Site icon ETHIO12.COM

በሸገር ከተማ መስጂድ ግንባታ በፕላኑ መሰረት ቦታ እንደሚሰጥ ስምምነት ተደረሰ፤ ስልሳ ከመቶ የሸገር ከተማ የህዝብ ማዝናኛ ይሆናል

አዲስ ፕላን ተዘጋጅቶ ሊገነባ ዝግጅቱ በተጀመረበት በሸገር ከተማ ምንም አይነት ፕሮጀክት በዘፈቀደ እንዲሰራ እንደማይፈቀድ አስቀድሞ መገለጹ ይታወሳል፡፡ በዚህ መሰረት የእቅድ ሳይሆን የአፈጻጸም ችግር እንዳለበት የተነገረለት ህገወጥ ግንባታዎችን የማፍረስ ሂደት አካል የሆነው የመስጊዶችን ጉዳይ አስመልክቶ ከስምምነት መደረሱ ታወቀ፡፡

ከኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ከአቶ ሽመልስ አብዲሳ ጋር የመከረው የኢትዮጵያ እስልም ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ” ሕዝበ ሙስሊሙ ያቀረባቸውና ለሚያቀርባቸው የመስጂድ ጥያቄዎች በፕላኑ መሠረት ምላሽ ይሰጣል ” ማለታቸውን አስታውቋል፡፡ የሸገር ከተማ አስተዳዳሪ ዶክተር ተሾመ አዱኛ በቅርቡ ለአሃዱ እንደገለጹት የሸገር ከተማ ለመኖሪያና መዝናኛ እንዲያመች ተደርጎ በአዲስ ፕላን እንደሚሰራ፣ ከፕላኑ ውጪ አንድም ግንባታ እንደማይፈቀድ አስታውቀው ነበር፡፡ ከተማዋ የከተማ ግብርና በስፋት የሚጀመርባትም እንደሆነች ተመልክቷል፡፡

የከተማዋ ስልሳ ከመቶ ክፍት የህዝብ መዝናኛዎች፣ ማረፊያ ፓርኮችና አረንጓዴ መስክ እንደሚደረግ ያወሱት ዶክተሩ ” በዚህ ጉዳይ ወደሁዋላ አይባልም” ሲሉ የተዋበ ከተማ የመስራቱ ስራ ቢያንስ በአምስት ኣመት ውስጥ መልኩን እንደሚይዝ አስታውቀዋል፡፡ ስለፈረሱትም ቤቶች ህገወጥነት ሲስረዱ የከተማዋን ፕላን ያከበረ አማራጭ ሊታይ እንደሚችል ጠቁመው አልፈዋል፡፡

ዛሬ የእስልምና ጉዳዮች ከአቶ ሽመልስ ጋር ሰፊ ንግግር ማድረጉን ጠቅሶ ባሰራጨውና ከስር ባስቀመጥነው መገለጫ መሰረት ለሁሉም እምነት ተቋማት በፕላኑ መሰረት ስፍራ እንደሚዘጋጅ፣ በቆርቆሮ መስራት እንደማይቻል፣ ደረጃቸውን የጠበቁ ግንባታዎች ሊሆኑ እንደሚገባ፣ ለጊዜው ሙስሊም ወገኖች የአምልኮ ስፍራ እንዳይቸግራቸው እንደሚደረግ ተገለጿል፡፡

ጠቅላይ ምክር ቤት ያውጣውና ያሰራጨው 12 ነጥቦችን የያዘው መግለጫ ከዚህ በታች የታተመው ነው፡፡

” ሕዝበ ሙስሊሙ ያቀረባቸውና የሚያቀርባቸው የመስጂድ ጥያቄዎች በፕላኑ መሠረት ምላሽ ይሰጣል ” – አቶ ሽመልስ አብዲሳ

ከኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ጋር በተደረገው ውይይት በክልሉ ፕሬዝዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ በኩል የተጠቀሱት ነጥቦች የሚከተሉት ናቸው ፦

  1. ቀደም ብሎ በጉዳዩ ላይ ዉይይት አለመደረጉ ስህተት መሆኑን ገልጸዋል።
  2. በተፈጠረው ሁኔታ ሕይወታቸውን ላጡት ሙስሊሞች ማዘናቸውን ገልጸዋል።
  3. የሸገር ከተማ የሃይማኖትን እሴትን መሠረት አድረጎ እንደሚገነባ እና የእሰልምናን ጨምሮ የሌሎችም ቤተእምነቶችም ተቋማት በብዛት በሸገር ከተማ ፕላን ዉስጥ እንደተካተቱ።
  4. አስፈላጊውን የቤተእምነት መሥሪያ መሬቶችን በፕላኑ መሠረት ለምዕመኑ እንደሚሰጥና በቆርቆሮ ሳይሆን የከተማዋን ፕላን የሚመጥን በርካታ ዘመናዊ መስጊዶች በከተማው እንዲሰሩ እንደሚፈልጉ።
  5. በሸገር ከተማ ላይ በሀገር ደረጃ ሊጠቀስ የሚችል ትልቅና ዘመናዊ መስጂድና ለሌሎች እምነት ተቋማት መሥሪያ ቦታ እንደሚሰጥ።
  6. በሸገር ከተማ ለኢስላማዊ ዩኒቨርሲቲ ግንባታ የሚሆን መሬት እንደሚሰጥ።
  7. ሸገር ከተማ ከ20 እስከ 30 ሚሊዮን ነዋሪዎች ያላት፥ ዘመናዊና በፕላን ብቻ ግንባታ የሚካድባት ከተማ ሆኖ ለመግንባት ሕግ ወጥ ግንባታን መከላከል፥ የተገነቡትን #ማፍረስ_እንደሚቀጥል ለዚህ ሂደት የእምነት ተቋማት ተባባሪ እንዲሆኑ እንፈልጋለን ብለዋል።
  8. አዲሱ የሸገር ከተማ ፕላን ወደ ተግባር እስኪገባ ድረስ ሙሉ ለሙሉ መኖሪያ ቤቶች ባልፈረሱባቸው አከባቢዎች ለሚኖሩ ሙስሊሞች በጊዜያዊነት የሚሰግዱባቸው መስጊዶች የኦሮሚያ ክልል መጅሊስና የሸገር ከተማ አስተዳደር በጋራ በመጋገር መስጂድ መሥሪያ ቦታ እንዲያዘጋጁ።
  9. የሸገር ከተማ ማስተር ፕላን በመጪው ሀምሌ ወር ወደ ተግባር ማዋል ከመጀመሩ በፊት በማስተር ፕላኑ ለእምነት ተቋማት የተዘጋጀውን ስፍራዎችን የሙስሊም ተወካዮች ከክልሉ መንግስት ጋር በጋራ ቀድመው ፕላኑን እንዲመለከቱና እንዲያረጋግጡ፡፡
  10. በሸገር ከተማ ሕዝበ ሙስሊሙ ያቀረባቸውና የሚያቀርባቸው የመስጂድ ጥያቄዎች በፕላኑ መሠረት ምላሽ እንደሚሰጥ።
  11. ሸገር ከተማን ጨምሮ በመላው ኦሮሚያ ክልል ከዚህ ቀደም ሲደረግ እንደነበረው የእምነት ተቋማት እና የመቃብር ሥፍራ መስጠት እንደሚቀጥል።
  12. በሸገር ከተማ ዉስጥ ካሉት ስምንት መቶ (800) የሁሉም እምነት ተቋማት መካከል 656(ስድስት መቶ ሀምሳ ስድስት) የሚሆኑት ከፕላን ዉጭ የተሠሩ በመሆናቸው እነዚህን የሚገነባውን ከተማ ፕላን የማይመጡትን የተለያዩ ቤተእምነቶችን ወደ በሕጋዊና ከተማውን በሚመጥኑ ተቋማት ለመተካት የሚደረገውን ሂደት የኦሮሚያ ክልል መጅሊስም ባለበት የኦሮሚያ ክልል የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ አቅሙን በማጠናከር በዉይይት የእምነት ተቋማቱ ራሳቸው መፍረስ ያለባቸውን እንዲያፈርሱ እንጂ ከአሁን በኋላ መንግስት በራሱ ማፍረስ እንደሚያቆም ገልጸዋል።

Exit mobile version