደሚገባ እነዚሁ ወገኖች አመልክተዋል። በተለያዩ የማህበራዊ አውዶችም ጉዳዩ ከቀድሞው ይልቅ ገሃድ መነጋገሪያ እየሆነ ነው። በተመሳሳይ የቁጥጥር ስራው እንዳይጀመር ለማራዘም ንክኪ ያላቸውና ህግ በማይፈቅደው መልኩ በህገወጥ ተግባር የተሰማሩ አጀንዳ እያዘጋጁ አለመረጋጋት እንዲሰፍን በሚቻላቸው ፍጥነት እየሰሩ መሆኑን ህዝብ እንዲገነዘብ አሳስበዋል።

Exit mobile version