Site icon ETHIO12.COM

የጀርመንና የኢትዮጵያ የመረጃ ደህንነት ተቋማት በጋራ ለመስራት ተስማሙ

የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ከጀርመን የመረጃና ደኀንነት ተቋማት ጋር በትብብር ለመሥራት ስምምነት አደረገ። የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ከጀርመን የመረጃና ደኀንነት ተቋማት ጋር በትብብር ለመሥራት የሚያስችለውን ውይይት ማድረጉና መስማማቱ ተገልጿል።

በብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጀነራል አቶ ተመስገን ጥሩነህ የተመራ የልዑካን ቡድን ከጀርመን የመረጃና ደኀንነት ተቋማት የልዑካን ቡድን ጋር በነበራው ቆይታ በቀጣናዊ፣ ዓለም አቀፋዊና ወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ በዝርዝርና በጥልቀት ተወያይቷል። ከውይይቱ በኋላም ተቋማቱ በጋራ ጉዳዮች ላይ ለመሥራት የሚያስችላቸውን የአቅም ግንባታ ስልጠናዎችን ለማድረግ መስማማታቸው ተገልጿል።

የኢትዮጵያና የጀርመን የመረጃና የደኅንነት ተቋማት ሽብርተኝነትን ፣ሕገ-ወጥ የገንዘብና የሰዎች ዝውውርን እንዲሁም ሌሎችንም ወንጀሎች በጋራ ለመከላከል የመረጃ ልውውጥ ማድረግም የስምምነታቸዉ አካል መሆኑን የብሔራዊ መረጃና ደኀንነት አገልገሎት ለመገናኛ ብዙሃን በላከዉ መረጃ አመልክቷል።

በሌላ ዜና በአዲስ አበባ እና በዴንቨር ከተሞች የሁለትዮሽ ስምምነት የመግባቢያ ሰነድ መፈረሙን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገልጸዋል። ስምምነቱን አስመልክቶ ከንቲባዋ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው እንደገለጹት የስምምነቱ ትኩረት የሁለቱን ከተሞች ግንኙነት ይበልጥ በማጠናከር በንግድ ፣ በኢንቨስትመንት እና በቴክኖሎጂ ዘርፎች በጋራ ለመስራት የሚያስችል ነው።

“በአለም የንግድ ቀን ፕሮግራም ላይም ኢትዮጵያን የሚያስተዋውቁ ምርቶችን አቅርበናል” ያሉት ከንቲባዋ በዴንቨር ከተማ ከአቀባበል ጀምሮ በቆይታቸው ለተደረገላቸው መስተንግዶ ከንቲባ ሃንኮክን እና ባልደረቦቻቸውን አመስግነዋል። ኢዜአ

Exit mobile version