ETHIO12.COM

በሼፍ ሳሙኤልሰን ማርኩስ ስም ሃያት ሪኤጀንሲ ሆቴል የሚከፍተው ሬስቶራንት ስልጠና አወዛገበ “የደንበኞችን ጾታ መጥራት አትችሉም”

ሼፍ ማርኩስ ሳሙኤልሰን ውድ የዓለማችን የምግብ አዘጋጅ ባለሙያና በዓለም ዙሪያ የበርካታ ታዋቂ ሬስቶራንቶች ባለቤት ነው። ቀደም ሲል እናቱ ሳይሞቱበት ካሳሁን ጽጌ ይባል የነበረው ድንቅ ሙያተኛ ከእህቱ ጋር በጉዲፈቻ ወደ ስዊዲን ወላጆቹ ዘንድ ካመራ በሁዋል የዓለማችን ድንቅ ሰው ሆኗል። ከመቂ አውራ ጎዳና ሰፈር ተነስቶ ዋይት ሃውስ ገብቶ ምግብ ማዘጋጀት ያቻለ ኢትዮጵያዊ ሆኗል። በዚህ ድንቅ የዓለማችን ታዋቂ ምግብ አዘጋጅ ስም ሃያት ሪኤጀንሲ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አዲሱ ህንጻ ላይ ሊከፍት ያሰበው ሪስቶራንት አስተናጋጆች ላይ የተጣለው መብት ግን ከወዲሁ ውዝግብ አስነስቷል።

ነገሩ እንዲህ ነው። ከላይ በተገለጸው መሰረት ሃያት ሪኤጀንሲ ከንግድ ባንክ ዘመናዊ ህንጻ ላይ በተከራየው ዘመናዊ ክፍሎች አዲስ ሬስቶራንት ለመክፈት ደፋ ቀና እያለ ነው። ሬስቶራንቱ ደግሞ የሚሰየመው በኦስካር ተሸላሚውና በሲኤኔን የዓመቱ ምርጥ ሼፍ ተብሎ በተሰየመው ማርኩስ ሳሙኤልሰን (Marcus Samuelsson) ስም ነው። ለዚህ ውድና እጅግ ዘመናዊ ሬስቶራንት አስተናጋጆች ተመልመለው ስልጠና ሲወስዱ ነው ውዝግቡ የተነሳው።

በአስተናጋጆች ስልጠና ወቅት ” የተተቃሚዎችን ጾታ መጥራት አይቻልም” የሚለው ጉዳይ የሰልጣኖችን ጆሮ አቆመው። ” አቶ፣ ወይዘሮ” ማለት ወይም በሴትና ወንድ ጾታ ለይቶ መጥራትን ነውር ያደረገው ስልጠና ግራ ካጋባቸው መካከል ለጊዜው ስሙን የማንጠቅሰው ሰልጣኝ ” በባህላችን ሴትንም ሆነ ወንድ የምንጠራበት አግባብ አለ። ከዚያም በላይ ሴትን ሴት፣ ወንድን ወንድ ማለት ምን ችግር አለው” የሚል ጥያቄ ያነሳል።

የተሰጠው መልስ ግን “ተጠቃሚዎች እንደሱ መጠራትን አይወዱም” የሚል ነው። ዜናውን በቀጥታ የላኩልን “ሰልጣኞቹ ምን አይነት ሰዎችን ለማስተናገድ ነው እየሰለጠኑ ያሉት?” የሚል ብዥታ ተፈጥሯል ብለዋል። ከሁሉም በላይ በአገሪቱ በህግ ደረጃ የወንድና የሴት የጾታ መለያ በግልጽ በተቀመጠበት ሁኔታ ተገልጋዮች በጾታቸው ሳይጠሩ እንዲገለገሉ የተሰጠውን ስልጠና የሚመለከታቸው አካላት እንዲያጠኑትና ማብራሪያ እንዲጠይቁበት ጥሪ አቅርበዋል።

ከሁሉም በላይ ግን ይህ አውሮፓና አሜሪካን እንደሰደድ እያዳረሰ ያለው የተመሳሳይ ጾታ ወላፈን ክራባቱን ለብሶ ወደ አገራችን መግባቱን የሚያመላክቱ መረጃዎች እየወጡ ባለበት በዚህ ወቅት ይህ ዜና መሰማቱ እንዳሳዘናቸው ዜናውን የላኩልን ገልጸዋል።

ቴርዶዞም የሚባለው የእንግሊዝ ድርጅት በሰብአዊ እርዳታ ስም በርካታ ወጣቶችን ማበላሸቱ የታወቀውና ድርጅቱ በይፋ ተዘግቶ ሰላባዎቹ ህክምናና ድጋፍ ካገኙ በሁዋላ በሰጡት ምስክርነት መሆኑንን የዜናው ሰዎች ወደሁዋላ መለስ ብለው አስታውሰዋል። ይህ ሃያት ሪኤጀንሲ የሚከፍተው ሬስቶራንት በታዋቂው የዓለማችን ቅንና ውድ ባለሙያ ስም መሆኑ፣ በኢትዮጵያ ትልቁ የመንግስት ተቋም በሆነው የንግድ ባንክ አዲሱ ህንጻ ላይ መሆኑን የሚያስከትለው አደጋ ከባድ ስለሆነ ነገ ዛሬ ሳይባል ጉዳዩ ሊመረመር እንደሚገባው ዜናውን ያደረሱት ወገኖች አመልክተዋል።

ማርኩስ ሳሙኤልሰንና እህቱ ማያን እናታቸው እነሱን በህጻንነታቸው ይዘው ኩየራ ለህክምና ከሄዱ በሁዋላ በሳምባ በሽታ በመሞታቸው ስውዲን አገር Anne-Marie and Lennart Samuelsson በጉዲፈቻ እንደተሰጡ ታሪካቸው ያስረዳል። ማርኩስ ባደገባት የጉተንበርግ ከተማ የምግብ ዝግጅት ትምሀርት ወሰደ። ለልምድ ጃፓንና አውሮፓ ተጓዘ። በመጨረሻም በ1994 ወደ ኒውዮርክ አቀና። እዛም ደርሶ አኮቪት ሬስቶራንት ተቀጠረ። በአጭር ጊዜ ስሙ ገነነ። በኒውዮርክ ታይምስ የዓመቱ ምርጥ ሼፍ ተባለ። የጀምስ ብሬድ / ሆስካር ተሸላሚ ሆነ።  ከዛም Red Rooster in Harlem, New York. ከፍቶ የራሱን ሬስቶራንት መምራት ጀመረ።

ይህ ድንቅ ሙያተኛ ስሙ ገኖ ዋይትሃውስ ገብቶ ምግብ የማዘጋጀት እምነት አገኘ። ከመቂ አውራጎዳና የተነሳው ጀግና ነጩን ቤት ተንጎራደደበት። ሳሙኤልሰን ግሩፕን አቋቁሞ ጃፓን፣ እንግሊዝ፣ አሜሪካ፣ ቬርሙዳ፣ ስካንዴቪያን አገሮች … ሬስቶራንት አስፋፋ። ይህ ጸሃፊና የቲቪ ፕሮግራም አዘጋጅ እንደሆነ የሚነገርለት ድንቅ የምግብ አዘጋጅ ዘንድ ለመመገብ ረዥም ቀጠሮ መያዝ ግድ ነው።

በ2004 ” እኔ ማን ነኝ” በሚል በታላቅ እህቱ ፋንታዬ አነሳሽነት አባቱን ፍለጋ ወደ አውራ ጎዳና የትውልድ ሰፈሩ አቀና። በዛም አባቱን አገኛቸው። አባቱ ጫማቸውን አውልቀው የእግራቸውን መመሳሰል አሳይተው እንዳስደመሙት ታሪኩ ያስረዳል። አባቱ ከሌላኛዋ ሚስታቸው በዛ ያሉ ልጆች በመውለዳቸው ወንድምና እህቶችን ያገኘው ሳሙኤልሰን ሁሉንም አቅፎና ደግፎ ከፍ እንዳደረጋቸው ስለ እሱ የተዘገቡ ሰነዶች ያስረዳሉ። በሰብአዊ ተግባር ላይ መሰማራቱንም እነዚሁ መረጃዎች ይጠቁማሉ።

እንግዲህ ዜናውን የሚያከብደው ይህ ባለትዳርና የልጅ አባት የሆነው ባለሙያ በስሙ በሚከፈተው እጅግ ውድና ዘመናዊ ሬስቶራንት ለአስተናጋጆች እንዲህ ያለ ስልጠና እንደሚሰጥ ያውቃል? የሚለው ሲሆን፣ ንግድ ባንክስ ምን በተመሳሳይ በዚህ ጉዳይ ላይ ምን ያህል እውቂያ አለው የሚለው ጉዳይ ሲነሳ ነው።

ሬስቶራንቱ ያለምንም ጥርጥር ውድና በቂ ሃብት ያላቸው የሚስተናገዱበት ነው። እንግዲህ ለአዲሱ ሬስቶራንት ” በጾታ ተለይተው መጠራት አይወዱም” የተባሉት ደንበኞቹ እነማን ይሆኑ? ወይም እነማንን ታሳቢ አድርጎ ነው ስልጠናው የተሰጠው? የሚለው ጥያቄ ውሃ የሚያነሳው እዚህ ላይ ነው።

ዝግጅት ክፍላችን ሃያት ሪኤጀንሲ ምላሽ እንዳለው ለመጠየቅ በመስተንግዶ ክፍሉ በኩል ተደጋጋሚ ጥሪ ቢያደርግም ምላሽ አላገኘም። በዜናው እንደተባለው ንግድ ባንክ ታላቅ የመንግስት ተቋምና ሰፊ ደንበኛ ያለው የአገሪቱ የኢኮኖሚ እምብርት በመሆኑ፣ የተጠቀሰው ባለሙያ ዓለም ዓቀፍ እውቅና ያለውና በቀላሉ የማይገኝ ምግባረ መልክም ዜጋ በመሆኑ ከወዲሁ ጥንቃቄ እንዲደረግ የሃያት ሪኤጀንሲ ምላሽ ባይካተትም ዜናውን አትመነዋል። አያት ሪአገንሲ ምላሽ ካለው ለማስተናገድ ዝግጅት ክፍላችን ከወዲሁ ያስታውቃል።

ይህንን ማስፈንጠሪያ ethio12news ተጭነው በቴሌግራም ገጻችን ይከተሉን

Exit mobile version