Site icon ETHIO12.COM

“እንዳለመታደል ኾኖ ኢትዮጵያን ኢትዮጵያውያንም አያውቋትም” ፕሮፌሰር አደም ካሚል

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በኢትዮጵያ ሰማይ ሥር ዝናብ በጣለ፤ ደመና ባዘለ ቁጥር አብዝቶ የሚበርዳቸው ጎረቤቶቿን ኾኗል፡፡ ኢትዮጵያውያን በውስጥ ችግራቸው፤ በግል ጉዳያቸው ቅራኔ የገባቸው በመሰላቸው ቁጥር እሳት እና ጭድ አቀባይ ክፉ ጎረቤቶችን አስተውለናል፡፡ በኢትዮጵያዊያን ጉስቁልና የሚሸቅጡ፤ በኢትዮጵያ ድካም የሚቃበጡ የሀገሪቷ ጥንተ ጠላቶች ዛሬም ተስፋ አልቆረጡም፡፡

በየዘመኑ ኢትዮጵያ ውስጥ ለተፈጠሩ ምስቅልቅሎች እና ፈተናዎች የሴራ ፊታውራሪዎቹ የፈርኦን አልጋ ወራሾቹ የካይሮ ነገሥታት እና መንግሥታት እንደነበሩ ይነገራል፡፡ ዳግማዊ አጼ ቴዎድሮስን ለመውጋት የመጣውን የእንግሊዝ ጦር ከሀገር ውስጥ አኩራፊዎች ጋር በመነጋገር መንገድ ለመጥረግ የግብጽ ረጂም የጥፋት እጅ ነበረበት፡፡ ኢትዮጵያ ጸጋዎቿን አውጥታ እና የተፈጥሮ ሃብቷን አልምታ እንዳትጠቀም ግብጽ ከጥንት እስከ ዛሬ ዐይነ-ጥላ ኾናባት ቆይታለች፡፡

ለአንድ ሀገር ብሔራዊ ደኅንነት ውጫዊ ሥጋት ከሚፈጥሩ ጉዳዮች መካከል ድንበር ተሻጋሪ የተፈጥሮ ሃብት አያያዝ እና አጠቃቀም ቀዳሚው ተጠቃሽ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ደኅንነት አኳያ ለዘመናት ትልቁ የሥጋት ምንጭ ኾኖ የዘለቀው የዓባይ ወንዝ ውኃ ነው፡፡

ዓባይ የኢትዮጵያ ብቻ ሳይኾን የአፍሪካ ቀንድ ጅኦ-ፖለቲካ የደኅንነት ገጽታ ተደርጎም ይወሰዳል፡፡ ኢትዮጵያ እና ግብጽ በዓባይ ውኃ ጉዳይ ውዝግብ ውስጥ መግባት የጀመሩት ከአንድ ሺህ ዓመት በፊት በዛጉዌ ሥርወ-መንግሥት እንደነበር ታሪክ ይነግረናል፡፡

በ11ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበረው የዛጉዌ ሥርወ-መንግሥት ንጉስ አጼ ይምርሃነ ክርስቶስ ከግብጾች ጋር በዓባይ ውኃ ጉዳይ ውዝግብ ውስጥ ገብተው ነበር ይባላል፡፡ ከ1066 ዓ.ም እስከ 1072 ዓ.ም የዓባይ ውኃ ፍሰት በከፍተኛ መጠን መቀነሱን ተከትሎ ግብጽ ውስጥ ረሃብ ተከስቶ እንደነበር ይነገራል፡፡ ግብጻዊያን የርሃቡ ምክንያት ኢትዮጵያ የዓባይ ወንዝን አቅጣጫ ማስቀየሯን ተከትሎ የተፈጠረ መኾኑን በማመናቸው ሽምግልና እስከመላክ እንደደረሱ መሪራስ አማን በላይ “የጥንቷ ኢትዮጵያ ትንሳኤ ታሪክ” በሚል ርእስ ባሳተሙት መጽሐፋቸው ላይ ነግረውናል፡፡

ከንጉሥ አጼ ይምርሃነ ክርስቶስ በኋላ የመጡት ንጉሥ እና ቅዱስ ላሊበላም ተመሳሳይ እርምጃዎችን ለመውሰድ ሞክረው እንደነበር ይነገራል፡፡ ከዚያ በኋላም ከአጼ አምደ ጽዮን እስከ አጼ ይስሃቅ፤ ከአጼ ዘርዓያዕቆብ እስከ አጼ ቴዎድሮስ፤ ከአጼ ምኒልክ እስከ አጼ ኃይለ ሥላሴ ዓባይ ወደ ግብጽ የሚያደርገውን ፍሰት ለማስቆም ግብጽ ላይ የማስፈራሪያ እና የማስጠንቀቂያ ፖሊሲዎችን ተጠቅመው እንደነበር ይነገራል፡፡ ይህንን ሁሉ ዛቻ፣ ማስጠንቀቂያ እና ፍራቻ ብቻዋን ስለመቋቋሟ ሥጋት የገባት ካይሮ 1940ዎቹ አጋማሽ ላይ ሰባት የአረብ ሀገራትን አሰባስባ የአረብ ሊግን መሰረተች፡፡ ዛሬ ላይ ላለፉት 12 ዓመታት ከሊጉ ተለይታ የቆየችውን ሶሪያን ጨምሮ 22 የአረብ ሀገራት በአባልነት ተቀላቅለውታል፡፡

ከአረብ ሊግ መመሥረት ማግስት ጀምሮ አህጉራዊውን ፖለቲካዊ ጉዳዮች እንዳሻየ ካልጠመዘዝኩ ለማለት የዳዳትን ግብጽ ለመገዳደር እና አደብ ለማስገዛት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የያኔውን የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እና የአሁኑን የአፍሪካ ኅብረት መሪዎችን አስተባብረው ለመመሥረት ተገደዱ ያሉን የታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር አደም ካሚል ናቸው፡፡ “ግብጽ አንድ ወቅት አፍሪካዊ ሀገር አይደለሁም ለማለት እና ከኅብረቱም ለመውጣት ዳድቷት ነበር” የሚሉት የታሪክ ምሁሩ እንደማያዋጣት ስታውቅ እና ነባራዊ ሁኔታው ስላስገደዳት ብቻ ከኅብረቱ ጋር ትሠራለች ይላሉ፡፡

ከአፍሪካዊነቷ ይልቅ አረብነቷ የሚበልጥባት ካይሮ የያኔውን የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የአሁኑን የአፍሪካ ኅብረት ብትችል ልታፈርሰው እንደምትፈልግ በተደጋጋሚ አሳይታለች፡፡ ኅብረቱን ማፍረስ ካልቻለች ደግሞ ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን ታሪካዊ ቁርኝት ለመነጣጠል የኅብረቱን መቀመጫ እስከ ትሪፖሊ ለማሸሽ ምን ያክል ጊዜ እንደደከመች ማየት በቂ እንደኾነ ፕሮፌሰር አደም ያነሳሉ፡፡ የአረብ ሊግንም ከተቋቋመበት ዓላማ እና መርህ ውጭ ከእስልምና ሃይማኖት ጋር ማስተሳሰር እና በኢትዮጵያ ላይ ለማነሳሳት እንደምትሞክርበት መረዳት ግድ ይላል ይላሉ፡፡

ፕሮፌሰር አደም ከሰሞኑ በሳዑዲ አረቢያ ጂዳ በተካሄደው 32ኛው የአረብ ሊግ ሀገራት ስብሰባ ላይ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ አጀንዳ የኾነበት እና አቋም እስከ መያዝ ያደረሳቸው የግብጽ ጫና እና ፍላጎት በመኖሩ ነው ብለውናል፡፡ በየትኛውም መንገድ ቢመዘን የዓባይ ወንዝ ውኃ የአረብ ሊግ ሀገራት የደኅንነት ሥጋት ሊኾን አይችልም የሚሉት ፕሮፌሰር አደም “አደፈረስክብኝ የሚለውን የዱር እና የቤት እንስሳት ተረታዊ ግጭት” የሚያስታውስ ነው ይላሉ፡፡

የአረብ ሊግ መሰል የአቋም መግለጫዎችን ሲያወጣ ይህ የመጀመሪያው አይደለም፡፡ የሚያመላክተውም ግብጽ አሁንም ድረስ በኢትዮጵያ ጉዳይ ዙሪያ አርፋ እንዳልተኛች በቂ ማሳያ ነው፡፡ ታሪክ የሚነግረን የኢትዮጵያ ጥንካሬ ሁሌም የሚመነጨው ከውስጧ እንጂ ከጠላቶቿ ድክመት አይደለም የሚሉት ፕሮፌሰር አደም “እንዳለመታደል ኾኖ ግን ኢትዮጵያን ኢትዮጵያውያንም አያውቋትም” ብለውናል፡፡

ውስጣዊ ግጭት እና የሠላም እጦት የኢትዮጵያን መከራ ያራዝም ካልኾነ መሠረታዊ ለውጥ አያመጣም የሚሉት የታሪክ ምሁሩ ከትናንቱ መማር፣ ቅድሚያ የሚሰጣቸውን ጉዳዮች መለየት እና ዓለም አቀፋዊውን አሰላለፍ መረዳት ተገቢ ነው ብለዋል፡፡ የአረብ ሊግ ወቅታዊ አቋም እና የግብጽ ጩኽት መጀመር የኢትዮጵያን ውስጣዊ ጉዳይ ከመረዳት የመነጨ እንደኾነም አንስተዋል፡፡

ዘጋቢ፡- ታዘብ አራጋው amara massemedia

Exit mobile version